የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የውኃ ሙሌትና ዓመታዊ አስተዳደርን በተመለከተ ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን ላለፉት አምስት ዓመታት ሲያደርጉት በነበረው ድርድር በበርካታ የቴክኒክ ጉዳዮች ላይ መግባባት ለመድረስ ቢያስችላቸውም፣ ድርድሩ ዛሬም በስምምነት መቋጨት አልቻለም።
ሦስቱ አገሮች በጋራ ሆነው ባካሄዷቸው ድርድሮች በቴክኒካዊ ጉዳይ ላይ ከሞላ ጎደል መግባባት እንደቻሉ ቢገልጹም፣ የድርድሩ ውጤት ሆኖ የሚቀርበው የስምምነት ሰነድ አስገዳጅ መሆን አለበት የሚለው የግብፅና የሱዳን ፍላጎትንና ከዚህ የተለየ ሐሳብ የያዘችውን ኢትዮጵያን ማቀራረብ ባለመቻሉ ውዝግቡ እንደ ቀጠለ ነው።
መሠረታዊው የልዩነት ነጥብ በድርድር የሚደረሰው ስምምነት አስገዳጅ መሆን አለበትና አስገዳጅ ሊሆን አይገባም የሚል ይሁን እንጂ፣ ይኼንን ልዩነት በማመቻመች መፍታት ካልተቻለ ሦስቱ አገሮች የተግባቡባቸውን ሌሎች ጉዳዮች በሙሉ ዜሮ የሚያደርግ ውጤት ሊያስከትል እንደሚችል፣ የኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ አስታውቋል።
ሦስቱ አገሮች በጋራ ቢመክሩበትም በአሜሪካና በዓለም ባንክ ታዛቢነት ወይም አደራዳሪነት የልዩነት ነጥቡን ዳግም ቢመለከቱትም፣ በኋላም በአፍሪካ ኅብረት አደራዳሪነት ቢሞክሩትም ፈቅ ያላለው የልዩነት ነጥብ የስምምነቱን አስገዳጅነት ጉዳይ የተመለከተ ቢመስልም፣ ጉዳዩ ግን ከህዳሴ ግድቡ ውጪ በዓባይ ውኃ ከመጠቀም የወደፊት መብት ጋር የተገናኘ በመሆኑ የተፈጠረ አለመግባባት ነው።
ይህ የልዩነት ነጥብ በኢትዮጵያና በግብፅ መካከል የተፈጠረ ቢመስልም፣ እውነታው ግን ሱዳንም ከግብፅ አቋም ጋር ወግና የቀረበችበት እንደሆነ የኢትዮጵያ መንግሥት ተደራዳሪዎች ይናገራሉ።
ከጥቂት ሳምንታት በፊት ኢትዮጵያ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት በላከችው ደብዳቤም፣ ይህንኑ የሱዳን መንግሥት አስታራቂ የሚመስል ሸንጋይ አካሄድ በግልጽ አመልክታለች።
ከህዳሴ ግድቡ የሚለቀቀው የውኃ መጠንን በተመለከተ ሦስቱ አገሮች የሚግባቡ ቢሆንም የድርቅ ወቅት፣ የተራዘመ የድርቅ ወቅት፣ እንዲሁም የተራዘመ ደረቅ ወቅት አመላካች ተብለው የተቀመጡት የውኃ መጠን መገለጫ አኃዞች የማይቀየሩ ወይም በምንም ዓይነት ሁኔታ የማይለወጡ ሆነው አስገዳጅ ስምምነት እንዲደረግባቸው፣ በግብፅ በኩል የተያዘው አቋም የልዩነቱ ምንጭ ነው።
ኢትዮጵያ የተገለጹትን የድርቅና የተራዘመ ደረቅ ወቅትን የሚያመላክቱት የውኃ መጠኖች ኢትዮጵያ ከህዳሴ ግድብ በላይ ወደፊት በምታደርገው ተጨማሪ መሠረተ ልማት ግንባታ ውኃ በመጠቀሟ የተፈጠሩ ከሆነ፣ የተገለጹት መለኪያዎች ላይ በጋራ ማሻሻያ መደረግ የሚገባው በመሆኑ ስምምነቱ መፈጸም ያለበት ይህንን ከግምት ውስጥ ባስገባ መንገድ ሊሆን እንደሚገባ ትሟገታለች።
