Saturday, April 1, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናለምርጫ ጉዳዮች ፍርድ ቤት የተሰጠው የውሳኔ መስጫ ጊዜ ማጠሩ ቅሬታ ቀረበበት

ለምርጫ ጉዳዮች ፍርድ ቤት የተሰጠው የውሳኔ መስጫ ጊዜ ማጠሩ ቅሬታ ቀረበበት

ቀን:

በግንቦት ወር ለሚካሄደው አገራዊ ምርጫ አከራካሪ የምርጫ ጉዳዮች በፍርድ ቤት የሚስተናገዱበት ደንብ ላይ የተቀመጡ አቤቱታ፣ ቅሬታ ማቅረቢያና ውሳኔ መስጫ ላይ የተቀመጡ ጊዜያት ቅሬታ ቀረበባቸው፡፡

በጠቅላይ ፍርድ ቤት ተዘጋጅቶ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተመራው ረቂቅ ደንብ፣ በቅድመና በድኅረ ምርጫ የሚከሰቱ ውዝግቦችን ለመፍታት፣ ከመደበኛው ፍርድ ቤት ውጪ ራሳቸውን የቻሉና በምርጫ ላይ ብቻ ያተኮሩ ችሎትን የሚያቋቁም ነው፡፡

ረቂቅ ደንቡ መጪው አገራዊ ምርጫ ነፃ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ እንዲሆን ለማስቻል የተዘጋጀ እንደሆነ፣ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ተስፋዬ ንዋይ ገልጸዋል፡፡

ረቂቅ አዋጁ ‹‹በመራጮች ምዝገባ ወቅት ከመመዝገብ ያላግባብ ተከልክያለሁ›› የሚል አቤቱታ የተነሳው ቅሬታ በአዲስ አበባ ወይም በድሬዳዋ ከተማ ከሆነ፣ ለፌዴራል መጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሚቀርብ ሲሆን፣ አቤቱታው የተነሳው ደግሞ በክልል ከሆነ በወረዳ ፍርድ ቤቶች በአምስት ቀናት ውስጥ እንደሚቀርብ ተመላክቷል፡፡

በሌላ በኩል አቤቱታ የቀረበበት ፍርድ ቤት አመልካች ያቀረበው አቤቱታ መነሻ የሚሆን ምክንያት ያለው መሆኑን ያመነ እንደሆነ፣ አቤቱታውና መጥሪያው በ48 ሰዓታት ውስጥ ለተጠሪው ደርሶት ተጠሪው በደረሰው ከ48 ሰዓታት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ እንደ ሁኔታው መልሱን በጽሑፍ ይዞ እንዲቀርብ ወይም በቃል ቀርቦ እንዲያስረዳ ትዕዛዝ ይሰጣል፡፡

በሌላ በኩል ማንኛውም በመራጭነት የተመዘገበ ሰው ድምፅ ለመስጠት ተከልክያለሁ በማለት ለምርጫ ክልሉ ቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ አቤቱታ ቀርቦ ኮሚቴው በሰጠው ውሳኔ ያልተስማማ ከሆነ፣ አቤቱታውን በ24 ሰዓት ውስጥ ማቅረብ እንዳለበት ይገልጻል፡፡

መጥሪያ እንዲደርስና ስለማዘዝ በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩ መጣራት ያለበት ተጠሪው ወይም ጉዳዩ የሚያገባው ሰው በተገኘበት መሆኑን በበቂ ምክንያት ያመነ እንደሆነ፣ ተጠሪው ወይም ጉዳዩ የሚያገባው ሰው በ24 ሰዓት ውስጥ እንዲቀርብ ትዕዛዝ እንደሚሰጥ በረቂቅ ደንቡ ተገልጿል፡፡

ይሁን እንጂ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍተሕ ቋሚ ኮሚቴ ረቂቅ ድንቡን አስመልክቶ ዓርብ መጋቢት 10 ቀን 2013 ዓ.ም. ባደረገው ውይይት፣ ውሳኔ መስጠትን አስመልክቶ በረቂቅ ደንቡ ላይ የተቀመጠውን ከአሥር ቀናት ማለፍ የለበትም መባሉ የፍርድ ቤትን ነፃነት የሚገፍና አስገዳጅ መሆኑ አግባብ አይደለም የሚል አስተያየት አቅርቧል፡፡

