በኢትዮጵያ ያለውን ከፍተኛ የእናቶችና ሕፃናት ሕመምና ሞት ለማቃለል፣ በመንግሥት በኩል የሚወሰዱ የጤና ማሻሻያ ፕሮግራሞች በሳይንሳዊ ጥናት ለማገዝ የሚረዳ ‹‹ሐሴት›› የተሰኘ ፕሮግራም ሚያዝያ 12 ቀን 2013 ዓ.ም. በይፋ ሆነ፡፡
የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሌኒየም ሜዲካል ኮሌጅና ከሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመሆን ያደራጁት ሐሴት ፕሮግራም፣ በእናቶችና ሕፃናት ጤናን በተመለከተ ለፖሊስ ግብዓት ሊሆኑ የሚችሉ ምርምሮችን እንደሚያከናውን የፕሮግራሙ ዋና ዳይሬክተር ልሳኑ ታደሰ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡
በአማርኛ ‹‹ደስታ›› የሚል ፍቺ ያለውን የሐሴት ፕሮግራምን ለመተግበር በእናቶችና ሕፃናት ጤና ላይ ምርምር እያደረጉ የሚገኙ ተቋማት፣ እንዲሁም ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚገኙ ባለሙያዎች አቅማቸውን የበለጠ በማጎልበት፣ ለችግሮቹ መፍትሔ ማቅረብ የሚያስችሉ ምርምሮችን እንዲያከናውኑ ማድረግ ዓላማው እንደሆነም ተወስቷል፡፡
እንደ ዋና ዳይሬክተሩ አገላለጽ፣ ተቋሙ ችግሮችን ለመፍታት እየተተገበሩ በሚገኙ ፕሮግራሞች ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን ለማስተካከል፣ ብሎም አዳዲስ አቅጣጫ ለሚያስፈልጋቸው በጥናት የተደገፉ የመፍትሔ አቅጣጫዎችን በመንደፍ ለፖሊሲ አውጪዎች ያቀርባል፡፡
ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተመረጡ አምስት በዶክትሬት ደረጃ የሚገኙ ከፍተኛ ባለሙያዎች፣ በእናቶችና ሕፃናት ጤና ትግበራ ላይ ያሉ ማነቆዎችን በመለየት ምርምሮችን ለማከናወን፣ እንዲሁም በዚሁ ዘርፍ በፕሮግራም በአስፈጻሚነት የሚሠሩ አምስት ባለሙያዎች ቅድሚያ በሚሰጣቸው ምርምሮች ላይ ትኩረት በመስጠት እንዲሠሩ በፕሮግራሙ ታቅፈው ዝግጅት መጀመራቸው ተገልጿል፡፡
በሒደትም የምርምር ውጤታቸውን ለፖሊሲ ግብዓት ያውሉታል ያሉት ዳይሬክተሩ፣ ለፕሮግራሙ የበጀት ድጋፍ የተገኘው ከቢል ኤንድ ሚሊንዳ ጌትስ ፋውንዴሽን መሆኑንም ገልጸዋል፡፡