የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የአፍሪካ ቀንድ ጉዳዮች ልዩ መልዕክተኛ አድርጎ የሰየማቸው አምባሳደር ጄፍሪ ፊልትማን፣ በግብፅና በአፍሪካ ቀንድ አገሮች ያደረጉትን ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች የተመለከተ ጉብኝት አጠናቀው ባለፈው ሳምንት ወደ አሜሪካ መመለሳቸው ይታወሳል፡፡ የአሜሪካ ሴኔት የልዩ መልዕክተኛውን የጉዞ ሪፖርት ለማዳመጥና የአሜሪካን ጥቅም መሠረት የሚያደርግ ቀጣይ የፖሊሲ አቅጣጫ ለመወሰን፣ ሰኞ ግንቦት 9 ቀን 2013 ዓ.ም. ምክክር አድርጓል።
የሴኔቱ የውጭ ግንኙነት ኮሚቴ ሰኞ ቀን ያካሄደው የውይይት መድረክ በመሠረታዊነት ኢትዮጵያ ላይ ትኩረት ያደረገ ቢሆንም፣ የውይይቱ ርዕሰ ጉዳይ ግን ‹‹በአፍሪካ ቀንድ ያሉ የአሜሪካ ሥጋትና ዕድሎች›› የሚል እንደሆነ የሴኔቱ መረጃዎች ያመለክታሉ።
በዚህ መድረክ ላይም ጄፍሪ ፊልትማን በሰሞኑ ጉዟቸው የተገነዘቡትን አስመልክቶ ከሚያቀርቡት ሪፖርት በተጨማሪ፣ በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ኃላፊ ሮበርት ጎዴክ፣ እንዲሁም ስማቸው እንዳይገለጽ ዕቀባ የተደረገበት የአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነት መሥሪያ ቤት የአፍሪካ ቀጣና የደኅንነት ኃላፊ ለሴኔቱ ሪፖርት ማቅረባቸው ታውቋል።
የአሜሪካ መንግሥት አካላት ሴኔቱን ጨምሮ በሕግ አግባብ በዝግ መካሄድ የሚገባው ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር፣ የዕለት ተዕለት ተግባራቸውን በቀጥታ ሥርጭትና በማንኛውም ሰዓትና ወቅት ለሕዝብ ተደራሽ በሆነ መንገድ ማከናወን ይጠበቅባቸዋል።
ይህ ኢትዮጵያን ማዕከል ያደረገውና ‹‹በአፍሪካ ቀንድ ያሉ የአሜሪካ ሥጋትና ዕድሎች›› የሚል ርዕሰ አጀንዳ የተሰጠው መድረክ ግን፣ የአገሪቱን ሕግ መሠረት አድርጎ በዝግ ተካሂዷል።
የሴኔቱ የአሠራር ሥነ ሥርዓት ደንብ የሴኔቱ አጠቃላይ ጉባዔም ሆነ የሴኔቱ ኮሚቴዎች ስብሰባም ሆነ አሠራር ለሕዝብ ክፍት በሆነ መድረክ እንደሚካሄድ፣ ነገር ግን በስድስት የተዘረዘሩ ደንቦች ምክንያት ሴኔቱ ውይይቱን በዝግ እንዲያካሂድ የሚጠይቅ ሞሽን ቀርቦለት በዝግ እንዲካሄድ ሊወስን እንደሚችል ያመለክታል።
ከእነዚህ የተዘረዘሩ ምክንያቶች አንዱና ውይይቱ በዝግ እንዲካሄድ ለመወሰን ሊጠቀሱ ከሚችሉት የደንቡ ስድስት አንቀጾች መሀል ከዚህ ጉዳይ ጋር ቀጥታ ግንኙነት የሚኖረው፣ ‹‹የአሜሪካ ብሔራዊ የደኅንነትን የሚመለከት ወይም በሚስጥር መካሄድ ያለበት የአሜሪካ የውጭ ግንኙነትን የሚመለከት እንደሆነ›› የሚለው ነው።
በዚህ መንገድ ተወስኖ የተካሄደ የውይይት መድረክ ላይ የሚቀርቡ ሪፖርቶችም ሆኑ የሚነሱ ሐሳቦች ከኮሚቴው ጽሕፈት ቤት መውጣት አይችሉም። ከጽሕፈት ቤቱ መውጣት የሚችሉት በማኅደር ተሰንደው እንዲቀመጡ ሲደረግ፣ ይህም ቢሆን ሴኔቱ ከሚገኝበት ካፒቶል ሂል “SVC-127” ተብሎ ከሚጠራው ቅጥር ግቢ ማለፍ እንደማይችል መረጃው ያመለክታል።
ሰኔቱ ኢትዮጵያን ማዕከል ያደረገው ውይይት ምን እንደሆነ በግልጽ አይታወቅ እንጂ፣ ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ተግባራዊ እያደረጉት የሚገኘው የአፍሪካ ቀንድ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ፣ በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ከከፍተኛ መቃቃር አልፎ በቃላት ጦርነት እየተካረረ ነው።
