Monday, March 20, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

[ክቡር ሚኒስትሩ ከህዳሴ ግድቡ ተደራዳሪ ቡድን አባላት የቡድን መሪ ጋር ግብፅ ስላነሳችው አዲስ ክርክር እየተወያዩ ነው]

  • እስኪ ካቆምክበት ሐሳብ ጀምርልኝ፡፡ የሰሞኑ ድርድር አዲስ ጉዳይ ምን ነበር?
  • ክቡር ሚኒስትር ለድርድር ብንቀመጥም በዋና ጉዳይ ላይ መወያየት አልቻልንም።
  • ለምን?
  • በግብፅ በኩል አዲስ የክርክር አጀንዳ ተመዟል፡፡
  • ከዚህ ቀደም ያልነበረ ነው?
  • አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡ 
  • አዲሱ ክርክር ምንድነው?
  • ድርሻዬ መነካት የለበትም ነው የምትለው።
  • ግብፅ ነች?
  • አዎ። 
  • የከረምንበት ክርክር አይደለም እንዴ ምኑ ነው አዲስ?
  • አዲስ የድርሻ ጥያቄ ነው የተነሳው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • የምን ድርሻ?
  • የደመና ድርሻ፡፡
  • ምን?
  • በኢትዮጵያ ላይ የደመና ድርሻ አለኝ እያለች ነው።
  • ወይ ግብፅ? እና ምን ይሁን አለች?
  • ስምምነት ሳይደረስ መጀመር የለበትም።
  • ምኑ?
  • ደመና ማዝነቡ።
  • እናንተ ምን ምላሽ ሰጣችሁ?
  • ስለደመና ለመደራደር ሥልጣን እንዳልተሰጠን አሳውቀናል፡፡
  • ሥልጣን ቢሰጣችሁስ? 
  • እንደማይሰጠን እናውቃለን ክቡር ሚኒስትር፡፡ 
  • ለምን?
  • በበላይ አካልጥብቅ የተያዘ መሆኑን እናውቃለን።
  • ሌላ ያነሱት ነገር አለ?
  • ግብፆች ካዳመጧቸው የማያነሱት ነገር የለም፡፡
  • ምን አነሱ?
  • በእረፍት ሰዓት ከደመና ማዝነቡ ጋር በተያያዘ ሲጠይቁን ነበር፡፡
  • ምን አሉ?
  • ደመና እንድታዘንቡ ብንስማማ እንኳን እንዲቀላቀል አንፈቅድላችሁም ይላሉ።
  • ምኑ ከምን እንዳይቀላቀል?
  • የደመናው ዝናብ ከዓባይ ወንዝ ጋር።
  • ለምን?
  • የዓባይ ድርሻችንን ለመለየት እንቸገራለን ነው የሚሉት፡፡
  • ወይ ግብፅ. . .  
  • አንዳንዶቹ ደግሞ የዓባይ ወንዝን የምናውቀው ብቻውን ነው፡፡ ከሰው ሠራሽ ደመና ዝናብ እንዲቀላቀል አንፈልግም ይላሉ።
  • ከሰው ከሠራሽ ደመና አንፈልግም አሉ?
  • አዎ። 
  • ምን ይሁን ይላሉ?
  • ኦርጋኒክ ደመና፡፡
  • ደመና ማዝነቡን ወደፊት ብንሞክረው ሳይሻል አይቀርም?
  • ይኼማ መንበርከክ ነው ክቡር ሚኒስትር. . . መሆን የለበትም፡፡
  • እኔ ከግብፅም ሆነ ከማንም ጋር አታካራ ውስጥ መግባት አልፈልግም፣ ሰላም ነው የምፈልገው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ይህንን እንዳይወስኑ፡፡
  • ነገርኩህ እኮ ሰላም ነው የምፈልገው። ደመና ማዝነቡን ወደፊት እንደርስበታለን።
  • ክቡር ሚኒስትር ሕዝቡ ምን ይለናል? 
  • ሕዝቡ ያለንበትን ሁኔታ ይረዳል። 
  • እሺ ሕዝቡ ተረዳን እንበል፣ ፓርላማውስ ምን ይለናል?
  • ፓርላማው ምንም አይለንም፡፡
  • እንዴት?
  • ባልፈቀደልን በጀት ሊቆጣጠረን አይችልም፡፡
  • ለነገሩ እሱስ ባልፈቀደው በጀት ምን ብሎ ይጠይቃል ልክ ነዎት!

