የስድስተኛው ጠቅላላ ምርጫ ውጤት የሥርዓቱን እውነተኛ ባህሪ በተግባር መፈተንና ማጋለጥ መቻሉን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አስታወቀ፡፡ ፓርቲው ስድስተኛው ጠቅላላ ምርጫ የሥርዓቱን ዓይነተኛ ባህሪ ለመረዳትና ለማጋለጥ እንደረዳው ያስታወቀው ሰኞ ሰኔ 28 ቀን 2013 ዓ.ም. በራዲሰን ብሉ ሆቴል፣ በምርጫውና በአጠቃላይ ወቅታዊ የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታን አስመልክቶ በፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች አማካይነት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት ነው፡፡
‹‹በምርጫው ሒደት የታየው ጎደሎነትና ክፍተት ከምርጫ ውጤት አኳያ የምንመዝነው ከሆነ፣ የአገራችንን ተጨባጭ ሁኔታና የሐሳብ ብዝኃነትን የማያመላክት መሆኑን መናገር ይቻላል፤›› በማለት፣ የሐሳብ ብዝኃነትን ከማስተናገድ አንፃር ምርጫው ውስንነት እንዳለበት አብን በመግለጫው ይፋ አድርጓል፡፡
ምንም እንኳን ምርጫው የሐሳብ ብዝኃነትን ከማስተናገድ አንፃር ክፍተት እንዳለበት ቢተችም፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ግን ለሒደቱ መሳካት ‹‹አንፃራዊ አዎንታዊነት›› አሳይቷል በማለት ‹‹በቦርዱ የበላይ አመራር የታየው የገለልተኝነት፣ የግልጽነትና የፍትሐዊነት መንፈስ እንደ ተቋም የሚፈተንበት ወቅት እንደሆነም እንገነዘባለን፤›› ሲል፣ ከምርጫ ቦርድ የሚጠበቀውን ተቋማዊ ኃላፊነትንም እንዲሁ አስታውቋል፡፡
ከዚህ ባለፈ በምርጫው ዕለት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሆኖም ድምፁን የሰጠውን ሕዝብ በማመሥገን፣ የመራጩ ድምፅ እንዲከበር ተገቢውን ሰላማዊና ሕጋዊ ጥረት እንደሚያደርግና የሕዝቡንም ውሳኔ ያለ ማወላወል እንደሚቀበል አስታውቋል፡፡
ፓርቲው በተወዳደረባቸው አካባቢዎች በምርጫው ሒደት ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች በማሰባሰብና በዝርዝር ቅሬታዎቹን በመሰነድ፣ በሕግ አግባብ መፍትሔ ለመሻት ለቦርዱ ማቅረቡን አስታውቋል፡፡
ወቅታዊ የአገሪቱን ፖለቲካዊ ሁኔታና ብሔራዊ ደኅንነትን በተመለከተ ደግሞ፣ ‹‹የብልፅግና አገዛዝ የአገሪቱን፣ የዜጎችንና የመንግሥቱን ሰላም፣ ደኅንነት፣ ጥቅምና ክብር በማስጠበቅ ረገድ ጉልህ ክፍተቶች እየተስተዋሉበት ነው፤›› ሲል አብን ወቀሳ ሰንዝሯል፡፡
በዚህ መሠረት፣ ‹‹ማዕከላዊ መንግሥትና በየደረጃው ያሉ መንግሥታዊ አካላት፣ አገሪቱ ከተደቀነባት የህልውና አደጋ ለመታደግ በሚደረገው ርብርብ የራሳቸውን ሚና በግልጽ ከመወሰን አንስቶ፣ ሁሉንም ባለድርሻ አካላትን ያካተተ የብሔራዊ ደኅንነት ዕርምጃ ይወሰድ፤›› ሲልም ፓርቲው ጥሪ አቅርቧል፡፡
ከዚህ ባለፈም በትግራይ ክልል የሚገኙ ተማሪዎችንና በአጠቃላይም የትግራይን ሕዝብ ደኅነነት የማስጠበቅ ኃላፊነት እንዲወጣም አብን ለመንግሥት ጥያቄ አቅርቧል፡፡
አብን ሰኔ 3 ቀን 2010 ዓ.ም. የመመሥረቻ ጉባዔውን በባህር ዳር ከተማ በማድረግ አገር አቀፍ ፓርቲ ሆኖ የተመሠረተ የፖለቲካ ድርጅት ሲሆን፣ በዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ እስካሁን ይፋ በተደረገው ቆጠራ ሁለት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ ያገኘ የፖለቲካ ድርጅት ነው፡፡