በስድስተኛው አገር አቀፍ ምርጫ ላይ ከዕጩዎችና ከመራጮች ምዝገባ ጀምሮ እስከ ፖሊሲ ክርክር ድረስ በጣም በርካታ ሳንካዎች የተከሰቱ ቢሆንም፣ በየትኛውም ምርጫ ሊያጋጥም የሚችል ልምድ ነው፡፡ በእንዲህ ዓይነቱን ልምድ በመቀነስ እንጂ ጨርሶ ለማጥፋት እንደማይቻል የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ፓርቲ ፕረዚዳንት ገልጸዋል፡፡
አቶ የሺዋስ አሰፋ ይህንን ያስታወቁት፣ በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ምርጫ ጣቢያ 11 ተገኝተው በሕዝብ ተወካዮችና ለአዲስ አበባ ምክር ቤቶች ድምፅ ከሰጡ በኋላ በሰጡት አስተያየት ነው፡፡
እንደ አቶ የሺዋስ አስተያየት እስካሁን በተካሄደው እልህ አስጨራሽ ጉዞ በበርካታ ዜጎች ላይ የሕይወት መስዋዕትነትና እንግልት እንደደረሰባቸው፣ ነገር ግን ይኼ ሁሉ ለኢትዮጵያ እስከሆነ ድረስ መቻል ያስፈልጋል፡፡
ምርጫው ሰኞ ቀን መከናወኑ ማንም ሰው ምርጫውን እንደ አንድ ሥራ አድርጎ እንዲያየው በማድረግ በኩል የጎላ አስተዋጽኦ እንዳለው ከአቶ የሺዋስ ማብራሪያ ለመረዳት ተችሏል፡፡
ምርጫ ሲባል የተሻለ ሥርዓት ማምጫ ሥልት ወይም ሰላማዊ መንገድ እንደሆነ፣ ይህ ዓይነቱም ሥርዓት ብቸኛው ነው ባይባልም የተሻለ፣ ሰላማዊና የሠለጠነ መንገድ እንደሆነ፣ ለዚህም ምርጫ ከዋና ዋናዎቹ ተጫዋቾች መካከል ኢዜማ አንዱ እንደሆነ ነው የተናገሩት፡፡
በምርጫው ብትሸናፉ ‹‹ምን ታደርጋላችሁ? ብታሸንፉስ ዓላማችሁ ምንድነው?›› ተብለው ለቀረበላቸው ጥያቄ አቶ የሺዋስ ሲመልሱ፣ ‹‹በዘውዱና በደርግ ሥርዓት የተከናወኑ ምርጫዎች ሁሉ ውጤታቸው በቅድሚያ የታወቀ ነው፡፡ ውጤታቸው የሚታወቁ ምርጫዎች ደግሞ ደባሪ (ቦሪንግ) ናቸው፡፡ ከዚህ አኳያ የዘንድሮ ስድስተኛው ምርጫ ውጤት ከወዲሁ አይታወቅም፡፡ ይህም ማለት ደግሞ የሕዝብን ዳኝነት ለመቀበል ዝግጁ ነው ማለት ነው ብለዋል፡፡
ከዚህ አኳያ የኢትዮጵያ ሕዝብ የውሳኔውን ለመቀበል ዝግጁ መሆኑንና ብልፅግናን ጨምሮ ሁሉም ፓርቲዎች በዚህ መልኩ ራሳቸውን ማዘጋጀት እንዳለባቸው ነው ያመለከቱት፡፡
ጨዋታው ጥሩ የሚሆነው በዚህ መልኩ ሲከናወን ነው፡፡ ሰው ሊሸንፍም ሊያሸንፍም እንደሚችል አውቆ ሲወዳደርና ሲፎካከር፣ በዚህ ላይ ደግሞ የሕዝብን ብይን ሲቀበል የዴሞክራሲ ሥርዓት ዕውን ይሆናል የሚል እምነት እንዳላቸው ነው የገለጹት፡፡
አቶ የሺዋስ ጨምረው እንዳስረዱት፣ ዋናው ነገር የሚፈለገው ኢትዮጵያ እንድታሸንፍ ነው፡፡ ስለሆነም በዚህ ምርጫ ያልተሳካለት የፖለቲካ ፓርቲ ከቀጣዩ አምስት ዓመት በኋላ ተጠናክሮ የሚወጣበትን መንገድ መቀየስ ግድ ይላል፡፡ ይህም በመሆኑ ሁሉም ፓርቲዎች ጨዋነት በሰፈነበት መልኩ የሕዝቡን ውሳኔ ለመቀበል ዝግጁ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