ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የማጠናቀቂያው የጨዋታ መርሐ ግብር በሐዋሳ ከተማ እየተከናወነ ይገኛል፡፡ ፋሲል ከነማ ውድድሩ አራት ጨዋታ እየቀረው የዋንጫ ባለቤት መሆኑን ቢያረጋግጥም፣ ውድድሩን በሁለተኛነት የሚያጠናቅቀው ክለብ ገና አልለየም፡፡ በሚቀጥለው ዓመት በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ላይ የመሳተፍ ዕድል ይኖረዋል፡፡
ከአንድ ዓመት በፊት ፕሪሚየር ሊጉን የተቀላቀለው ሀድያ ሆሳዕና የፋሲል ከነማ ተቀናቃኝ ሆኖ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በደረጃ ሠንጠረዡ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ነበር፡፡ በዚሁ የተነሳ ክለቡ በውድድር ዓመቱ እንደነበረው ጥንካሬና ውጤት በቀጣዩ ዓመት በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ላይ የመሳተፍ ዕድል ይኖረዋል የሚል ቅድመ ግምትም አግኝቶ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ክለቡ ፋይናንስን ጨምሮ በገጠመው ውስጣዊ ችግር ምክንያት በቅድመ ግምቱ መሠረት አሁን ላይ ያንን የሚያሳካ አይመስልም፡፡ ብዙዎቹ የቡድኑ ተጫዋቾች ቃል የተገባልን የፊርማና ወርኃዊ ክፍያ አልተከፈለንም በሚል ሆቴል ለቀው ከወጡ ሰነባብተዋል፡፡ ክለቡን በበላይነት የሚያስተዳድረው አካል ደግሞ በድርጊቱ ተሳትፈዋል ያላቸውን እያንዳንዱን ተጫዋች እግር ኳሳዊ ከሆኑ እንቅስቃሴዎች ሁለት ዓመት እንዲታገዱ ማድረጉን ክለቡ በማኅበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል፡፡
ክለቡ በፕሪሚየር ሊጉ የማጠናቀቂያ ጨዋታዎች ተከታታይ ሽንፈቶችን እያስተናገደ፣ በደረጃ ሠንጠረዥ ቀድሞ የነበረውን ደረጃም እየለቀቀ መምጣቱ የክለቡን ደጋፊዎች አስቆጥቶ በሆሳዕና ከተማና አካባቢው ድርጊቱ ወደ ተቃውሞ ተለውጦ የንብረት ውድመት ማስከተሉ እየተነገረ ይገኛል፡፡
የክለቡ ኃላፊዎች በበኩላቸው ጉዳዩ በመገናኛ ብዙኃን ከሚገባው በላይ መጋነኑ ያስከተለው ችግር እንደሆነ በመግለጽ ደጋፊዎችና አንዳንድ የክለቡ ተጫዋቾች እንዲረጋጉ፣ ችግር እንኳ ቢኖር በውይይትና በንግግር ለመፍታት ዝግጁ ስለመሆናቸው ጭምር ይናገራሉ፡፡
በሌላ በኩል ማንነታቸውን መግለጽ ያልፈለጉ ተጫዋቾች ደግሞ፣ ‹‹ከተማ አስተዳደሩ በፕሪሚየር ሊግ ደረጃ የሚወዳደር ቡድን እንዲኖረው ከማሰቡ በፊት ማድረግ የሚገባው፣ እችላለሁ ወይስ አልችልም የሚለውን ከመጀመሪያው ማሰብ ነበረበት፡፡ በዚያ ላይ ክለቡ ለተጫዋቾች የገባውን ቃል እንዲፈጽም ጥያቄ ሲቀርብለት ጉዳዩን በውይይት ከመፍታት ይልቅ ወደ ቅጣት መግባቱ ምን ያህል በተሳሳተ መንገድ ላይ መሆኑን የሚያመላክት እንደሆነ መረዳት ይቻላል፤›› ይላሉ፡፡ ክለቡ አሁንም ችግሩን ውጫዊ ከማድረግ ወደ ራሱ ተመልክቶ ለመፍትሔው ጥረት ቢያደርግ ነው ለክለቡ የሚጠቅመው፤›› በማለትም ይገልጻሉ፡፡
የሀድያ ሆሳዕና ክለብ አመራሮች ተጫዋቾቹ ላቀረቡት ጥያቄ ተገቢውን ምላሽ ባለመስጠታቸው የተነሳ ክለቡ ከነበረበት ደረጃ እያሽቆለቆለ መምጣቱ ያበሳጫቸው ደጋፊዎች፣ ወደ ጎዳና በመውጣት ከጉዳዩ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌላቸው ግለሰቦች ንብረት ላይ ጉዳት ያደረሱ ደጋፊዎች ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ የሚጠይቁ ደጋፊዎች አልጠፉም፡፡
እነዚህ ደጋፊዎች፣ ‹‹የዞኑ አመራሮች ባለፈው የቡድኑ አባላት ወደ ድሬዳዋ ላለመሄድ አድማ በመቱ ጊዜ የተፈጠረውን የደጋፊዎች ቁጣ ከግምት አስገብቶ ለችግሩ መፍትሔ ቢሰጥ ኖሮ አሁን የተፈጠረው ችግር ባልተፈጠረ ነበር፤›› ይላሉ፡፡ አሁንም ተጨማሪ ችግር ከመከሰቱ በፊት አመራሮቹ አፋጣኝ የመፍትሔ አቅጣጫ ማስቀመጥ እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል፡፡
‹‹በወጣቶች ብቻ ሳይሆን በአብዛኛው ማኅበረሰብ ልብ ውስጥ ሰርጾ የገባውን ክለብ አመራሮቹ ዞኑን በማስተባበር በችግሩ ምክንያት ወደ አላስፈላጊ አቅጣጫ ሊሰማሩ የሚችሉ ወጣቶችን አዕምሮ አዎንታዊ በሆነ መንገድ ማስተናገድ ይጠበቅበታል፤›› ሲሉም ይመክራሉ፡፡
በጉዳዩ ላይ የክለቡን አመራሮች አስተያየት ለማግኘት ያደረግነው ጥረት አልተሳካም፡፡