በወርኃ ግንቦት መጨረሻ አካባቢ እንደሚካሄድ የተነገለረት ምርጫ 2013 ዓ.ም. እየተቃረበ ነው፡፡ በድምፁ ወሳኙን ዳኝነት የሚሰጠው ሕዝብ ከወዲሁ በርካታ ሁነቶችን እየታዘበ ነው፡፡ በምርጫ ከሚፎካከሩ ግለሰቦችና የፖለቲካ ፓርቲዎች 500 ያህል አቤቱታዎችና ቅሬታዎች መቅረባቸው እየተሰማ ነው፡፡ ይህ በራሱ መጪው ምርጫ እንደታሰበው ነፃና ተዓማኒነት ያለው ሳይሆን፣ የተለመደው ሸፍጥ ሊበክለው ይሆን ወይ የሚል አሳሳቢ ጥያቄ ያጭራል፡፡ መራጩን ሕዝብ ከጎናቸው አሠልፈው ለሰላማዊው የፖለቲካ ትግል ፉክክር ሙሉ ጊዜያቸውን ያለባቸው ተፎካካሪዎች፣ ገና ከአሁኑ ቅሬታና አቤቱታ ማዥጎድጎድ ከጀመሩ ብርቱ ችግር አለ ማለት ነው፡፡ ‹‹ድመት መንኩሳ አመሏን አትረሳ›› እንደሚባለው፣ በገዥው ፓርቲ ሠፈር ያለው ሁኔታ መመርመር ይኖርበታል፡፡ መጪውን ምርጫ ከሸፍጥና ከአሉባልታ መፅዳት ካልተቻለ፣ በሰላምና በነፃነት ይከናወናል ማለት ዘበት ነው፡፡ በዚህ በሠለጠነ ዘመን ሥልጣን የሚያዘው በምርጫ ብቻ ነው መባል አለበት፡፡ የፖለቲካ ፉክክሩ በውጣ ውረድና በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ የሚካሄድ ቢሆን እንኳ፣ ወሳኙን መራጭ ሕዝብ ማዕከል ማድረግ ካልተቻለ ልፋቱ ሁሉ ከንቱ ይሆናል፡፡ ገዥው ፓርቲም ሆነ ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ምርጫውን ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ እንዲያደርጉ ይጠበቃሉ፡፡ ሁሉም ወገኖች የሚፈለግባቸውን በሰላማዊና በዴሞክራሲያዊ መንገድ ማከናወን ሲያቅታቸው፣ የሕዝብን አደራ እንደበሉ ይቆጠራሉ፡፡ ሕዝብ የሥልጣን ሉዓላዊ ባለቤት እንደሆነ በተጨባጭ ሊረጋገጥ የሚችለው፣ እንደሚባለው የምርጫው ሒደት ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሲሆን ብቻ ነው፡፡ ከሸፍጥና ከአሉባልታ ሲፀዳ ነው፡፡
እንደ ማንኛውም ታዳጊ አገር በኢትዮጵያም የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው ሒደት አንድ ዕርምጃ ወደፊት እንዲራመድ ሲፈለግ፣ ሕዝቡን ማዕከል ማድረግ አለበት፡፡ ሕዝብ በንቃት የሚሳተፍበትና መብቱን የሚያስከብርበት ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ የግድ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ የምርጫውና የፖለቲካው ሒደት ተዓማኒነት ሊኖረው ይገባል፡፡ የሕዝቡ ተሳትፎ ሊኖር የግድ ነው ሲባልም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያለውና የሕዝብን ይሁንታ ያገኘ ምርጫ እንዲካሄድ፣ ገዥውን ጨምሮ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች ዝግጁ መሆን አለባቸው፡፡ ሕዝቡ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶቹ ተጠብቀው ያለ ምንም መሸማቀቅ የፈለገውን እንዲመርጥ መንገዱ መመቻቸት አለበት፡፡ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚያጋጥሟቸው ችግሮች በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ውሳኔ ዕልባት እንደሚያገኙ ቢጠበቅም፣ ሁሉም ወገኖች በሀቅ ካልሠሩ በምርጫው ሒደት ላይ የሚፈጥረው ሳንካ ሊጤን ይገባዋል፡፡ የገዥው ብልፅግና ፓርቲ አመራሮች፣ በየደረጃው ያሉ የመንግሥት መዋቅር ሹማምንት አላስፈላጊ ድርጊቶች ፈር መያዝ ይኖርባቸዋል፡፡ በሌላ በኩል የውስጥ ችግሮችን በሠለጠነና በዴሞክራሲያዊ አግባብ መፍታት ያለበት ማንኛውም ፓርቲ፣ መጀመሪያ አባላቱንና ደጋፊዎቹን ለሰላማዊ የፖለቲካ ትግል የሚመጥኑ የማድረግ ግዴታ አለበት፡፡ የራስን የውስጥ ጉዳይ ሳያስተካክሉና ለሰለማዊ የፖለቲካ ፉክክር የሚያበቃ አቋም ሳይኖር፣ የምርጫውን ሒደት ለማደፍረስ አሉባልታ ውስጥ መዘፈቅ መቆም ይኖርበታል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሰለቸው ሸፍጥና አሉባልታ ነው፡፡
ገዥው ፓርቲ በተደጋጋሚ ለሕዝብ ቃል እየገባ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው የመንግሥታቸው ኃላፊነት ምርጫውን ነፃ፣ ዴሞክራሲያዊና ተዓማኒነት እንዲኖረው ማድረግ ነው ብለዋል፡፡ ይህ ለሕዝብ የተገባ ቃል እዚህ ግቡ በማይባሉ ምክንያቶች ቢጣስ ስለሚያሳፍር ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ገዥው ፓርቲ አባላቱም ሆኑ ደጋፊዎቹ ከፀረ ዴሞክራሲ ድርጊቶች እንዲታቀቡ ማድረግ አለበት፡፡ ለሕዝብ የገባው የአደራ ቃል እንዳይታጠፍ ፅኑ ፍላጎት ካለው የመወዳደሪያ ሜዳው ከእንከን የፀዳ እንዲሆን መሥራት ይኖርበታል፡፡ ሥልጣን ላይ ለመቆየት የረጅም ጊዜ ዕቅድ ቢኖረው እንኳ፣ ሥልጣኑ የሚገኘው በሕዝብ ድምፅ ብቻ እንደሆነ ማመን ይጠበቅበታል፡፡ ምርጫ ሕገ መንግሥታዊ መብት በመሆኑ ሁሉም ዜጋ የፈለገውን በነፃነት መርጦ፣ ኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ብርሃን እንዲታይባት ኃላፊነቱን መወጣት ግድ ይለዋል፡፡ ‹‹መልካም ስም ከመልካም ሽቶ ይበልጣል›› እንደሚባለው ከሥልጣን በላይ የአገር ህልውና ይቅድም፡፡ ሕዝብ ይከበር፡፡ የሸፍጥና የአሉባልታ በር ይዘጋ፡፡ በኢትዮጵያ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ምርጫ ሲቃረብ ድምፃቸው ከምንጊዜውም በላይ ጎልቶ መደመጡ አዲስ አይደለም፣ ምንም ችግር የለውም፡፡ ነገር ግን ድምፃቸው ተሰምቶ የማይታወቅ ፓርቲዎች ሳይቀሩ ቀፎው እንደተነካበት የንብ መንጋ ከየመሸጉበት ተንጋግተው ግርግር መፍጠራቸው፣ ዴሞክራሲያዊ ሒደትን አያሳይም፡፡ እውነተኛ ዴሞክራሲ በአንድ አገር ላይ የሚያብበው ጠንካራ የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃነት ሲንቀሳቀሱ ብቻ ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደሚያራምዱት አቋም የሕዝብን ቀልብ ለመሳብ ተግተው መሥራት አለባቸው፡፡ የራሳቸውን የቤት ሥራ ሳይሠሩ በሥልጣን ላይ ያለው ፓርቲ ድክመቶች ላይ ብቻ በማተኮር ለመንቀሳቀስ ሲሞክሩ፣ ሕዝቡ በበኩሉ የእናንተስ አማራጭ የታለ ይላል፡፡ ሸፍጥና አሉባልታ ፋይዳ የላቸውምና፡፡
