ከዓመታት በፊት በኦሮሚያ ክልል ይፋ በተደረገው የኢኮኖሚ አብዮት መሠረት ከተቋቋሙት ኩባንያዎች መካከል አንዱ የሆነው የኬኛ የመጠጥ አክሲዮን ማኅበር ለቢራ ፋብሪካ ግንባታ፣ ለማሽነሪዎች አቅርቦትና ተከላ ከጀርመን ኩባንያ ጋር የ5.5 ቢሊዮን ብር ስምምነት ተፈራረመ።
ባለፈው ሳምንት በኦሮሚያ ምዕራብ ሸዋ ዞን ጊንጪ ከተማ በተደረገ ዝግጅት፣ ኬኛ የመጠጥ አክሲዮን ማኅበር ከጀርመኑ ክሮንስ ኤጅ ጋር ውል ፈጽሟል።
አክሲዮን ማኅበሩ የማሽነሪዎች ግዥና ተከላ ጨረታ ሒደት፣ የጨረታ ግምገማና የሰነድ ዝግጅትን ጨምሮ አሥር ወራት የወሰደበት መሆኑን፣ ግንባታውን ጀምሮ ለማጠናቀቅ 5.5 ቢሊዮን ብር እንደሚፈጅም አስታውቋል። በ101 ሔክታር መሬት ላይ ያረፈው ፋብሪካው ቢራ፣ ድራፍት፣ ማልት፣ ለስላሳ መጠጦች፣ ጭማቂና የታሸገ ውኃ እንደሚያመርት የኬኛ መጠጦች አክሲዮን ማኅበር አባልና የፕሮጀክቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ነዋይ መገርሳ ለሪፖርተር አስረድተዋል።
ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ ወደ ሥራ ሲገባ በዓመት ሦስት ሚሊዮን ሔክቶ ሌትር ቢራ የማምረት አቅም ይኖረዋል ተብሏል፡፡ ባለክሲዮኖችን ካሰባሰበ በኋላ ዓለም አቀፍ አማካሪ ድርጀቶችን በማፈላለግ ተጠምዶ የነበረው አክሲዮን ማኅበር፣ በተቋቋመበት በሁለተኛ ዓመቱ ከጀርመኑ ብሩቴክ ጂኤምቢኤች የሚባል ተቋም የፋብሪካውን የአዋጭነት ጥናት፣ የውኃ ቁፋሮ፣ የቢራ ፋብሪካ ተከላ፣ እንዲሁም የድራፍት አጠማመቅን እንዲያጠናለት ውል ማሰሩ ተጠቅሷል፡፡
ኩባንያው አርሶ አደሮችን ጨምሮ 5,000 ባለአክሲዮኖች እንዳሉት፣ በቂ የምርት ግብዓት ለማግኘት ከአርሶ አደሩ ጋር እየሠራ እንደሆነ አቶ ነዋይ ጠቁመዋል። ወላቡ ኮንስትራክሽን የተባለ የአገር ውስጥ ሥራ ተቋራጭ ኩባንያ የሲቪል ሥራውን ተረክቦ ፕሮጀክቱን እየገነባ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በኦሮሚያ ክልል የኢኮኖሚ አብዮቱን ከተከተሉት ኩባንያዎች አንዱ የሆነው ኬኛ በአጠቃላይ የተፈቀደለት ካፒታል ሦስት ቢሊዮን ብር ሲሆን፣ በአሁኑ ጊዜ ለፕሮጀክቱ ተጨማሪ ፋይናንስ ለማግኘት እየሠራ እንደሆነ አቶ ነዋይ አክለዋል።
የከሮንስ ኤጄ ተወካይ ዲሪክ ሀምሌንግና የኬኛ ቢራ ዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ቶሎሳ ገደፋ፣ የድርጅቱ ልዑካንና የኬኛ ቢራ ፋብሪካ አክስዮን ማኅበር የቦርድ አባላት በተገኙበት ስምምነቱ ተፈጽሟል፡፡
የቦርድ ሰብሳቢው አቶ ቶሎሳ፣ ‹‹ስምምነቱ እያንዳንዱን ዕርምጃና ሰነድ በጥልቀት በመተንተን ከረዥምና ጠንካራ ድርድር በኋላ ማሳካት ተችሏል፤›› ብለዋል፡፡
በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደተገለጸው ክሮንስ ኤጄ በዘርፉ ዕውቅናን ያተረፈ የጀርመን ኩባንያ ሲሆን፣ ግንባታውን ሙሉ በሙሉ ገንብቶ አጠናቆ ቁልፉን የማስረከብ ስምምነት መደረጉን አቶ ነዋይ አስረድተዋል፡፡
ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ መሥራት ለ3,500 ሰዎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ለኬኛ መጠጦች ብሩቴክ ጂኤምቢኤች ከተባለው ሌላ የጀርመን አማካሪ ኩባንያ በዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት የጨረታ ግዥን በመጠቀም የአዋጭነት ጥናት፣ ልማት፣ ዲዛይንና ግንባታ እንዲሁም የማሽነሪ ተከላውን ማከናወኑም ተገልጿል፡፡
በቀጣይ ክልሉ ያለውን ሀብት ዘርፍ አጢኖና ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ቀርፆ የክልሉንና የአገሪቱን ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ለማቃለል፣ በኦሮሚያ ኢኮኖሚ አብዮት ሥር ከኦሮሚያ ምሁራን በጋራ እየተወያየ እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡ በኢኮኖሚው አብዮት ሥር ያሉ ሌሎች ፕሮጀክቶች ኦዳ የተቀናጀ ትራንስፖርት፣ ኬኛ የእርሻ ማሽነሪዎች ማምረቻ፣ አኳ አምቦና ወላቡ ኮንስትራክሽን ኩባንያን ጨምሮ አምስት አክሲዮን ማኅበራት ይገኛሉ፡፡