የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ የተወሰኑ ምርጫ ጣቢያዎች አከላለልን አስመልክቶ የአፋር ክልል ያቀረበውን ቅሬታ መርምሮ በዛሬው እለት ውሳኔ አሳለፈ።
ምርጫ ቦርድ ይፋ ያደረገው የምርጫ ጣቢያዎች አወቃቀር የአፋር ክልል የአስተዳደር ወሰን ውስጥ የሚገኙ የተወሰኑ ቀበሌዎችን በሶማሌ ክልል ስር እንዲካለሉ ማድረጉ ተገቢ አይደለም የሚል አቤቱታ የአፋር ክልል አቅርቦ የነበረ ሲሆን ይህንንም አስመልክቶ ሪፖርተር ባለፈው እሁድ እትሙ መዘገቡ ይታወሳል።
ምርጫ ቦርድ ዛሬ ባወጣው መግለጫ ከአፋር ክልል የቀረበውን አቤቱታ በመመርመር ቅሬታ የቀረበባቸው የምርጫ ጣቢያዎይች እንዳይቋቋሙ መወሰኑን አስታውቋል።
ቦርዱ በ2007 ዓ.ም የተጠቀመበትን የመረጃ ዝርዝር ለ6ተኛው አገራዊ ምርጫ በመጠቀም የምርጫ ጣቢያዎችን ያቋቋመ እንደሆነ የሚገልጸው መግለጫው ፣ በዚህ መሠረት የሚቋቋሙት የምርጫ ጣቢያዎችም በክልሎች መካከል ያሉ የአስተዳደር ወሰን ጥያቄዎችን የሚወስኑ እንዳልሆነ አስታውቋል።
ቢሆንም ይህ ቅሬታ በምንም መልኩ በዘንድሮው ምርጫ ለሰላም መደፍረስ ምክንያት እንዳይሆን በማሰብ በአፋር ክልል እንዲቋቋሙ ከተወሰነው የምርጫ ጣቢያዎች ውስጥ ቅሬታ በቀረበባቸው ቀበሌዎች ውስጥ የሚቋቋሙ 30 የምርጫ ጣቢያዎች እንዳይቋቋሙ መወሰኑን አስታውቋል።
እነዚህም በጋላእቶ/አዳይሌ ፣በአዳይቱ/አዳይቱ ፣ በቴውኦ/አላሌ ፣በጉርሙዳሊ/ዳንሌሄላይ ፣በኡንዳፎኦ/ኡንዱፎ ፣በጋዳማይቱ/ጋርባኢሴ ፣በአፍዓሶ/አፉአሴ ፣በባላእቲ ጎና/መደኒ ቀበሌዎች ሲሆኑ በጥቅሉ በስራቸው የሚቋቋሙ 30 የምርጫ ጣቢያዎች መሆናቸውን አስታውቋል።
በዚህም መሰረት በአካባቢው የሚኖሩ፣የመራጮች ምዝገባና የድምጽ መስጠት ሂደት ውስጥ የሚሳተፉ ዜጎች በአቅራቢያቸው ባለ ሌላ ቀበሌ መመዝገብና ድምጻቸውን መስጠት የሚችሉ እንደሆነ ያስታወቀው ቦርዱ ፤ ይህንንም ተግባራዊ እንዲያደርጉ ለምርጫ አስፈጻሚዎቹ ተገቢውን መመሪያ እንደሚያስተላልፍ ገልጿል።
“ይህ ውሳኔ የምርጫ ሰላምን ቅድሚያ በመስጠት በቦርዱ የተወሰነ ሲሆን የመራጮችን የመምረጥ መብት በማይገድብ መልኩ እንዲፈጸም ያደርጋል። በዚህ አጋጣሚም ቦርዱ ሌሎች አካላት የምርጫ ኦፕሬሽንን የምርጫ ጣቢያዎችና የምርጫ ክልል ቢሮዎቸን አከፋፈት ለቆዩ የአስተዳደራዊ ወሰን ውዝግቦች ግብአት ከመጠቀም ሊቆጠቡ ይገባል” ሲል አሳስቧል።