አገር አቀፍ የባህልና ጥበባት ሙያተኞች ዕውቅናና ሽልማት ሰኔ 29 ቀን 2013 ዓ.ም. ሊካሄድ መሆኑን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ሰኔ 29 ቀን 2013 ዓ.ም. ለሚካሄደው አገር አቀፍ የባህልና ጥበባት ሙያተኞች ዕውቅናና ሽልማት ላይ የሚሳተፉ የዕጩዎች ምልመላና የመረጣ የጥቆማ ማቅረቢያ ቅጽ መርሐ ግብር መጀመሩንም ገልጿል፡፡
ውድድሩም የሚደረግባቸው ዘርፎች በድርሰት፣ በፊልም፣ በሰርከስ፣ በሥዕልና ቅርፃ ቅርፅ ጥበብ፣ በሙዚቃ፣ በቴአትርና በውዝዋዜ ጥበቦች ላይ ያሉ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ተሳታፊ መሆን እንደሚችሉ መረጃው ያመለክታል፡፡
ለመጀመርያ ጊዜ ይደረጋል በተባለው ውድድር የሚቀርቡ ተወዳዳሪዎች የተቀመጠውን መሥፈርት በማማሏት መሳተፍ ይችላሉ ተብሏል፡፡
በሙያው ረዥም ዓመታት በሥራ ያሳለፉ፣ በሙያቸው ተተኪዎችን በተጨባጭ ስለማፍራታቸው፣ ከአገር ውስጥ ባለፈ በውጭ አገር ጭምር አድናቂዎች ያላቸው፣ ሥራዎቻቸው በሁሉም ዓይነት መገናኛ ብዙኃን ተደራሽ ማድረጋቸውና ተመልካች እንዲሁም አድናቆት ማትረፋቸው፣ ሥራዎቻቸው አገራዊ ባህል፣ ታሪክና ወግን የጠበቁ ሆነው አገራዊ አንድነትና ለብሔራዊ መግባባት ያበረከቱት አስተዋጽኦ፣ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ስለማጠናከራቸውና በተለያዩ አገራዊ ቋንቋዎች እንዲተላለፉ ያደረጉትን ጥረት አስመልክቶ የተዘጋጀውን መመዘኛ ነጥቦች የሚያሟሉ በውድድሩ መሳተፍ የሚችሉ ናቸው፡፡