[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ቢሯቸው እንደገቡ አጀንዳቸውን ተመልክተው ለዕለቱ ቀጠሮ የተያዘላቸው አንድ የሚዲያ ባለሙያ እንዲገባ አዘዙ]

  • ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡ 
  • እንደምን አለህ? እስኪ አረፍ በል፡፡ 
  • ክቡር ሚኒስትር ለሚዲያ ዘርፉ ዕድገት ባለዎት ቀና አመለካከትና ከእኛ ጋር ለመወያየት ቢሮዎ ዘወትር ክፍት መሆኑን አደንቃለሁ። 
  • ለአገራችንና ለሕዝባችን ዴሞክራሲ አስፈላጊ በመሆኑ ነው ዘርፉን የምንደግፈው። 
  • ዛሬ የመጣሁት ግን ቅሬታ ለማቅረብ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን ገጠመህ?
  • በግሌ ደህና ነኝ፣ ለዘርፉ ዕድገት ትርጉም ያለው አስተዋጽኦ ይኖረዋል ያልነው የሕግ ማሻሻያ በፓርላማ ቢፀድቅም እስካሁን ወደ ሥራ አለመግባቱ አሳስቦናል።
  • ምን አሳሰባችሁ?
  • ክቡር ሚኒስትር ሕጉ ወደ ሥራ ያልገባው በመንግሥት በኩል የአቋም መንሸራተት በመኖሩ ነው የሚሉ መረጃዎች እየደረሱን በመሆኑ ነው ሥጋት የጫረብን። 
  •  ሃሃሃ. . . ሥጋት አይግባችሁ፣ ሕጉ በነጋሪት ጋዜጣ ኅትመት ላይ እያለ መጠነኛ ችግር ስለገጠመን ነው የዘገየው። 
  • ነጋሪት ጋዜጣ ላይም ተበላሽቶ እንዳይሆን?
  • ምኑ?
  • የኅትመት ማሽኑ፣ የኅትመት ሚዲያዎችን ያሰቃየው አንዱ ችግር አንድ ለእናቱ የምንለው የኅትመት ማሽን በተደጋጋሚ መበላሸት ነው።
  • አይ እንደዚያ እንኳን አይደለም።
  • እሱ ካልሆነ ወረቀት ወይም ቀለም አልቆ ነው የሚሆነው፡፡
  • አይደለም ስልህ። 
  • ታዲያ ምን ተፈጥሮ ነው?
  • ኅትመቱ እንዲዘገይ ታዞ ነው። 
  • ለምን ክቡር ሚኒስትር? 
  • አዋጁ በነጋሪት ታትሞ ከመውጣቱ በፊት ሹመቶች ለመስጠት ታስቦ ነው።
  • ሹመት?
  • አዎ፣ ከአዋጁ በፊት የሚዲያ ዘርፉን ለሚቆጣጠረው መሥሪያ ቤት ባለሥልጣናትን ለመሾም ነው።
  • ምን? 
  • ምነው ደነገጥክ?
  • እንዴት ይሆናል ይኼ ክቡር ሚኒስትር? መሆን የለበትም፡፡
  • ለምን? 
  • የሕግ ማሻሻያው ተስፋ የሰጠን አንዱ ጉዳይ እኮ ነው። 
  • የምን ተስፋ?
  • ለባለሥልጣኑ የሚሾሙ ኃላፊዎች በገለልተኛ ቦርድ ታጭተው መቅረብ እንዳለባቸው ነው ፓርላማው ያፀደቀው ሕግ የሚደነግገው።
  • አዎ ልክ ነህ። 
  • ታዲያ የአዋጁ ኅትመት እንዲቆም ተደርጎ ከሕጉ ውጪ ባለሥልጣን መሾም ትክክል ነው ክቡር ሚኒስትር? እንዴት ይሆናል?
  • ግዴለህም ተረጋጋ. . . የሳትከው ነገር አለ፡፡
  • ምንም የሳትኩት የለም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ይኸውልህ አዋጁ ፀደቀ እንጂ ተፈጻሚ አልሆነም።
  • . . .
  • አድምጠኝ! አዋጁ ተፈጻሚ መሆን የሚጀምረው መቼ እንደሆነ አልተገነዘብክም።
  • እንዴት?
  • አዋጁ ተፈጻሚ የሚሆነው በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ይፋ ከተደረገበት ቀን አንስቶ እንደሆነ በአዋጁ የመጨረሻ አንቀጽ አልተደነገገም?
  • እውነት ነው ተደንግጓል፡፡
  • ታዲያ በነጋሪት ታትሞ ከመውጣቱ በፊት ሹመት መስጠት ምን ችግር አለው?
  • የሆነው እንደዚያ አይደለማ?
  • ምንድነው የሆነው?
  • የነጋሪት ጋዜጣው ኅትመት ቆሞ ሹመቱ ተካሄደ። 
  • ያው ነው። 
  • እንዴት ያው ይሆናል?
  • አዋጁ ካልታተመ ተፈጻሚ አይሆንም፡፡
  • የተሾሙት ኃላፊዎች እንዴት ናቸው? ልምድ አላቸው ክቡር ሚኒስትር?
  • ስለሱ አታስብ። ዋና ዳይሬክተሩመረጃ መረብ ደኅንነት ባልደረባ የነበሩና ጥሩ ልምድ ያላቸው ናቸው፡፡
  • ከመረጃ መረብ ደኅንነት ነው ያሉኝ?
  • አዎ። 
  • ጉድ ፈላ በሉኛ?
  • ምን አልክ?
  • አለቀልን፡፡
  • ሌላው ያልነገርኩህ. . .
  • ምን?
  • የነጋሪት ጋዜጣው ኅትመትም እንዲፋጠን ተወስኗል፡፡
  • ምን ዋጋ አለው አሁን። ከተበላሸ…
  • ምኑ?
  • ማሽኑ! 