በሌላ በኩል የቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ በአምስት ቀናት ውስጥ ውሳኔ መስጠት እንዳለበት የሚያስቀምጥ መሆኑን፣ ነገር ግን የሚቀርቡ አቤቱታዎች በባህሪያቸው ምርመራን የሚፈልጉ በመሆናቸው በአምስት ቀናት ውስጥ ሊያልቁ የማይችሉ ናቸው ወይ ተብሎ በምክር ቤቱ ተጠይቋል፡፡

በመራጭነት የተመዘገበ ሰው ድምፅ ለመስጠት ተከልክያለሁ ብሎ በ24 ሰዓት ውስጥ አቤቱታ ማቅረብ እንዳለበት የሚገልጸው አንቀጽ፣ በሌላ በኩል የተከለከለ ሰው በ24 ሰዓት ውስጥ አቤቱታ ማቅረብ የማይቻልባቸው አስቸጋሪ ሁኔታዎች ሊፈጠሩ እንደሚችሉ ከምክር ቤቱ የሕግ ክፍል በኩል በውይይቱ ላይ የቀረበው ጥያቄ ያመለክታል፡፡

ለተነሱት ጥያቄዎች አቶ ተስፋዬ መልስ ሲሰጡ ጊዜው ገደብ ተለይቶለት ካልተቀመጠ፣ ድምፅ ከተቆረጠና ቆጠራ ከተካሄደ በኋላ የሚፈጠሩ ችግሮችን መፍታት አስቸጋሪ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡

አቶ ተስፋዬ አክለውም በየትኛውም ዓለም የጊዜ ገደብ ያልተቀመጠበት የምርጫ ፍርድ ቤት የለም ብለዋል፡፡ ነገር ግን ካሉት ነባራዊ አገራዊ ሁኔታዎች አንፃር የምርጫ አስፈጻሚዎች፣ የተከራካሪዎችና እንዲሁም የፍርድ ቤቶች ዝግጁነት ካለ በተገለጸው ሰዓት ውስጥ ጉዳዩን ማከናወን እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡

በተጨማሪም ዳኞች ለህሊናቸው ተገዥና ግዴታ ያለባቸው ከመሆኑም በላይ የዳኝነትን ሥራ በጊዜ ተገማች በማድረግ አሁን በችሎቶች ላይ የሚታየውንና በተከራካሪዎች ለጉዳይ መጓተት የሚነሳውን ችግር ግምት ውስጥ በማስገባት፣ የምርጫ ጉዳይ እንደ ሌሎች የፍርድ ቤት ውሳኔዎች ሁሉ ተጓቶ ለሌላ ጊዜ መራዘም ስለሌለበት ነው ብለዋል፡፡

በአሁኑ ጊዜ በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተማ የምርጫ ጉዳዮች የሚዳኙባቸው አሥር ችሎቶች በከፍተኛ ፍርድ ቤት እያንዳንዳቸው ሦስት ዳኞችን በመያዝ፣ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ደግሞ እያንዳንዳቸው አንድ ዳኛ በመያዝ፣ በአጠቃላይ 21 ችሎቶች እየተደራጁ እንደሆነና በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በኩልም ሥራዎች መጀመራቸውን አቶ ተስፋዬ ገልጸዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ተወግዘው የነበሩ ሦስቱ ሊቀጳጳሳትና 20 ተሿሚ ኤጲስ ቆጶሳት ውግዘት ተነሳ

_ቀሪዎቹ ሦስት ህገወጥ ተሿሚዎች የመጨረሻ እድል ተሰጥቷቸዋል ​ ጥር 14...

በሕወሓት አመራሮች ላይ ተመስርቶና በሂደት ላይ የነበረው የወንጀል ክስ ተቋረጠ

በቀድሞ የትግራይ ክልል ፕሬዚደንት ደብረጽዮን ገብረሚካኤ,(ዶ/ር)ና ባለፈው ሳምንት በተሾሙት...

[የምክር ቤቱ አባል ላቀረቡት ጥያቄ በተሰጣቸው ምላሽ አቤቱታቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር ትክክል ነው? ምነው? ምክር ቤቱም ሆነ...

የጉራጌ የክልልነት ጥያቄ ትኩሳት

ቅዳሜ መጋቢት 16 ቀን 2015 ዓ.ም. በጉራጌ ዞን ወልቂጤ...