በኢትዮጵያ ከፍተኛ የጤና ችግር ከሚባሉት ተላላፊ በሽታዎች መካከል ዋነኛዎቹ በሆኑት በቲቢና መድኃኒት በተላመደ ቲቢ በየዓመቱ 164 ሺሕ ሰዎች እንደሚያዙ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ሚኒስትር ዴኤታው ደረጀ ድጉማ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ከእነዚህም መካከል 157 ሺሕ ሰዎች ከቲቢ፣ የቀሩት 1,400 ሰዎች ደግሞ መድኃኒቱን ከተላመደ ቲቢ ጋር አብረው ይኖራሉ፡፡
‹‹ቲቢ በሽታን ለመግታት ጊዜው አሁን ነው›› በሚል መሪ ቃል 15ኛው ዓመታዊ የቲቢ ምርምር የሦስት ቀናት ጉባዔ መክፈቻና የዘንድሮው የዓለም የቲቢ ቀን መጋቢት 13 ቀን 2013 ዓ.ም. በተከበረበት ሥነ ሥርዓት ላይ ሚኒስትር ዴኤታው እንዳሳሰቡት፣ በቲቢ ከሚያዙትም መካከል በየዓመቱ 21 ሺሕ፣ ሰዎች ለኅልፈት ይዳረጋሉ፡፡
ፀረ ተህዋስያንን የተለማመደ ቲቢ ያደረባቸው ዜጎች ደግሞ ሞትና በሽታውን ወደ ሌላ የማስተላለፍ ዕድላቸው በጣም ከፍተኛ እንደሆነ፣ መድኃኒቱን የተላመደ ቲቢ ብቻ ሳይሆን፣ መድኃኒቱን ያልተላመደውም ቲቢ በደንብ ሕክምና ካላገኘ ወደ መድኃኒት የተላመደ ቲቢ ሊቀየር ወይም ሊተላለፍ እንደሚችል ሚኒስትር ዴኤታው አስገንዝበዋል፡፡
ከዚህም ሌላ በቲቢ ከተያዙትና ከፍ ብሎ ቁጥራቸው ከተገለጹት ሰዎች መካከል 71 በመቶ የሚሆኑት ወደ ሕክምና ተቋም እየቀረቡ መድኃኒት ሲያገኙ፣ የቀሩት 29 በመቶ ያህሉ ደግሞ ወደ ተቋሙ እንደማይመጡና በዚህም የተነሳ ምንም ዓይነት ሕክምና እንደማያገኙ ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
የበሽታው ምልክት የታየባቸውን በአፋጣኝ ወደ ሕክምና ተቋማት ማምጣት፣ በአንድ ተቋም ብቻ የተጣለ ሳይሆን ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላትና ማኅበረሰቡም የበኩሉን ዕገዛና አስተዋጽኦ ሊያደርግ ይገባል፤›› ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፣ መንግሥት በበኩሉ የሕክምና ሥርዓቱን ለማስፋፋት ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑንና መድኃኒት ለተላመደ ቲቢ በተወሰኑ ቦታዎች ላይ ብቻ ይሰጥ የነበረው ሕክምና በ64 ሆስፒታሎች ጭምር እንዲሰጥ መደረጉን አመልክተዋል፡፡
የቲቢ በሽታን ለመግታት በተሠሩ ሥራዎች ከፍተኛ መሻሻል ቢኖርም፣ አሁንም በዓለም አቀፍ ደረጃ በቲቢ በሽታ እየተጠቁ ካሉ 30 አገሮች ኢትዮጵያ አንዷ በመሆኗ ብዙ ሥራዎች ይቀራሉ ብለዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የውስጥ ደዌና የሳምባ ስፔሻሊስት አምሳሉ በቀለ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የቲቢና የኮሮና በሽታ ምልክቶች ተመሳሳይ በመሆናቸው ሳል ያለባቸው ሰዎች ኮሮና እንደያዛቸው በማሰብ በቤታቸው የመቆየት አዝማሚያ ማሳየታቸውን ገልጸው፣ ሳል በተለይም ሁለት ሳምንትና ከዚያ በላይ የቆየ ሳል ሲኖር ለቲቢ መመርመር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በሁሉም ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች ውስጥ በሚገኙ ከአራት ሺሕ በላይ መንግሥታዊና በተፈቀደላቸው ከ800 በላይ መንግሥታዊ ባልሆኑ ጤና ተቋማት የቲቢ በሽታ ምርመራ ሕክምናና ክትትል፣ በ67 ጤና ተቋማት ደግሞ መድኃኒት የተላመደ ቲቢ ሕክምና እንደሚሰጥ ከሦስት ሺሕ የማያንሱ የቲቢ መመርመርያ ላቦራቶሪዎችም አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ መረጃው ያመለክታል፡፡
