እነ አምባቸው መኮንንን (ዶ/ር) በመግደል በተከሰሱትም ላይ ውሳኔ ተሰጥቷል
ከአትላስ ወደ አውሮፓ ኅብረት በሚወስደው ጎዳና ደሳለኝ ሆቴል አካባቢ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ውስጥ፣ ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ምሽት 3፡00 ሰዓት አካባቢ የቀድሞውን የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹም ጀነራል ሰዓረ መኮንንን በጥይት ደጋግሞ በመተኮስ እንደገደላቸው፣ በቀረበበት ክስ መረጋገጡን በመንገር ፍርድ ቤት ጥፋተኛ ያለው ተከሳሽ በሞት እንዲቀጣ ተጠየቀ፡፡
ጥያቄውን ያቀረበው የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ሲሆን፣ ጥያቄው የቀረበለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ፀረ ሽብርና የሕገ መንግሥት ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ደግሞ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ለሰኔ 21 ቀን 2013 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ጀነራሉ የተገደሉት ከጓደኛቸው ሜጀር ጀነራል ገዛኢ አበራ ጋር መሆኑንና ገዳይ መሆኑ በዓቃቤ ሕግ በቀረበበት ክስ፣ የሰነድና የሰው ማስረጃ ተረጋግጦበት ጥፋተኛ የተባለው ልዩ አጃቢና ጥበቃቸው የነበረው አስር አለቃ መሳፍንት ጥጋቡ መሆኑ በተደጋጋሚ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
ፍርድ ቤቱ ግንቦት 27 ቀን 2013 ዓ.ም. በተከሳሹ ላይ የጥፋተኛነት ውሳኔ ከሰጠ በኋላ፣ ዓቃቤ ሕግ የቅጣት ማክበጃውን እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡
በመሆኑም ዓቃቤ ሕግ ሰኔ 11 ቀን 2013 ዓ.ም. በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 149 (3) ድንጋጌ መሠረት የቅጣት ማክበጃውን አቅርቧል፡፡ ዓቃቤ ሕግ በቅጣት ማክበጃው እንደገለጸው፣ ተከሳሹ በቀድሞ የአማራ ክልል የሰላምና የሕዝብ ደኅንነት ቢሮ ኃላፊ ሟች ብርጋዴር ጀነራል አሳምነው ጽጌ መሪነት ታቅዶ ለነበረው ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን የመለወጥ ድርጊት አካል ነበር፡፡ ጀነራል ሰዓረን የመግደል ተልዕኮ መቀበሉንና ከእነ ጓደኞቻቸው ግድያ መፈጸሙን በመጠቆም፣ በወንጀል ቅጣት አወሳሰን መመርያ ቁጥር 2/2006 መሠረት የወንጀል ድርጊቱ እጅግ ከባድ ተብሎ እንዲወሰንበት ጠይቋል፡፡
ተከሳሹ ወንጀሉን የፈጸመው የተጣለበትን እምነትና ኃላፊነት ያላግባብ በመገልገል በመሆኑ፣ በወንጀል ሕግ ቁጥር 84 (1ለ)፣ እንዲሁም በወንጀል ሕግ አንቀጽ 84 (1መ) እና በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 84 (1ሠ) ድንጋጌ መሠረት ቅጣቱ እንዲከብድ ጠይቋል፡፡
የወንጀል ቅጣት አወሳሰን መመርያ ቁጥር 2/2006ን መከተል ሳያስፈልግ ተከሳሹ አስር አለቃ መሳፍንት በሞት እንዲቀጣ ጠይቋል፡፡
በተመሳሳይ ቀን ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በአማራ ክልል በባህር ዳር ከተማ የተገደሉት አምባቸው መኮንን (ዶ/ር)፣ አቶ ምግባሩ ከበደና አቶ ዕዘዝ ዋሴን በመግደል ተከሰው ከነበሩት 55 ግለሰቦች መካከል አቶ ዘመነ ካሴን ጨምሮ 20 ግለሰቦች በነፃ ተሰናብተዋል፡፡
ባህር ዳርና አካባቢዋ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሰኔ 11 ቀን 2013 ዓ.ም. በዋለው ችሎት በሰጠው ውሳኔ፣ ስድስት ተከሳሾች በሌሉበትና በሌሎቹ ላይ የተለያዩ ውሳኔዎችን አስተላልፏል፡፡ 31 ተከሳሾች ላይ የክስ መቃወሚያና መከላከያ ምስክር ለመስማት ለሐምሌ 5 ቀን 2013 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