Sunday, March 26, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊትምህርት ሚኒስቴር ለጀርመን ኤምባሲ ትምህርት ቤት ማሳሰቢያ ሰጠ

ትምህርት ሚኒስቴር ለጀርመን ኤምባሲ ትምህርት ቤት ማሳሰቢያ ሰጠ

ቀን:

ትምህርት ሚኒስቴር የጀርመን ኤምባሲ ትምህርት ቤት ከሁለቱ አገሮች ስምምነት ውጪ የክፍያ ጭማሪ በማድረጉ ማሳሰቢያ ሰጠ፡፡

የጀርመን ኤምባሲ ትምህርት ቤት በኢትዮጵያ የሚኖሩ ጀርመናውያን፣ የጀርመን ኤምባሲ ሠራተኞችና በተለያዩ ሥራዎች የተሰማሩ ዜጎች ልጆች፣ ከዚህ በፊት በጀርመንኛ ቋንቋ ሲማሩ የነበሩ፣ እንዲሁም ከውጭ አገር የመጡና የሁለቱን አገሮች ግንኙነት ያጠናክራሉ ተብለው የተመረጡ ኢትዮጵያውያንን ሁለቱ አገሮች በ1999 ዓ.ም. ባደረጉት ስምምነት መሠረት ያስተምራል፡፡

በ1999 ዓ.ም. የቀድሞ የትምህርት ሚኒስትር ስንታየሁ ወልደ ሚካኤል (ዶ/ር) እና በወቅቱ የጀርመን አምባሳደር፣ የኢትዮጵያንና የጀርመንን ግንኙነት ያጠናክራሉ ተብለው ለሚመረጡ ተማሪዎች በቅናሽ ክፍያ ዕድሉን እንዲያገኙ ስምምነት እንዳደረጉ ሪፖርተር ያገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

ይሁን እንጂ ትምህርት ቤቱ ከሚያዝያ ወር 2013 ዓ.ም. መጨረሻ ጀምሮ በቅናሽ የትምህርት ዕድል እንዲያገኙ በተፈቀደላቸው ተማሪዎች ላይ በሙሉ ክፍያ ከሚማሩት ተማሪዎች ጋር እኩል እንዲከፍሉ በመባሉ፣ ዕድሉን አግኝተው ልጆቻቸውን በትምህርት ቤቱ የሚያስተምሩ ወላጆች ቅሬታቸውን ለትምህርት ሚኒስቴር አቅርበዋል፡፡

በዚህም የወላጆቹን ቅሬታ አስመልክቶ የትምህርት ሚኒስቴር ለጀርመን ኤምባሲ ትምህርት ቤት የላከውን የማሳሰቢያ ደብዳቤ ሪፖርተር አግኝቶ ተመልክቶታል፡፡

ለትምህርት ቤቱ የተጻፈው ደብዳቤ ሊደረግ የታሰበው የዋጋ ጭማሪ በ1999 ዓ.ም. ሁለቱ አገሮች ከተፈራረሙት ስምምነት ጋር የማይጣረስ መሆኑን ሚኒስቴሩ እስኪያረጋግጥ፣ የትምህርት ጥራት ማረጋገጥ ዘርፍ የትምህርት ቤቱ አመራሮችና ቅሬታ አቅራቢ ወላጆች ተወካዮች በተገኙበት የውይይት መድረክ እስኪፈታ ድረስ፣ የታሰበው የትምህርት ክፍያ ጭማሪ እንዲቆም የሚያሳስብ ነው፡፡

የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ሁሪያ ዓሊ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ ሚኒስቴሩ ከበርካታ ወላጆች በቃልና በጽሑፍ ቅሬታዎችን ተቀብሏል ብለዋል፡፡ የተባለውን ቅሬታ ሚኒስቴሩ ቦታው ድረስ በመሄድ እስኪመረምር ድረስ፣ የተባለው ነገር ቀድሞ ከተደረገው ስምምነት ጋር እንዳይጋጭ የማሳሰቢያ ደብዳቤ መላኩንም አረጋግጠዋል፡፡

በዚህም ትምህርት ቤቱ ያሰበው ጭማሪ ሁለቱ አገሮች ቀድሞ የተስማሙባቸውን ጉዳዮች የሚጋፋ ከሆነ፣ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ዝም ብሎ እንደማይመለከት አስታውቀዋል፡፡

ትምህርት ቤቱ ሊያደርግ ያሰበውን የዋጋ ጭማሪና የሚኒስቴሩን ማሳሰቢያ በተመለከተ አስተያየት ለማግኘት የትምህርት ቤቱን የበላይ ኃላፊዎች በኢሜል ጭምር ለማግኘት ጥረት ቢደረግም፣ ባይቻልም፣ በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር  ስቴፈን አወር ስለጉዳዩ ማብራሪያ ተጠይቀው የጀርመን ኤምባሲ የትምህርት ቤቱ ቦርድ ትምህርት ቤቱ ቀጣይነት ያለው፣ በጥራትና በግልጽ መመርያ የሚመራ፣ እንዲሁም ጤናማ የሀብት መሠረት ያለው ተቋም እንዲሆን ጠንክሮ የሚሠራ ቢሆንም፣

ትምህርት ቤቱ ለትርፍ ያልተቋቋመ በመሆኑ አስፈላጊ የሆኑ ወጪዎችን ለመሸፈን ተገቢውን ኢንቨስትመንት በማካሄድ፣ ሕጋዊ የሆነ የሀብት ክምችት ሊኖረው እንደሚገባ አምባሳደሩ ተናግረዋል፡፡

የትምህርት ቤቱ ቦርድ መዋቅራዊ ክፍተቶችን ለመሙላት፣ ብቃትን ለመጨመር፣ያልተገባ ጭማሪን ለማስቀረትና  ለረዥም ጊዜ በተመሳሳይ ዓይነት የክፍያ መጠን እንዲቆይ በማድረግ ከፍተኛ ሥራ መሥራቱን አምባሳደሩ አስረድተዋል፡፡

በአጠቃላይ በትምህርት ቤቱ 69.3 በመቶ ለሚሆኑት ተማሪዎች ቅናሽ የሆነ የትምህርት ክፍያ እንደሚያስከፍል በመግለጽ፣ በቅርቡ ትምህርት ቤቱ ለማድረግ ያሰበው የዋጋ ጭማሪ በ1999 ዓ.ም. ከተደረገው ስምምነት ጋር እንደማይጋጭም አክለዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...