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

ብልጽግና ፈተና ሆነውብኛል ያላቸውን አምስት ተግዳሮቶች ይፋ አድርጎ የአግዙኝ ጥሪ አቀረበ

ብልፅግና በነፃነት ስም በሚፈጸም ወንጀል ምክንያት በትግሉ ያገኘውን ነፃነት...

ዋሊያዎቹ ሁለት ሚሊዮን ብር ተሸለሙ

ለአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ በምድብ 11 ከአይቮሪኮስት፣ ማዳጋስካርና ኒጀር ጋር የተደለደለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋሊያዎቹ) ሁለት ሚሊዮን ብር የገንዘብ ሽልማት ተበረከተለት፡፡

መንግሥት ከጦርነቱ ለማገገም በመጭዎቹ አምስት ዓመታት 20 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል አለ

በጦርነቱ የተሳተፉ 250 ሺሕ ተዋጊዎችን መልሶ ለማቋቋምና ወደ ኅብረተሰቡ...

ዜጎች የተፈተኑበት የኑሮ ውድነት

በኢትዮጵያ በየጊዜው እየተባባሰ የመጣው የኑሮ ውድነት የበርካታ ዜጎችን አቅም...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

ዜጎች የተፈተኑበት የኑሮ ውድነት

በኢትዮጵያ በየጊዜው እየተባባሰ የመጣው የኑሮ ውድነት የበርካታ ዜጎችን አቅም...

በድርቅ ለተጎዱ አካባቢዎች የሚደረጉ ድጋፎች ዘላቂነት እንዲኖራቸው ተጠየቀ

በድርቅ ለተጎዱ አካባቢዎች የሚደረጉ ድጋፎች ዘላቂነት እንዲኖራቸውና በተቀናጀ መልኩ...

ወደ ኋላ የቀረው የሠራተኞች ደኅንነት አጠባበቅ

በአበበ ፍቅር ለሠራተኞች የሚሰጠው የደኅንነት ትኩረት አናሳ በመሆኑ በርካታ ዜጎች...

ቲቢና ሥጋ ደዌን ለመከላከል ያለመ ስትራቴጂክ ዕቅድ

ኢትዮጵያ የቲቢ፣ ሥጋ ደዌና ሌሎች የሳንባ በሽታዎች ጫና ካለባቸው...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[የባለሥልጣኑ ኃላፊ የቴሌኮም ኩባንያዎች የስልክ ቀፎ የመሸጥ ፈቃድ እንዳላቸው ለማረጋገጥ ክቡር ሚኒስትሩ ጋር ደወሉ]

ክቡር ሚኒስትር ዕርምጃ ከመውሰዳችን በፊት አንድ ነገር ለማጣራት ብዬ ነው የደወልኩት። እሺ ምንን በተመለከተ ነው? የቴሌኮም ኩባንያዎችን በተመለከተ ነው። የቴሌኮም ኩባንያዎች ምን? የቴሌኮም ኩባንያዎች የሞባይል ቀፎ እንዲሸጡ በሕግ...

[ክቡር ሚኒስትሩ ተቋቋመ ስለተባለው የሽግግር መንግሥት ከአማካሪያቸው መረጃ እየጠየቁ ነው]

እኛ ሳንፈቅድ እንዴት ሊያቋቁሙ ቻሉ? ስምምነታችን እንደዚያ ነው እንዴ? በስምምነታችን መሠረትማ እኛ ሳንፈቅድ መቋቋም አይችልም። የእኛ ተወካዮችም በአባልነት መካተት አለባቸው። ታዲያ ምን እያደረገ ነው? ስምምነቱን መጣሳቸው...

[የክልሉ ከፍተኛ ባለሥልጣን በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ለመመካከር በሚኒስትሩ ቢሮ ተገኝተው ውይይታቸውን ጀምረዋል]

ክቡር ሚኒስትር ባላንጣዎቻችን የእኛኑ ስልት መጠቀም የጀመሩ ይመስላል። እንዴት? ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ? እስከዛሬ እኛ የምንሰጣቸውን አጀንዳ ተቀባይ ነበሩ። በዚህም በውስጣቸው ልዩነትንና አለመግባባትን መትከል ችለን ነበር። አሁን...