የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ስድስተኛውን አገራዊ ምርጫ የድምፅ መስጫ ቀን ተግባራት ለማከናወን፣ ካሁን ቀደም የዕጩዎችን ምዝገባ ካከናወኑ 138,655 የምርጫ አስፈጻሚዎች በተጨማሪ 106,345 የምርጫ አስፈጻሚዎች እንደሚያስፈልጉት አስታወቀ፡፡
ቦርዱ ምርጫው ከሁለት እስከ ሦስት ሳምንታት ላሉ ጊዜያት የድምፅ መስጫ ቀኑን እንደሚያራዝም ቅዳሜ ግንቦት 7 ቀን 2013 ዓ.ም. መግለጹን ተከትሎ የድምፅ መስጫ ቀኑ ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. እንዲከናወን መወሰኑን ለማስታወቅ ግንቦት 12 ቀን 2013 ዓ.ም. በዲሊ ኦፖል ሆቴል መግለጫ የሰጡት የቦርዱ የኮሙዩኒኬሽንስ አማካሪ ሶልያና ሽመልስ፣ እነዚህ አስፈጻሚዎች መቀጠራቸው በድምፅ መስጫ ቀን በእያንዳንዱ የምርጫ ጣቢያዎች አምስት አስፈጻሚዎች እንዲኖሩ ያደርጋል ብለዋል፡፡
እነዚህን አስፈጻሚዎች በቦርዱ ካሁን ቀደም አስፈጻሚ ለመሆን አመልክተው በተጠባባቂነት ከተያዙ ከ160 ሺሕ በላይ አመላካቾች መካከል ለመመልመል መታቀዱን ያስታወቁት አማካሪዋ፣ ያሉበትን ቦታ በመለየትና በብዛት ከሚገኙባቸው ቦታዎች እጥረት ወዳለባቸው ሥፍራዎች በመውሰድ እንዲሠሩ ለማድረግ ታቅዷል፡፡ በተለይም አፋርና ሶማሌ ክልሎች በብዛት እጥረት የታየባቸው አካባቢዎች ናቸውም ብለዋል፡፡
እነዚህ አስፈጻሚዎችና የምርጫ ጣቢያ ኃላፊዎች እንዲሁም የምርጫ ተቆጣጣሪዎች በአራት ዙር ሠልጥነው ይሰማራሉ ያሉት ሶልያና፣ ሁሉም አስፈጻሚዎች በምርጫ ቀን ዝግጅት፣ በድምፅ ቆጠራ፣ በውጤት ድመራ እንዲሁም አስተዳደር ላይ ሥልጠና እንደሚወስዱ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ለድምፅ መስጫ ቀን የሚያገለግሉ ቁሳቁሶችን ለማጓጓዝ ዕቅድ እንደወጣና የድምፅ መስጫ ወረቀት ኅትመት በደቡብ አፍሪካና በዱባይ እየታተመ ስለሚገኝ በቀጣይ አሥር ቀናት ተጠናቅቀው ለሥልጠናና ለድምፅ መስጫ ቀን እንዲደርሱ በሚያስችል መልኩ ይሠራጫሉ ብለዋል፡፡
በመራጮች ምዝገባ በተለያዩ ምክንያቶች መራዘም ሳቢያ የድምፅ መስጫ ቀን ወደ ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. እንዲሸጋገር ውሳኔ የተላለፈ ቢሆንም፣ የመራጮች ምዝገባ ዘግይቶ በተጀመረባቸውና የፍርድ ቤት ክርክር ባለባቸው የምርጫ ክልሎች ምርጫው ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. እንደማይከናወን ተነግሯል፡፡ በዚህም መሠረት፣ በምዕራብ ወለጋ፣ በምሥራቅ ወለጋ፣ በቄለም ወለጋና በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከመሽና መተከል ዞኖች፣ እንዲሁም በቀረበባቸው ቅሬታ ሳቢያ የመራጮች ምዝገባ እንዲያቋርጡ በተደረጉ የሶማሌ ክልል ሰባት የምርጫ ጣቢያዎች ምርጫው ሰኔ 14 እንደማይከናወን ተገልጻል፡፡
በተመሳሳይ፣ ከክልላቸው ውጪ የሚኖሩ የሐረሪ ብሔረሰብ ነዋሪዎች ሐረሪዎች ብቻ ለሚወከሉበት የክልሉ ምክር ቤት አንድ አካል ድምፅ እንዲሰጡ የቀረበለትን ጥያቄ ቦርዱ ያልተቀበለው ሲሆን፣ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ደግሞ ውሳኔውን ውድቅ አድርጎት ነበር፡፡ ነገር ግን ቦርዱ ለሰበር ሰሚ ችሎት ይግባኝ በማለቱ ከክልላቸው ውጪ የሚኖሩ ሐረሪዎች ለብሔራዊ ሊግ ምርጫ ሰኔ 14 ድምፅ አይሰጡም ተብሏል፡፡
በሶማሌ ክልል ያሉ የምርጫ ክልሎች የቀረበባቸው ቅሬታ ማጣራት እየተደረገበት ሲሆን፣ ድምፅ ሊሰጥባቸው ይችላል ወይስ አይችልም የሚለውን የሚያጣራ ቡድን በክልሉ ተሰማርቶ እየሠራ እንደሆነም ተነግሯል፡፡ ስለዚህም፣ እነዚህ ሰባት የምርጫ ክልሎች እንደታገዱ ይቆያሉ፡፡