Sunday, March 26, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናአብን ኢቲቪ ካዘጋጀው የምርጫ ክርክር ራሱን አገለለ

አብን ኢቲቪ ካዘጋጀው የምርጫ ክርክር ራሱን አገለለ

ቀን:

የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ‹‹አማራን  መሠረት ያደረገ  ግድያ በቀጠለበት በዚህ ወቅት በክርክር ላይ ለመሳተፍ አልችልም›› በማለት፣ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን (ኢቲቪ) ከተዘጋጀው የምርጫ የክርክር መድረክ ራሱን እንዳገለለ አስታወቀ፡፡

በግንቦት ወር ለሚከሄደው አገር አቀፍ ምርጫ  የፖለቲካ ፖርቲዎች በቴሌቪዥን የሚያካሂዱት የምርጫ ክርክር ከተጀመረ ሁለተኛ ሳምንቱን ይዟል፡፡

ማክሰኞ ሚያዚያ 12 ቀን 2013 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በነበረው የምርጫ ክርክር ሊሳተፉ የነበሩት፣ የፓርቲው ምክትል ሊቀመንበር አቶ የሱፍ ኢብራሂምና የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው አቶ ጣሂር መሐመድ፣ ‹‹በአማራ ወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለው ጅምላ ፍጅትና ሰቆቃ ተጠናክሮ በቀጠለበት በዚህ ወቅት በክርክርደቱ ላይ ለመሳተፍ እንደማይቻላቸው በመግለጽ፣ መድረኩን ረግጠው ወጥተዋል፤›› ሲል አብን በመግለጫው አስታውቋል፡፡

በክርክር መርሐ ግብሩ ላይ ተከራካሪዎቹ የፌዴራል ሥርዓቱ መነሻ ሕገ መንግሥቱ መሆኑን በመጥቀስ፣ ይህ ሰነድ ደግሞ የኦሮሞ ነፃነት ግንበር (ኦነግ) እና የሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ውል እንጅ የኢትዮጵያ ሕዝብ ባለመሆኑና ብዝኃነትን ስለማያስተናግድ ወኪሎቹ ከክርክሩ መውጣታቸውን አክሎ ገልጿል፡፡

‹‹አሁን ያለው ሥርዓት በትርክትና በመዋቅር ረገድ ካለፈው የተለየና ብቸኛው ለውጥ የማጥቂያ ሥልቱ ብቻ እንደሆነ፣ በዚህም የአማራ ሕዝብ የዘር ማጥፋት ወንጀል እየተፈጸመበት መሆኑን›› መድረኩ ላይ መግጻቸውን አብን አስታውቋል፡፡

‹‹የሕዝባችን ደም በከንቱ እየፈሰሰ በመሆኑ የተቀናጀ የተቃውሞና ራስን የመከላከል ትግል ውስጥ እንደገባ፣ አብንም የዚሁ አካል በመሆኑ፣ እንዲሁም እዚህ በመቆየት የሕዝቡን ትግል ማሳነስ እንደማይፈልግ›› በመግለጽ፣ የህሊና ፀሎት እንዲደረግ ጠይቆ ከመድረኩ መውጣቱን በመግለጫው አትቷል፡፡

በአማራ ክልል በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታና ግድም ወረዳ በአጣዬ ከተማና አካባቢው ሚያዝያ 8 ቀን 2013 ዓ.ም. ታጣቂዎች በሰነዘሩት ጥቃት በርካታ ንፁኃን ዜጎች መሞታቸው፣ በርካቶች መፈናቀላቸውና ንብረት መውደሙ ይታወሳል፡፡

ጉዳዩን አስመልክቶ አብን ሚያዝያ 10 ቀን 2013 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ ‹‹መንግሥታዊ ሽብሩን በማባባስ፣ በመደገፍና ትዕዛዝ በመስጠት ጭምር የሚሳተፉት የአገራችን ጠቅላይ ሚንስትርና የሚመሩት የኦሮሞ ብልፅግና ክፍል መንግሥታዊ መዋቅርንና የአገር ሀብትን በመጠቀም የአማራን ሕዝብ የማሸበር ተግባር አጠናክረው ቀጥለዋል፤›› ሲል ወቀሳውን ሰንዝሯል፡፡

በተመሳሳይ ፓርቲው በመግለጫው፣ በአማራ ሕዝብ ላይ እየተፈጸመ ያለውን ተደጋጋሚ የዘር ጥቃት ማስቆም ይቅርና ጅምላ ፍጅቱ በአገር ደረጃ ለሐዘን መግለጫ እንኳ እንዳይበቃ የተደረገ ከመሆኑም በላይ፣ ‹‹በሐዘን ድንኳናችን ላይ ቀይ ምንጣፍ አንጥፈው ሕንፃና አበባ የሚመርቁበት አስደንጋጭ ማኅበራዊ ስላቅ ሳይቋረጥ ቀጥሏል፤›› ብሏል፡፡

በዚህም በአማራ ሕዝብ ላይ የተከፈተው ዘር ተኮር ጥቃት የታቀደና የተቀናጀ እንደሆነና የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጭምር፣ ‹‹የዘር ማጥፍት ወንጀል ለማስፈጸም አመላካች የሆኑ የመግቢያ ንግግሮችን በይፋ ሲያሰሙ መቆይታቸውና ለዚህም ምንም ዓይነት አስተዳደራዊም ይሁን ፖለቲካዊ ዕርምት አለመሰጠቱ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩና የሚመሩት መንግሥት በዚህ የአማራን ሕዝብ የማሸበርና የዘር ፍጅት እንቅስቃሴ ውስጥ ሚና አላቸው ብሎ ንቅናቄያችን ለማመን ተገዷል፤›› ሲል ፓርቲው አስታውቋል፡፡

አብን ሰኞ ሚያዚያ 11 ቀን 2013 ዓ.ም.  ባወጣው በሌላኛ መግለጫው፣ በአጠቃላይ በአማራ ሕዝብ ላይ ባለማቋረጥ የሚፈጸሙት መንግሥት መራሽ የዘር ፍጅቶች፣ በገለልተኛ ኮሚሽን በጥልቀት ተጣርተው በቀጥታ በጥቃት ውስጥ የተሳተፉ፣ ኃላፊነታቸውን ያልተወጡ፣ መንግሥታዊ መዋቅርን ለጥቃት ማስፈጸሚያነት ያዋሉ፣ ያስተባበሩና የተመሳጠሩት አካላት ማንነት ለሕዝብ በይፋ እንዲገለጽና ተጠያቂ እንዲሆኑ ሲል ጠይቋል፡፡

በዚህም በአማራ ሕዝብ ላይ ለተፈጸሙት ተደጋጋሚ የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ብሔራዊ ዕውቅና እንዲሰጥ፣ እንዲሁም ብሔራዊ ይቅርታ እንዲጠየቅና በተለያዩ አካባቢዎች በአማራ ሕዝብ ላይ ያንዣበቡ ዘር ተኮር ጥቃቶች ፍፁም የማይደገሙ ስለመሆናቸው የማያወላዳ ማረጋገጫና የደኅንነት ዋስትና በይፋ እንዲሰጥ ጠይቋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...