ቤዝ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ በአሥር የቱሪስት መዳረሻዎች አካባቢ እያንዳንዳቸው ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ የቱሪስት መዝናኛና የባህል ማዕከላት ሊገነባ መሆኑን ለሪፖርተር በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡
አቶ መሠረት መኮንን የቤዝ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ድርጅትና የቤዝ ኢንተርናሽናል ቱር ኤንድ ትራቭል ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ በ300 ሚሊዮን ብር ያስገነቡትን ሆቴል ለአግልግሎት ክፍት ሲያደርጉ እንዳብራሩት፣ የመዳረሻ ቦታዎች የሚገነቡት እነዚህ ማዕከሎች ከዚህ በፊት የነበረውን ደረጃውን የጠበቀ የምግብ፣ የመኝታ፣ የመዝናኛ ሥፍራ እንዲሁም ጠቅለል አድርጎ የአካባቢውን ባህልና ወግ አለማሳየት ችግሮች ለመቅረፍ ያስችላሉ፡፡
ጎንደርን፣ አርባ ምንጭንና ኮንሶን ጨምሮ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገነቡት እነዚህ ማዕከላት ከኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች በስተቀር ሙሉ በሙሉ አካባቢው ላይ ባሉ ባህላዊ ቁሳቁስ የሚሠሩ ሲሆን፣ እያንዳንዳቸው ከ50 በላይ የመኝታ ክፍሎች፣ ዘመናዊና ባህላዊ ሬስቶራንቶች፣ የየክልሉን ባህል የሚያሳዩ ሙዚቃ የሚቀርብበት፣ ጎብኚዎች ባህላዊ ምግብና መጠጦች የሚታደሙባቸው አዳራሾች፣ አነስተኛ ሙዚየሞች፣ የመኪና ማቆሚያ ቦታዎችና ሌሎችም አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው፡፡
የገንዘብ አቅርቦት ከባንክ የተገኘ ሲሆን፣ አሁን ያለው የፀጥታ ችግር ከተስተካከለ እያንዳንዳቸው በስድስት ወራት ውስጥ ግንባታቸው እንደሚጠናቀቅ አቶ መሠረት ገልጸዋል፡፡ የመሬት አቅርቦትን በተመለከተ ከየክልሎቹ ጋር ተነጋግረው ፈቃደኛ መሆናቸውን አክለዋል፡፡
ግንባታው ሲጠናቀቅም ለበርካታ ኢትዮጵያውያን የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ በኮቪድ ምክንያት የቀዘቀዘውን የቱሪዝም እንቅስቃሴ ሊያነቃቃው እንደሚችል ተስፋ አድርገዋል፡፡
አቶ መሠረት እንዳሉት፣ በኮቪድ ምክንያት የውጭ ቱሪስት የቀነሰ ቢሆንም፣ የአገር ውስጥ ቱሪስት ሊጨምር አጋሚው ጥሩ ሆኖ ሳለ በአገሪቱ አልፎ አልፎ ባሉ ግጭቶችና በየትኛው አካባቢ ምን ሊከሰት እንደሚችል አለመታወቁ ጎብኚዎችን ይዞ ለመንቀሳቀስ አስቸጋሪ አድርጓል፡፡ ሥራዎች በብዛት እየቆሙ በመሆናቸውም ሰላሙ ቶሎ መስፈን ካልቻለ ለቱሪዝሙ ዘርፍ ከባድ አደጋ ያጋጥመዋል፡፡
ቤዝ ኢንተርናሽናል ቱር ኤንድ ትራቭል ኢትዮጵያ ከተቋቋመ ከሰባት ዓመታት በላይ ሲሆን፣ ከ200 በላይ ሠራተኞችንም ቀጥሮ ያሠራል፡፡ በቅርቡም አትላስ አካባቢ የሚገኘውን ቀድሞ ሲያንሲቲ የሚባለውን ከ40 በላይ የመኝታ ክፍሎች ያሉትን ሆቴል በመግዛትና ሙሉ በሙሉ እንደ አዲስ በማደስ ቤዝ ኢንተርናሽናል ሆቴል በሚል በአዲስ ስያሜ ለአገልግሎት ክፍት አድርጓል፡፡