ልዩ መልዕክተኛው ፊልትማን ግብፅን ጨምሮ በኢትዮጵያ፣ በሱዳንና በኤርትራ ያደረጉትን ጉብኝት አጠናቀው ወደ አሜሪካ መመለሳቸውን በተመለከተ የአሜሪካ መንግሥት ያወጣው መግለጫ ላይ፣ አሜሪካ የኢትዮጵያ ሁኔታ እንደሚያሳስባት በድጋሚ አስታውቃለች።
ይህንንም ተከትሎ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አንቶኒ ብሊንከን ባለፈው ዓርብ ባወጡት መግለጫ፣ ይህንኑ የመንግሥታቸውን አቋም በድጋሚ አስረግጠዋል።
በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል የተፈጠረው የግንኙነት መሸርሸርና መካረር ዋና ምክንያት የትግራይ ክልልን ሲያስተዳድር የነበረው ሕወሓት በመከላከያ ሠራዊቱ ላይ ጥቃት መሰንዘሩን ተከትሎ፣ የፌዴራል መንግሥት ወደ ሙሉ ጦርነት በመግባቱና በዚህም ክልሉ በከፍተኛ ቀውስ ውስጥ መገኘቱ፣ በተጨማሪም በዚህ ጦርነት ውስጥ የኤርትራ ጦር የፌዴራል መንግሥትን ወግኖ አልያም በኤርትራ ብሔራዊ ደኅንነት ላይ ሥጋት ደቅኗል በማለት በጦርነቱ በመሳተፉ ነው።
በሌላ በኩል የትግራይ ክልል ግጭትን ተከትሎ በኢትዮጵያና በሱዳን የጋራ ድንበር የይገባኛል ጥያቄ አዲስ ወታደራዊ ግጭት መቀስቀሱ፣ በተጨማሪም በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን ልዩነታቸውን ለመፍታት ያደርጉት የነበረው ድርድር መፍትሔ ባለማምጣቱ በአገሮቹ መካከል የፖለቲካ ውጥረቱን ማጦዙ፣ አዲሱን የጆ ባይደን መንግሥት ኢትዮጵያን ማዕከል አድርጎ ትኩረቱን በዚህ ቀጣና ላይ እንዲያደርግ ያስገደዱት ምክንያቶች ሆነዋል።
ከፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ቀደም ብሎ የነበረው የአሜሪካ መንግሥት አስተዳደር (የትራምፕ አስተዳደር) የትግራይ ክልል ግጭትን በተመለከተ ለዘብተኛ የፖለቲካ አቋም ያራምድ የነበረ ሲሆን፣ ይህ ሁኔታ ግን አዲሱ አስተዳደር ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ ተቃራኒ የሚባል የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ለውጥ ስለማድረጉ የሚያስገነዝብ ይፋዊ መረጃ በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ድረ ገጽ ላይ መመልከት ይቻላል።
የትግራይ ክልል ወታደራዊ ግጭት በተፋፋመበት የኅዳር ወር አጋማሽ ላይ በወቅቱ የነበረውን አዲስ ክስተት አሰመልክቶ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ የሰጡት የፕሬዚዳንት ትራምፕ አስተዳደር የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የአፍሪካ ረዳት ተጠሪ ቲቦር ናዥ፣ እንዲሁም በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር የነበሩት ማይክ ራይነር የትግራይ ክልል ቀውስ ወደ አፍሪካ ቀንድ የመስፋፋት ሥጋትን ይኖረው እንደሆነ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፣ ግጭቱ ከትግራይ ክልል አልፎ የሚሄድበት ዕድል እንደሌለው፣ እንዲያውም በኢትዮጵያዊያን ላይ አንድ የሆነ የፖለቲካ አመለካከት እንደፈጠረ በመናገር ሥጋቱን አጣጥለውት ነበር።
የፕሬዚዳንት ጆ ባይደን አስተዳደር ግን በትግራይ ክልል ያለው ቀውስ በፍጥነት ካልተፈታ፣ ወደ ሌሎች የአካባቢው አገሮች ሊዛመት ይችላል የሚል ሥጋት አለው።