በአራቱም ማዕዘናት የሚኖረው መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ለአገሩ መድኅን ሊሆኑ የሚችሉ ተፎካካሪዎችን ማየት ይፈልጋል፡፡ እጅግ አስመራሪ ከሆነው የድህነት ማጥ ውስጥ ጎትተው የሚያወጡት የፖለቲካ ድርጅቶችን ይሻል፡፡ የተሻለ ፖሊሲና አማራጭ ያላቸው ተፎካካሪዎች ምን ይዘው እንደመጡለት እንዲነግሩት ነው የሚፈልገው እንጂ፣ የዘመናት ቁስሉን እየነካኩ እርስ በርስ የሚያባሉትን አይደለም፡፡ ብሔርና እምነትን እየታከኩ በደሙ የሚነግዱ ቁማርተኞችን ሳይሆን፣ ከድህነት አረንቋ ውስጥ መንጥቀው የሚያወጡትን ጥራት ያለው ራዕይ የሰነቁትን እየፈለገ ነው ያለው፡፡ የግጭት ነጋዴዎችን ሳይሆን አስተማማኝ ሰላም የሚያሰፍኑትን የታላችሁ እያለ ነው፡፡ በተጨማሪም ዴሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብቶቹን አስከብረው በአገሩ ዘለቄታዊነት ያለው ልማት ለማረጋገጥ ቆርጠው የተነሱ ፓርቲዎች ነው እየጎመጀ ያለው፡፡ ተፎካካሪዎች ድህነትን ለማስወገድ ምን ዓይነት ፖሊሲ ይዛችኋል? ሰብዓዊ መብት ታከብራላችሁ ወይ? ለሐሳብ ነፃነት መብት ትቆማላችሁ? ተዘዋውሮ የመሥራትና ሀብት የማፍራት መብት ታረጋግጣላችሁ? የመደራጀት መብት ታስከብራላችሁ? የኃይል ማመንጫ ግድቦችን፣ መንገዶችን፣ የባቡር መስመሮችን፣ ዘመናዊ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ልማቶችን ታስፋፋላችሁ? ትምህርት ቤቶችን፣ ዩኒቨርሲቲዎችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ወዘተ በጥራት ትገነባላችሁ? የአገሪቱን ሉዓላዊነት ታስከብራላችሁ? የጠራ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አላችሁ? የመሳሰሉ በርካታ ጥያቄዎች ከሕዝብ ይቀርባሉ፡፡ ሕዝብ ሊከበር ይገባዋል፡፡ ሸፍጥና አሉባልታ ለአገር አይጠቅሙም፡፡
ተፎካካሪ ፓርቲዎች ከገዥው ፓርቲ ጋር ያላችሁን ችግር እንዴት ነው የምትፈቱት? ገዥው ፓርቲስ ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ሊኖረው የሚገባውን ግንኙነት ምን መምሰል አለበት? ተፎካካሪ ፓርቲዎች በአገራዊ የጋራ ጉዳዮች ላይ ከገዥው ፓርቲ አቋማችሁ ለምን የተለየ ይሆናል? ገዥው ፓርቲስ ለምን የተፎካካሪ ፓርቲዎች ተሳትፎ እንዲገደብ ታደርጋለህ? ተፎካካሪ ፓርቲዎች ለሰላማዊ የፖለቲካ ትግሉ ስትሉ በሰጥቶ መቀበል መርህ ገዥውን ፓርቲ ለምን ለመቅረብ አትፈልጉም? ገዥው ፓርቲስ ተፎካካሪ ፓርቲዎችን ፋይዳ ቢስ እያደረግክ ለምን ታጣጥላለህ? ተፎካካሪ ፓርቲዎች በአገር ውስጥ እንቅስቃሴያችሁ ችግር ሲገጥማችሁ ሕጋዊውን መንገድ ተከትላችሁ መብታችሁን ለማስከበር እስከ መጨረሻው ትታገላላችሁ? ገዥው ፓርቲስ በሰላማዊ የፖለቲካ ትግሉ ውስጥ የሚገኙትን ተፎካካሪ ፓርቲዎች ለምን ማንገላታት ጀመርክ? ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ወሳኙን የሕዝብ ድጋፍ ችላ እያላችሁ ለምን ከኋላ ሆነው የሚገፉዋችሁ ላይ ብቻ ትለጠፋላችሁ? ለምን እርስ በርስ ትባላላችሁ? ገዥው ፓርቲስ ለምን የሕዝብ ድጋፍ እንዳያገኙ ታደናቅፋለህ? በርካታ የሕዝብ ጥያቄዎች ይነሳሉ፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች ገዥው ፓርቲም ሆነ ተፎካካሪዎች መመለስ አለባቸው፡፡ ሕዝብን የማያከብር የፖለቲካ ትግል ውጤት አይኖረውም፡፡ ሸፍጥና አሉባልታ የአገር ፀሮች ናቸው፡፡
ምርጫ 2013 ሒደቱ ፍፁም ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሊሆን የሚችለው ከሸፍጥና ከአሉባልታ ሲፀዳ ብቻ ነው፡፡ እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ሊኖር የሚችለው ተፎካካሪ ፓርቲዎች ሕዝቡን አክብረው ሲንቀሳቀሱ ብቻ ነው፡፡ ለዘመናት ውስጣቸው የተቋጠረውን ቂምና ጥላቻ ይዘው ወደ ምርጫ የሚገቡ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፣ እያንዳንዱን ችግር ለምርጫው እንከንነት ስለሚጠቀሙበት ሕዝቡን ያሳዝኑታል፡፡ በሕዝብ ድምፅ እተማመናለሁ የሚል ማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ግን ሕዝብን ብቻ ነው የሚያከብረው፡፡ ሕዝብን እናከብራለን የምትሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ራሳችሁን ለዚህ አዘጋጁ፡፡ ምርጫው ከሸፍጥና ከአሉባልታ ይፅዳ ሲባል እኮ ከዚህ ቀደም የተካሄዱት ዓይነት አምስት አሳዛኝ ምርጫ መሰል ድራማዎች እንዳይደገሙ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን ለአገራቸው የመጨረሻውን መስዋዕትነት ጭምር በመክፈል፣ መጪውን ምርጫ ዓለም አቀፍ ደረጃውን እንዲጠብቅ መታገል አለባቸው፡፡ ገና ከአሁኑ ከምርጫ የሚያፈገፍጉም ሆነ ሒደቱን ለማበላሸት የሚያሴሩ ጭምር መገንዘብ ያለባቸው፣ ይህንን መልካም አጋጣሚ ማደፍረስ የሚያስከፍለው ዋጋ እጅግ ከፍተኛ መሆኑን ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ፣ መንግሥት፣ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፣ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ የሲቪል ማኅበረሰቡ፣ ሚዲያውም ሆነ ሌሎች ይመለከተናል የሚሉ ባለድርሻ አካላት ለቅድመ ምርጫ ሒደቱ ስኬት በሚገባ ኃላፊነታቸውን ከተወጡ፣ ምርጫውም ሆነ ከምርጫው በኋላ የሚኖሩት ጊዜያት ሰላማዊ ሆነው ይቀጥላሉ፡፡ ካልሆነ ግን የተለመደው አሳዛኝና አሳፋሪ የምርጫ ድራማ ሌላ ጦስ ይዞ መምጣቱ አይቀርም፡፡ የቅድመ ምርጫ ሒደቱ ከሸፍጥና ከአሉባልታ እንዲፀዳ ጥረት ይደረግ!