ለዚህ የምታቀርቀበው መከራከሪያም ስምምነቱ በዚህ መንገድ ካልተፈጸመ ኢትዮጵያ በዓባይ ውኃ ላይ ወደፊት ተጨማሪ የመጠቀም መብት አይኖራትም የሚል ሲሆን፣ ይህንን ጉዳይ ከግምት ያላስገባ አስገዳጅ ስምምነት ለመፈረም እንደማትችል ፅኑ አቋም ይዛለች።
በዚህ ክርክር ላይ ኢትዮጵያና ግብፅ የሚተዋወቁ ቢሆንም፣ ልዩነቱ የቴክኒክ ጉዳይ አለመሆኑን የምትረዳው ግብፅ ለመፍትሔው ፖለቲካዊ መንገድን አማራጭ አድርጋለች። ይህንንም ለመፈጸም ከተከተለቻቸው መንገዶች አንዱ ሱዳንን ቀኝ እጅ አድርጎ መጠቀም ነው።
ሱዳን በዋናነት የግብፅን ተልዕኮ ለመፈጸም ከተከተለችው መንገድ አንዱ የሚደረሰው ስምምነት ከህዳሴ ግድቡ በላይ የሚኖረውን የኢትዮጵያን የወደፊት በውኃው የመጠቀም መብት እንደማይጣረስ ለኢትዮጵያና ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እንድታስረዳ፣ ኢትዮጵያ ማስተማመኛ ቢሰጣትም ለመስማማት ፈቃደኛ እንዳልሆነች አድርጎ በመሣል ዲፕሎማሲያዊ ጫና መፍጠር ነው።
ሪፖርተር ያነጋገራቸው አንድ የኢትዮጵያ ተደራዳሪ ቡድን አባል ሱዳን በህዳሴ ግድቡ ድርድር መሠረታዊ የልዩነት ነጥብ በሆነው ኢትዮጵያ ከግድቡ በላይ ወደፊት የሚኖራትን በውኃው የመጠቀም መብት በተመለከተ የምታራምደው አቋም ሙሉ በሙሉ ከግብፅ አቋም ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ፣ ነገር ግን ግብፅ ይህንን አቋም በተለየ ቋንቋ አድበስብሳ እንደምታቀርብ ያስረዳሉ።
ሱዳን ለዋናው የልዩነት ነጥብ አስታራቂ ይሆናል ብላ ያቀረበችው አማራጭ ሐሳብ በሦስቱ አገሮች መካከል የሚደረገው ስምምነት የኢትዮጵያን የወደፊት በውኃው የመጠቀም መብት የሚገድብ አይሆንም፣ የታችኞቹ ተፋሰስ አገሮችን ነባር ወይም አሁናዊ የመጠቀም መብትም የሚጎዳ አይሆንም የሚል የስምምነት አንቀጽ እንዲገባ የሚጠይቅ እንደሆነ ይጠቁማሉ።
ይህ አገላለጽ ከላይ ሲታይ ከህዳሴ ግድቡ በላይ ኢትዮጵያ ወደፊት የሚኖራትን መሠረተ ልማት ወይም በውኃው የመጠቀም መብት በዚህ ስምምነት ሊገደብ አይችልም የሚል እንደሚመስል፣ ነገር ግን የታችኞቹ አገሮችን ነባር የመጠቀም መብትም የሚጎዳ አይሆንም የሚል ሐሳብ አብሮ የተያያዘበት በመሆኑ በውጤቱ ከግብፅ አቋም የተለየ እንዳልሆነ ይገልጻሉ።
‹‹ይህም ማለት ሱዳን የኢትዮጵያን የወደፊት የመጠቀም መብት አትደግፍም ወይም አትቀበልም እንደ ማለት ነው። ምክንያቱም ኢትዮጵያ ከግድቡ በላይ ውኃውን ከተጠቀመች የታችኞቹ አገሮች ነባር የውኃ ድርሻ ላይ ቅናሽ ማስከተሉ አይቀርም፡፡ ስለሆነም የኢትዮጵያ የወደፊት የመጠቀም መብት የሚከበረው በታችኞቹ የተፋሰሱ አገሮች ነባር የውኃ ድርሻ ላይ ቅናሽ እስካላስከተለ ድረስ ብቻ ነው። ይህ ደግሞ ሊሆን የሚችል ነገር አይደለም፤›› ሲሉ አብራርተዋል።
