ከምርጫው በፊት ለብሔራዊ መግባባት ጉዳይ ቅድሚያ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርቧል
በትግራይ ክልል የተፈጠረው ሰብዓዊ ቀውስና ግጭት እንዲያበቃና በክልሉ የሚገኘውን የኤርትራ ሠራዊት ለማስወጣት የገባውን ቃል፣ የኢትዮጵያ መንግሥት በፍጥነት የማይፈጽም ከሆነ፣ ሊወሰድ የሚችለውን ዕርምጃ አስመልክቶ፣ የአባል አገሮች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በቅርቡ እንደሚመክሩበት የአውሮፓ ኅብረት አስታወቀ።
ይህንን የተናገሩት የኅብረቱ ምክትል ፕሬዚዳንትና የውጭ ግንኙነት ኃላፊው ጆሴፕ ቦሬል ናቸው።
የኅብረቱ የውጭ ግንኙነት ምክር ቤት አባል የሆኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ሰኞ ሚያዚያ 11 ቀን 2013 ዓ.ም. በበይነ መረብ አማካይነት የተወያዩ ሲሆን፣ በዚህ ውይይትም በቅርቡ በትግራይ ያለውን ሁኔታ በአካል ተገኝተው እንዲታዘቡ የተወከሉት የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፔካ ሀቢስቶ ሪፖርት ማቅረባቸውን የኅብረቱ መግለጫ ያመለክታል።
የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በዋናነት የተሰጣቸው ተልዕኮ በኢትዮጵያ የትግራይ ክልል ቀውስን መገምገም ሲሆን፣ ከዚሁ ጋር በተገናኘም የኢትዮጵያ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታንም እንዲቃኙ ኃላፊነት ተስጥቷቸው ነበር።
በዚህም መሠረት ወደ ኢትዮጵያ ከመድረሳቸው አስቀድሞ በግብፅ፣ በተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስና ባሳዑዲ ዓረቢያ ተገኝተው ከአገሮቹ መሪዎች ጋር ተወያይተዋል።
በመቀጠልም በኢትዮጵያ ባደረጉት ጉብኝት ከፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ጋር፣ ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ እንዲሁም በትግራይ ክልል በመገኘት ከክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ኃላፊዎች ጋር ምክክር ያደረጉ ሲሆን፣ በክልሉ ያለውን ሁኔታ በመዘዋወር ቃኝተው ተመልሰዋል።
ወደ አገራቸው ከተመለሱ በኋላም ሰኞ ዕለት ጉብኝታቸውን የተመለከተ ሪፖርት ለአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ምክር ቤት ማቅረባቸው ታውቋል።
በሪፖርታቸውም በትግራይ ክልል አሁንም ግጭቱ መቀጠሉንና የሰብዓዊ ዕርዳታ ለማቅረብ ያልተገደበ እንቅስቃሴ ማድረግ የሚያስችል ሁኔታ በክልሉ አለመስፈኑን፣ የኤርትራ ወታደሮችም ከክልሉ አለመውጣታቸውን ገልጸዋል።
ይህንንም ተከትሎ የኅብረቱ አባል አገሮች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ባደረጉት ውይይት፣ በትግራይ ክልል ያለውን ችግር ለመፍታት ቁጥጥር የሚደረግበት የተኩስ ማቆም አስፈላጊነትን፣ የጦር ወንጀልን፣ ፆታዊ ጥቃቶችንና ኢሰብዓዊ ጥሰቶችን የተመለከተ ገለልተኛ ምርመራ መከናወን እንዳለበት፣ እንዲሁም አስቸኳይ የሰብዓዊ ዕርዳታ አቅርቦት መድረስ እንደሚገባው ትኩረት አድርገው መወያየታቸውን መግለጫው ያመለክታል።
ከዚህም በተጨማሪ በኢትዮጵያ በቅርቡ የሚካሄደው አጠቃላይ ምርጫን በተመለከተ መወያየታቸው ታውቋል።
ውይይቱን ተከትሎ ጆሴፕ ቦሬል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የኅብረቱ የውጭ ግንኘነት ምክር ቤት ያደረገው አስቸኳይ ስብሰባ በመሆኑ፣ ውይይቱ በበይነ መረብ አማካይነት መካሄዱን ጠቅሰው፣ ምክር ቤቱ በቀናት ውስጥ በአካል ተገናኝቶ በዚሁ ጉዳይ ላይ በስፋት እንደሚመክር ገልጸዋል።
በቀጣይ የሚካሄደው ውይይት ትክረት ከሚያደርጉባቸው ጉዳዮች መካከል የኢትዮጵያ መንግሥት በገባው ቃል መሠረት በትግራይ ያለውን ቀውስ የማይፈታ ከሆነ፣ የአውሮፓ ኅብረት የሚወስደው ዕርምጃን የተመለከተ ውይይት እንደሚደረግ ተናግረዋል።
በተጨማሪም በቅርቡ ከሚካሄደው ምርጫ አስቀድሞ የኢትዮጵያ መንግሥት ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር የሚያሰችል ውይይት ለማድረግ ቁርጠኛ መሆን እንዳለበት በኅብረቱ አቋም መያዙን አስረድተዋል፡፡
ኅብረቱ በመጪዎቹ ጥቂት ቀናት ውስጥ በሚያደርገው ወይይት በኢትዮጵያ የሚካሄደው ምርጫ ተጨማሪ የውይይት ነጥብ እንደሚሆን፣ ኅብረቱም የምርጫ ታዛቢ ቡድን ለመላክ ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ገልጸዋል።
የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በኢትዮጵያ የነበራቸውን ቆይታ ለማጠቃለል ከአቶ ደመቀ መኮንን ጋር ውይይት ባደረጉት ወቅት፣ ሰብዓዊ ዕርዳታ ለሚያቀርቡ ድርጅቶች በትግራይ ክልል ለመንቀሳቀስ የተሻሻለ ሁኔታ መፈጠሩን እንደገለጹላቸው፣ መጪው የክረምት ወቅት ከመግባቱ አስቀድሞ በክልሉ የተፈናቀሉ ነዋሪዎችን የተሻለ መጠለያ እንዲያገኙ የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ ወደ ትግበራ ለመግባት ዝግጅት መጀመሩን፣ ከክልሉ አስተዳደር መረዳታቸውን ለአቶ ደመቀ ገልጸውላቸው እንደነበር፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
በተጨማሪም በክልሉ የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ለማጣራት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በጋራ እንዲሰማሩ መፈቀዱን፣ የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በወቅቱ መልካም ነው ማለታቸውን መረጃው ያመለክታል።
በክልሉ የተወሰኑ አካባቢዎች ባለው ግጭት ምክንያት የሰብዓዊ ዕርዳታ ድርጅቶች ለመንቀሳቀስ በመቸገራቸው፣ ከመከላከያ ሠራዊቱ ጋር በመሆን መንግሥት በራሱ የሰብዓዊ ዕርዳታ በእነዚህ አካባቢዎች እያቀረበ እንደሚገኝ አቶ ደመቀ፣ ለፊንላንድ አቻቸው በወቅቱ ማስረዳታቸውንም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።