ቲቢን የመከላከሉ ሒደትና ተግዳሮቱ
በአማርኛ ‹‹የሳምባ ነቀርሳ›› የሚባለው የቲቢ በሽታ፣ ቲቢ የተባለውን ስያሜ ያገኘው ቲዩበርክሎሲስ የሚለውን መጠርያ በአህፅሮተ ቃል በመውሰድ ነው፡፡ መንስዔውም አልፎ አልፎ እንደሚናገር ብርድ ወይም ነፋስ ሳይሆን ረቂቅ በሆነው ባክቴሪያ ነው፡፡
ከጤና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በኢትዮጵያ የቲቢ በሽታን የመከላከልና መቆጣጠር ሥራ ከተጀመረ ስድስት አሠርታት ያስቆጠረ ሲሆን፣ በዋናነት የምትጠቀምባቸው የዓለም ጤና ድርጅት ለአባል አገሮች የሚያቀርቧቸውን ሥልቶች ነው፡፡
በእነዚህም ሥልቶች በመታገዝና የዘላቂ ልማት ዕቅድ አካል በሆነው የጤናው ዘርፍ ዕቅዶች በሚመሩት አገራዊ የቲቢ በሽታ መከላከልና ቁጥጥር ሥልታዊ ዕቅዶችን አዘጋጅታለች፡፡ በአሁኑ ወቅት በሥልታዊ ዕቅዶች በመታገዝ የሚሰጡ አገልግሎቶችን በሁሉም ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች ማድረስ በመቻሉ ብዙ ሰዎች የቲቢ በሽታ ምርምርና ሕክምና አገልግሎቶችን በማግኘታቸው የበርካቶችን ሕይወት መታደግ መቻሉን ሚኒስቴሩ ይገልጻል፡፡
ለዚህም በአብነት ሊጠቀሱ የሚችሉት በየዓመቱ አዳዲስ በቲቢ በሽታ የሚያዙ ሕሙማን ምጣኔ በ2005 ዓ.ም. መጨረሻ ከነበረው 247 ከ100 ሺሕ፣ በ2012 ዓ.ም. ወደ 140 ከ100 ሺሕ መውረድና በቲቢ የሚከሰተውን የሞት ምጣኔ በ2005 መጨረሻ ከነበረው 35 ከ100 ሺሕ፣ በ2012 ወደ 22 ከ100 ሺሕ መውረድ ናቸው፡፡
ይሁንና ውጤቶች የሚያበረታቱ ናቸው ቢባልም፣ በበሽታው ላይ ቀጥሎ የተጠቀሱና ልዩ ትኩረት የሚሹ ችግሮች እንዳሉ መረጃው ጠቁሞ፣ ከችግሮቹም መካከል የቲቢ በሽታ ይገኝባቸዋል ተብለው ከሚታሰቡ 30 ከመቶ የሚደርሱ ወደ ሕክምና አለመምጣታቸው አንዱ ነው፡፡ የቲቢ መድኃኒቶች የተላመዱ ተህዋሲያን መፈጠርና መምጣት፣ የኤችአይቪ ወረርሽኝ ተፅዕኖ፣ በቲቢ በሽታ መከላከልና ቁጥጥር ላይ የሚንቀሳቀሱ አጋር ድርጅቶች አናሳ መሆን ፈታኝ ሆኗል፡፡ እንዲሁም የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በቲቢ በሽታ መከላከልና ቁጥጥር ላይ እያስከተለ ያለው አሉታዊ ተፅዕኖም ተጠቃሽ ነው፡፡
የተጠቀሱትንና ሌሎች የተለዩ ችግሮችን መቅረፍ ያስችላሉ የተባሉትንና ከዘንድሮ ጀምሮ ለአምስት ዓመታት የሚቆይ የቲቢና ሥጋ ደዌ በሽታዎች ሥልታዊ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ተግባር መገባቱ ታውቋል፡፡
የዕቅዱም ግቦች በየዓመቱ አዲስ በቲቢ በሽታ የሚያዙ ሕሙማን ምጣኔ በ2012 ዓ.ም. ከነበረው 140 ከ100 ሺሕ በ2018 ወደ 91 ከ100 ሺሕ ማውረድ፣ በቲቢ የሚከሰተውን የሞት ምጣኔ በ2012 ዓ.ም. ከነበረው 22 ከ100 ሺሕ፣ በ2018 ወደ 7 ከ100 ሺሕ ማውረድና ቤተሰቦች ቲቢ ሕሙማንን ለማሳከም ከተጠቃሚ ኪስ የሚወጣን ወጪ ከ25 በመቶ በታች ማውረድ ተብለው መለየታቸውን ሚኒስቴሩ ገልጿል፡፡