በመሆኑም በሱዳን በኩል የቀረበው አማራጭ አስታራቂ ሳይሆን ግብፅና ሱዳን እ.ኤ.አ. በ1959 ያደረጉት የዓባይ ውኃ ክፍፍል እንዲከበር፣ ኢትዮጵያም ይህንን ስምምነት እንድትቀበል በሌላ ሸንጋይ የቋንቋ አጠቃቀም የቀረበ እንደሆነ ገልጸዋል።
ይህ የሁለቱ አገሮች ፍላጎት ኢትዮጵያ የምትገነባው የታላቁ ህዳሴ ግድብ በዓባይ ውኃ ላይ የመጀመርያውም የመጨረሻውም መሠረተ ልማት እንዲሆን መሆኑን፣ ኢትዮጵያ በዚህ መንገድ የተቀረፀውን ስምምነት ተቀበለች ማለት የዓባይ ውኃ ክፍልል እንዳደረገች የሚቆጠር እንደሚያደርገውም አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ተደራዳሪዎች ግን በግብፅ መንግሥት በኩል በግልጽ የቀረበውንም ሆነ፣ የግብፅን ተልዕኮ የተቀበለችው ሱዳን በሸንጋይ ቋንቋ ባቀረበችውን አስታራቂ ተብሎ የቀረበ ሐሳብ ውስጥ ያለውን አሻጥር በመረዳት፣ አሻጥሩ በተገለጸበት መንገድ ምላሽ ሰጥተዋል።
በምላሹም በግብፅና በሱዳን በኩል እየቀረበ ያለው ጥያቄ መፍትሔ ሊያገኝ የሚችለው፣ ሁሉም የዓባይ ወንዝ ተፋሰስ አገሮችን የሚያካትት አጠቃላይ የውኃ ክፍፍል ስምምነት እንዲደረግ ጥያቄ አቅርባለች። ወደዚህ ለማምራት ይረዳ ዘንድም የኢንቴቤ ስምምነት ተብሎ የሚታወቀውን የናይል ትብብር ማዕቀፍ ግብፅና ሱዳን ተቀብለው እንዲፈርሙ ጥያቄ ብታቀርብም፣ ግብፅና ሱዳን ግን በዚህ የኢትዮጵያ አማራጭ ላይ ከፍተኛ ተቃውሞ አቅርበውበታል።
ኢትዮጵያ ይህንን የግብፅን ፍላጎት ፈጽሞ የማትቀበል ከሆነ ሌላው በግብፅ መንግሥት የተያዘው አማራጭ፣ እ.ኤ.አ. በ1902 በኢትዮጵያና በግብፅ የተፈረመውን ስምምነት በመጠቀም ጉዳዩን ወደ ተመድ በመውሰድ፣ ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፍ ስምምነት አልተገዛችም የሚል ክስ በመመሥረት ፍላጎቷን ለማስፈጸም መሞከር ነው።
ይህንን የግብፅ መንገድ ለመፈጸምም ሱዳን ተልዕኮ ተቀብላ ጉዳዩን እየሄደችበት እንደሆነ የሚገልጹት እኚሁ የኢትዮጵያ ተደራዳሪ፣ ሱዳን ከግብፅ የተቀበለችውን ተልዕኮ ለመፈጸም በሰላማዊ መንገድ ድርድር እየተደረገበት የነበረውን ከኢትዮጵያ ጋር የሚያዋስናትን አወዛጋቢ ድንበር ማንም ሳይገምተው መውረሯን ይገልጻሉ።
ይህንን በማድረግ ለማስቆጠር የተፈለገው ውጤት አንድ ነው የሚሉት ባለሙያው፣ ይኸውም ኢትዮጵያና ሱዳን የሚጋሩት አወዛጋቢ ድንበር ውል የታሰረው በዚሁ ግብፅ በምታነሳው የ1902 ስምምነት ሰነድ ላይ ነው።
