የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ማክሰኞ መጋቢት 28 ቀን 2013 ዓ.ም. ባወጣው ሪፖርት፣ የኢትዮጵያ መንግሥትና የፀጥታ ኃይሎች በኢትዮጵያውያን ላይ ከፍተኛ የሰብዓዊና የፖለቲካ መብቶች ጥሰት ፈጽመዋል አለ።
በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ይፋ የተደረገው ሪፖርት፣ የኢትዮጵያ መንግሥትና የፀጥታ ኃይሎች ሕጋዊ ያልሆነ ግድያ በተለያዩ አካባቢዎች ፈጽመዋል ያለ ሲሆን፣ ለዚህም የተለያዩ የውጭ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማትንና በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ሪፖርቶችን ዋቢ አድርጓል።
ከተፈጸሙት ሕገወጥ ግድያዎች በተጨማሪ በሕግ የተከለከሉ የጭካኔና ማሰቃየት ተግባራት፣ እንዲሁም የአስገድዶ መድፈር ወንጀሎች በፀጥታ ኃይሎች በትግራይ ክልልና በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች መፈጸማቸውን በሪፖርቱ አመልክቷል።
የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በፖለቲካ እንቅስቃሴያቸው ሊሆን በሚችል ምክንያት በወንጀል መታሰራቸውን፣ ሐሳብን የመግለጽና የሚዲያ ነፃነት በከፍተኛ ደረጃ መጣበቡንና ጋዜጠኞች መታሰራቸውንም ሪፖርቱ ያብራራል።
ከፍተኛ የሆነ ሙስና በመንግሥት ተቋማት እየተፈጸመ መሆኑንም ሪፖርቱ ያመለክታል።
የአሜሪካ መንግሥት ያወጣውን ሰፊ ሪፖርት በተመለከተ ሪፖርተር ለኅትመት እስከገባበት ሰዓት ድረስ በኢትዮጵያ መንግሥት በኩል የተሰጠ ምላሽ የለም።