Sunday, April 2, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ስፖርትየአሠልጣኝ ውበቱ ዕቅድና የዋሊያዎቹ ስኬት

የአሠልጣኝ ውበቱ ዕቅድና የዋሊያዎቹ ስኬት

ቀን:

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋሊያዎቹ) ዋና አሠልጣኝ ውበቱ አባተ፣ ያሳኩት ውጤት በዕቅድና በሥራ የተገኘ ነው ሲሉ ከትናንት በስቲያ ሰኞ መጋቢት 27 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አብራርተዋል፡፡

ጋዜጣዊ መግለጫው በዋናነት አሠልጣኙ ብሔራዊ ቡድኑን በኃላፊነት ከተረከቡ በኋላ ያደረጓቸውን የመጨረሻዎቹን ሁለት ጨዋታዎችና ቀደም ሲል በሰበታ ከነማ እግር ኳስ ክለብ በነበሩበት ወቅት የነበራቸውን የውል ስምምነት የተመለከተ ነበር፡፡

ከቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሠልጣኝ ኢንስትራክተር አብርሃም መብርሃቱ ምትክ በ2012 የውድድር ዓመት መጨረሻ ዋሊያዎቹን የተረከቡት አሠልጣኝ ውበቱ አባተ፣ ኢትዮጵያ ከስምንት ዓመት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ የበቃችበትን ውጤት አሳክተዋል፡፡ አንዳንዶች የኢትዮጵያ ቡድን ለዚህ ስኬት የበቃበትን መንገድ ከዕድል ጋር የሚያያይዙት ቢኖሩም፣ አሠልጣኝ ውበቱ በዚህ አይስማሙም፡፡ ለዚህም የቡድኑን ኃላፊነት ተረክበው መደበኛ ዝግጅት ከመጀመራቸው በፊት ከተጫዋቾቻቸው ጋር ያቀዷቸውን ዕቅዶችና ውይይቶች ተመልክቶ እውነታውን መረዳት እንደሚቻል ጭምር ነው በመግለጫቸው ያብራሩት፡፡

አሠልጣኙ ለመጀመሪያዎቹ የቡድናቸው ስብስብ ‹‹እመኑኝ ለካሜሩን የአፍሪካ ዋንጫ እንበቃለን፤›› ብለው እንደነገሯቸው፣ ይህ ደግሞ በምኞት ብቻ ሳይሆን ሊተገበሩ የሚችሉ ዕቅዶች አቅደው መሥራት በመቻላቸው እንደሆነም አስረድተዋል፡፡

አሠልጣኝ ውበቱ ብሔራዊ ቡድኑን ለማሠልጠን ኃላፊነቱን የተረከቡት፣ የቀድሞ አሠልጣኝ ኢንስትራክተር አብርሃም ብሔራዊ ቡድኑን ይዘውና በምድቡ ከጠንካራዋ አይቮሪኮስት ጋር በባህር ዳር ስታዲየም ተጫውተው 2ለ1 በሆነ ውጤት የረቱበት ወቅት መሆኑ የበረታ ተቃውሞ በሚደመጥበት ወቅት እንደነበር ይታወሳል፡፡

ለአሠልጣኝ ውበቱ ሌላው የተነሳላቸው ጥያቄ፣ ዓምና ከፋሲል ከነማ ጋር የነበረው ውል እንደተጠናቀቀ ሰበታ ከነማን ለማሠልጠን የሁለት ዓመት ኮንትራት የተፈራረሙበት ጊዜ እንደመሆኑ መጠን ከክለቡ ጋር የተለያዩበት ሁኔታና የሕግ አካሄድ ምን እንደሚመስል የተመለከተ ነበር፡፡

አሠልጣኙ ብሔራዊ ቡድኑን ለማሠልጠን ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሁለት ዓመት ኮንትራት ሲቀበሉ፣ በክለቡ ያልሠሩበትን የአንድ ዓመት የፊርማ ክፍያ ለክለቡ እንደመለሱ፣ ሆኖም ግን ከክለቡ ሊከፈላቸው የነበረውን ክፍያ በተመለከተ ግን ከፌዴሬሽኑ እንደሚያገኙ ቃል እንደተገባላቸው አውስተዋል፡፡

ከአሠልጣኝ ውበቱ አባተ ጋር በጋዜጣዊ መግለጫው ለተገኙት የብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን ከብሔራዊ ቡድኑ ቀጣይ ጉዞና ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ለተነሱ ጥያቄዎች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በካሜሩን አስተናጋጅነት ለመጀመሪያ ጊዜ 24 ቡድኖችን ለሚያሳትፈው የአፍሪካ ዋንጫ አስተናጋጇ ካሜሩን፣ ኢትዮጵያ፣ አልጀሪያ፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ኬፕቨርዴ፣ ኮሞሮስ፣ አይቮሪኮስት፣ ግብፅ፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ ጋቦን፣ ጋምቢያ፣ ጋና፣ ጊኒ፣ ጊኒ ቢሳዋ፣ ማላዊ፣ ማሊ፣ ሞሪታኒያ፣ ሞሮኮ፣ ናይጀሪያ፣ ሴኔጋል፣ ሱዳን፣ ቱኒዚያ፣ ዚምባቡዌና ቤኒን ተሳታፊዎች ይሆናሉ፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ኦቲዝምን ለመቋቋም በጥምረት የቆሙት ማዕከላት

ከኦቲዝም ጋር የሚወለዱ ልጆች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ...

አወዛጋቢው የወልቃይት ጉዳይ

የአማራና ትግራይ ክልሎችን እያወዛገበ ያለው የወልቃይት ጉዳይ ዳግም እየተነሳ...

ተጠባቂው የቴሌኮም ኦፕሬተሮች የውድድር መለኪያ የሆነው የሞባይል ገንዘብ ዝውውር በኢትዮጵያ

የሞባይል ገንዘብ ዝውውር የሞባይል ስልክን በመጠቀም ሊገኙ የሚችሉ የፋይናንስ...

የአማራና ደቡብ ክልሎች ለሠራተኛ ደመወዝ መክፈል መቸገራቸውን የፓርላማ አባላት ተናገሩ

በአማራና በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልሎች የሚገኙ የመንግሥት ተቋማት...