የ1902 ስምምነት በኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒልክና በወቅቱ ሱዳንና ግብፅን በቅኝ ግዛት ታስተዳድር በነበረችው እንግሊዝ መካከል የተፈረመ ነው።
ኢትዮጵያ በዚህ የ1902 ስምምነት ውስጥ የተጠቀሰውን የሱዳን ድንበር ጉዳይ ተቀብላ ድንበሩን ለማካለል ከሱዳን መንግሥት ጋር የድንበር ኮሚሽን በመመሥረት እየተንቀሳቀሰች የነበረ ቢሆንም፣ ጉዳዩን ከዚህ መንገድ በማውጣት ሱዳን በኃይል ድንበሮቹን ወራለች።
ይህንንም ካደረገች በኋላ በተደጋጋሚ በሱዳን መንግሥት የተሰጡት መግለጫዎች፣ ሱዳን አልፋ የወረረችው የኢትዮጵያ ድንበር እንደሌለና በ1902 ስምምነት የተወሰነላት እንደሆነ የሚገልጹ ናቸው።
እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ድረስ ያሉት የኢትዮጵያ መሪዎች በሙሉ ከሱዳን ጋር የለውን ድንበር ለመፍታት ያደረጓቸው ጥረቶች የ1902 ስምምነትን የሚጥስ ባለመሆኑ፣ ኢትዮጵያ የዚህን ስምምነት አንዱን ይዘት ተቀብላ በዚሁ የስምምነት ሰነድ አካል የሆነውን የዓባይ ውኃ አጠቃቀም በተመለከተ የተደረገውን ሌላኛው ስምምነት ለመቀበል አሻፈረኝ እንዳለች አድርጎ ጫና ለመፍጠር የተደረገ ሴራ መሆኑን ያስረዳሉ።
ኢትዮጵያ በ1902 ስምምነት የገባችው ውል የዓባይ ፍሰትን ሙሉ በሙሉ የሚገድብ መሠረተ ልማት ላለማካሄድ እንጂ ምንም ዓይነት መሠረተ ልማት ለማከናወን እንዳልሆነ የሚጠቅሱት ባለሙያው፣ ኢትዮጵያ ይህንን ስምምነት ለማፍረስ የሚያስችል መብት እንዳላትም ጠቁመዋል።
ግብፅ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ለተመድ የፀጥታ ምክር ቤት ባስገባችው ስምምነት ይህንኑ የ1902 ስምምነት በመጥቀስ፣ ኢትዮጵያ ይህንን ስምምነት የፈረመችው በቅኝ ግዛት ውስጥ ሆና ሳይሆን ነፃ መንግሥት ሆና በራሷ የፈረመችው እንደሆነ፣ በዚህ ስምምነት መሠረትም ከሌሎች ጎረቤቶቿ ጋር የተፈጠሩ ልዩነቶችን እንደፈታችበት አስታውቃለች።
የኢትዮጵያ መንግሥት የሱዳን መንግሥት አካሄድን በትዕግሥት እየተመለከተው እንደሆነ የሚታወቅ ሲሆን፣ በተደጋጋሚ ባወጣው መግለጫም የኢትዮ ሱዳን የድንበር መስመር የሁለቱም አገሮች ዜጎች ትብብር የሚያጠናክር የግንኙነት ነጥብ እንጂ፣ የመለያየት ግድግዳ ሊሆን እንደማይገባው አሳስቧል።
የድንበር ጉዳዮች በሚመለከታቸው አካላት መካከል በድርድርና በውይይት የሚፈቱት ዓለም አቀፍ ደንብና ልምዶችን በመከተል መሆን እንዳለበት፣ እንዲሁም ማንኛውም ዓይነት የአንድ ወገን እንቅስቃሴ ዘላቂ መፍትሔ ለማምጣት እንደማይረዳ አስታውቋል።
ሱዳን በአሁኑ ወቅት እያደረገች ያለችው ድርጊት ታይቶ የማይታወቅና የሌላ አካል ተልዕኮን ለመፈጸም እንጂ፣ የሱዳናዊያን ፍላጎትን ያገናዘበ እንዳልሆነ በይፋ ማሳወቁ ይታወቃል።