ባለፈው ሳምንት መጨረሻ መግለጫ የሰጡት አንቶኒ ብሊንከን፣ የትግራይ ክልል ጦርነት በአፋጣኝ እንዲቆም በድጋሚ በማሳሳብ ይህ የማይሆን ከሆነ፣ መንግሥታቸው ከሌሎች አጋር አገሮች ጋር በመተባበር ዕርምጃ እንደሚወስድ አስታውቀው ነበር።
የትግራይ ክልል ቀውስ በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ ከፍተኛ የሰብዓዊ ቀውስ እንደፈጠረ የገለጹት ብሊንከን፣ የኤርትራ ጦር ከትግራይ በፍጥነት የማይወጣ ከሆነ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል ጭምር ሥጋታቸውን ገልጸዋል።
በተመሳሳይም የአማራ ክልል ልዩ ኃይል ከትግራይ ክልል ሙሉ በሙሉ ለቆ እንዲወጣ፣ በዚህ ጦር ቁጥጥር ሥር የሚገኙ የምዕራብ ትግራይ የአስተዳደር ወሰኖችን ለትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ማስረከብ እንደሚገባውም አሳስበዋል።
አንቶኒ ብሊንከን ይህንን ማሳሰቢያ በሰጡ በማግሥቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ለዚህ ምላሽ የሚመሰል ንግግር፣ በአፋር ክልል የተገነባውን የኢንዱስትሪ ፓርክ ባስመረቁበት ወቅት አድርገዋል።
ኢትዮጵያ ዛሬ ቁርሷን ምን መብላት እንዳለባትና ማታ ስትተኛ ምን መልበስ እንዳለባት ታሪክ የሌላቸው አገሮች የገንዘብ አቅማቸውን መሠረት አድርገው ሊያዙ እየዳዳቸው እንደሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረው፣ ‹‹እኛ ያልተገዛን፣ ያልተንበረከክንና የማንንበረከክ ታሪክ ያለን ሕዝቦች ነን። ስለሆነም ታሪክ የሌላቸው አገሮች በገንዘባቸው አቅም ሊያዙን አይችሉም፤›› ብለዋል።
አክለውም፣ ‹‹መላው ኢትዮጵያዊያዊ በፖለቲካ፣ በብሔርና በሃይማኖት ሳይከፋፈል አንድ ሆኖ እኛ ኢትዮጵያውያን ነፃ የነበርንና ነፃ ሆነን የምንቀጥል ኩሩ ሕዝቦች መሆናችንን በከፍተኛ ማስተዋልና ትብብር ለእነዚህ ጎረምሶች ማስተማርና ማሳየት ያስፈልጋል። እነሱ ሳይፈጠሩ የነበርን፣ ከእነሱ ቀድመን ዴሞክራሲንም ሆነ ዲፕሎማሲን ቀድመን የተገበርን መሆናችንን ዓለም እንዲረዳው እንድታደርጉ እጠይቃለሁ፤›› ሲሉም ተደምጠዋል።
‹‹በቀጣይ ዓመታት ያለ ምንም ጥርጥር የኢትዮጵያን የግዛት አንድነትና የኢትዮጵያን ሰላምና ብልፅግና እናረጋግጣለን፡፡ አሁን በቂ ልምድና ብቃት ያካበትን በመሆኑ፣ ይህንን ከማሳካት ለማስቆም የሚችል ምንም ምድራዊ ኃይል እንደሌለ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ፤›› ብለዋል።
የጀርመን መንግሥት ዓለም አቀፍ የፀጥታና ደኅንነት ጉዳዮች ኢንስቲትዩት ባልደረባና የአፍሪካ ቀንድ ጉዳዮች ተንታኝ የሆኑት አንቴ ዌበር ማክሰኞ ግንቦት 10 ቀን 2013 ዓ.ም. በኢትዮጵያና በቀጣናው ጉዳዮች ላይ በሰጡት አስተያየት፣ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የአካባቢውን ትስስር ለማሳለጥ ከተቋቋመው የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥት ተቋም ከሆነው ኢጋድ ውጪ በመንቀሳቀስ ኢትዮጵያን፣ ሶማሊያንና ኤርትራን ያካተተ የሦስትዮሽ መንገድ መከተላቸው በሌሎች የቀጣናው አባል አገሮችም ሆነ በአካባቢው ላይ ጂኦፖለቲካዊ ጥቅም ባላቸው አሜሪካና የአውሮፓ ኅብረት አገሮች ላይ ሥጋት መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡
ይህንንም ለማምከን በተቻለው ዲፕሎማሲያዊ መንግድ በጋራ እየሠሩ መሆኑን፣ ከምንጊዜውም በላይ ምዕራባውያኑ በአካባቢው ፖለቲካ ላይ የተናበበ ጥምረት እንዲያደርጉ ማስገደዱን አክለዋል።