ኢትዮ ቴሌኮም ላለፉት ሁለት ዓመታት ሥራ ላይ ለማዋል ዝግጅት ሲያደርግበት የቆየውን የሞባይል ገንዘብ ዝውውር አገልግሎት ‹‹ቴሌ ብር›› በይፋ አስጀመረ።
ለ127 ዓመታት የድምፅ፣ የመልዕክት፣ የኢንተርኔትና ተዛማጅ አገልግሎቶችን ብቻ ሲያቀርብ የነበረው ኢትዮ ቴሌኮም፣ መንግሥት የቴሌኮም ዘርፉን ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት ለማድረግ መወሰኑን ተከትሎ፣ ላለፉት ሁለት ዓመታት ሲንቀሳቀስበት የነበረውንና ያለፉት አምስት ወራት ከቻይናው ሁዋዌ ኩባንያ ጋር የዘረጋውን የቴሌ ብር የሞባይል አገልግሎት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሪት ፍሬሕይወት ታምሩ፣ የኢትዮ ቴሌኮም የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ግርማ ብሩና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች በተገኙበት ማክሰኞ ግንቦት 3 ቀን 2013 ዓ.ም. በወዳጅነት አደባባይ በይፋ አስመርቋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት መጀመር ሲገባ በጊዜው ያልተጀመረ አገልግሎት ነው ብለው፣ በ2000 ዓ.ም. አገልግሎቱን የማስጀመር መነሻ ሐሳብ ለመንግሥት ቀርቦ በወቅቱ ምላሽ ያላገኘ ዕቅድ እንደነበረ አስታውሰዋል።
አገልግሎቱን ለማስጀመር ብዙ ዋጋ ተከፍሏል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ፣ ይህም መንግሥት የውጭ ቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢዎችን በአገር ውስጥ እንዲሳተፉ ሲጋብዝ ከቴሌኮም አገልግሎት ሁለት ሦስተኛ የሆነ ገቢ ያስገኛል የሚባለውን የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት ለአንድ ዓመት በብቸኝነት በኢትዮ ቴሌኮም ብቻ እንዲሰጥ መፍቀዱ አንዱ እንደሆነ ገልጸዋል። በሒደት ግን አገልግሎቱ ለሌሎች ኩባንያዎች የሚከፈትበት ሁኔታ እንዳለ አስታውቀዋል።
ወ/ሪት ፍሬሕይወት በበኩላቸው የቴሌኮም መሠረተ ልማትን ከመደበኛ አገልግሎት ባሻገር ለመጠቀም፣ በኢትዮጵያ 35 በመቶ ብቻ የሆነውን የፋይናንስ አገልግሎት ተጠቃሚ ተደራሽነትን ለማሳደግና የጥሬ ገንዘብ ዝውውርን ለመቀነስ በማሰብ የሞባይል ገንዘብ ዝውውርን በይፋ ማስጀመር አስፈልጓል ብለዋል።
አገልግሎቱ ገንዘብን ከማስተላለፍ፣ ከመቀበልና ክፍያ ከመፈጸም በተጨማሪ ከተለያዩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጋር በመሆን እንደ ውኃና ፍሳሽ፣ የኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ የትራንስፖርትና ሌሎች አገልግሎቶች በተዘጋጀው የሞባይል መተግበሪያ፣ እንዲሁም ከኩባንያው ጋር ልዩ ውል ካላቸው ጋር በመሆን የሚከናወን እንደሆነ ተገልጿል።
ኢትዮ ቴሌኮም በመጀመርያው ዓመት 12.7 ሚሊዮን ከሚሆኑት የሞባይል ደንበኞቹ 710 ሚሊዮን የሚደርስ የግብይት ዝውውር በማድረግ 66.9 ቢሊዮን ብር ለማዘዋወር ያቀደ ሲሆን፣ ይህን ቁጥር በአምስት ዓመት መጨረሻ ከ33 ሚሊዮን ደንበኞች 3.5 ትሪሊየን ብር በአገልግሎቱ እንደሚያንቀሳቅስ ተገልጿል ።
የሞባይል ገንዘብ ዝውውር አገልግሎት ኢትዮ ቴሌኮም በአገሪቱ ካለው ሰፊ ተደራሽነት አንፃር ትልቅ የሚባል ሚና እንደሚጫወት የተገለጸ ሲሆን፣ በተለይም በውጭ አገር ከሚገኙ ተጠቃሚዎች የሚደረገው የገንዘብ ማስተላለፍ አገልግሎት፣ ለኩባንያውም ሆነ ለአገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ግኝት የሚኖረው አስተዋጽኦ ትልቅ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
በተንቀሳቃሽ ስልክ በባንክ የሚገኝ ገንዘብን ማንቀሳቀስ፣ መላክ፣ መቀበልና ክፍያ የመፈጸም አገልግሎት እንደ ኬንያ ባሉ የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች ስኬታማነቱ ይጠቀሳል። የኢትዮጵያ ባንኮችና የገንዘብ ተቋማትም ይህንኑ አገልግሎት ከውጭ አገር የቴክኖሎጂ አቅራቢ ኩባንያዎችና ከኢትዮ ቴሌኮም በተናጠል ተግባራዊ ለማድረግ ቅድመ ዝግጅት ሲያደርጉ መቆየታቸው ይታወሳል።