ኢትዮጵያ የዓረብ ሊግ ጣልቃ ገብነት ከአፍሪካ ኅብረት ጋር ያለውን ግንኙነት ይጎዳል አለች
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ሁለተኛው ዓመት የውኃ ሙሌት፣ ከግድቡ ከፍታና መጨመር ጋር ተያይዞ የተፈጠረ እንደሆነ ግብፅና ሱዳን ከጅምሩ አንስቶ የሚያውቁት ጉዳይ መሆኑ ተጠቆመ።
ሪፖርተር ያነጋገራቸው አንድ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ከፍተኛ ኃላፊ እንደገለጹት፣ የግብፅና ሌሎች የውጭ ሚዳያዎች ‹‹ኢትዮጵያ የሁለተኛውን ዓመት የግድቡ የውኃ ሙሌት ማካሄድ ጀመረች›› በማለት ያስተጋቡት፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት በግድቡ አለመግባባት ላይ ሰሞኑን ውይይት እንደሚያደርግ በማሰብና የምክር ቤቱን አባላት በማሳሳት ተፅዕኖ ለማሳደር ያደረጉት እንደሆነ ጠቁመዋል።
ግብፅና ሱዳን የምሕንድስና ባለሙያዎች በግድቡ የውኃ ሙሌትና አስተዳደር ላይ ከኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች ጋር ሲያደርጉ መክረማቸውን፣ እንዲሁም የውኃ ሙሌት አተገባበሩን የተመለከቱ መረጃዎችና የግድቡ ዲዛይንን ጭምር እንደሚያውቁት ገልጸዋል።
ከዚህ በተጨማሪም በ2012 ዓ.ም. በግድቡ የተደረገው የመጀመርያ የውኃ ሙሌት በተመሳሳይ መንገድ የተያዘ መሆኑን እያወቁ ሆነ ብለው የፀጥታ ምክር ቤቱንና የአገራቸውን ሕዝብ ለማሳሳት ኢትዮጵያን ለመክሰስ እንደመረጡ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ግድቡን ለመገንባትም ሆነ፣ ውኃ ለመያዝ የማንንም ፈቃድ የመጠየቅ የሕግም ሆነ የሞራል ግዴታ እንደሌለባት ይህንንም በግልጽ ለተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ማሳወቋን የገለጹት ኃላፊው፣ የግድቡ ከፍታ እስከጨመረና ከፍተኛ የውኃ መጠን ወደ ግድቡ እስከመጣ ድረስ በግድቡ ውኃ መያዙ እንደማይቀርና ይህንንም ሁለቱም አገሮች ጠንቅቀው እንሚያውቁት አስረድተዋል።
‹‹ወደ ግድቡ የሚመጣው ውኃ ከግድቡ መውጣት ከሚችለው በላይ ከሆነ፣ ውኃ እየተያዘ እንደሆነ በግልጽ ያውቁታል። ሁለቱን የታችኛው የግድቡ ውኃ ማስወጫ አካላት (Bottom Outlet) ወደ ሥራ ከማስገባታችን አስቀድሞ ለሁለቱም አገሮች በይፋ ስናሳውቅ ምን እያደርግን እንደሆነ ግልጽ ነበር፤›› ብለዋል።
ኢትዮጵያ በዘንድሮ ዓመት የውኃ ሙሌት ላታካሂድ የምትችለው የግድቡን የመካከለኛ ክፍል ግንባታ ያላከናወነች እንደሆነ ብቻ መሆኑን ያስረዱት ኃላፊው፣ የግድቡ መካከለኛ ክፍል ግንባታ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ፍጥነት እየተከናወነ መሆኑንም አስረድተዋል።
በዘንድሮ ክረምት የሚያዘው 13 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ የውኃ መጠን ከምንጊዜውም የበለጠ እንደሆነና ይህ የውኃ መጠን ተያዘ የሚባለው የግድቡ መካከለኛ ክፍል ከፍታ ከባህር ወለል በላይ 695 ሜትር ሲደርስ መሆኑን ገልጸዋል።
ባለፈው ዓመት የግድቡ መካከለኛ ክፍል ከፍታ 665 ሜትር ላይ በመድረሱ 4.9 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ውኃ መያዙን ያስታወሱት ኃላፊው ዘንድሮ ይህንን የግድቡ መካከለኛ ክፍል ወደ 695 ሜትር ለማድረስ የተጀመረው የግንባታ ሒደት በአሁኑ ወቅት በጥሩ ሁኔታ እየሄደ መሆኑን ገልጸዋል።
እስካሁን ባለው የግንባታ ሒደት የመካከለኛው ክፍል ግንባታ ከ675 ሜትር በላይ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፣ በተያዘው ዕቅድ መሠረት እስከ ሐምሌ ወር አጋማሽ ድረስ ወደሚፈለገው 695 ሜትር ከፍታ ሊደረስ እንደሚችል ጠቁመዋል።
በግንባታው ሒደት የግድቡ ከፍታ እስከጨመረና ከፍተኛ የውኃ መጠን ወደ ግድቡ እስከመጣ ድረስ፣ ኢትዮጵያ በግድቡ ውኃ አለመያዝ እንደማትቸል ያስረዱት ኃላፊው፣ ከዚህ ውጪ ያለ ጥያቄ ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ ታቁም እንደማለት አልያም በሙሉ በግድቡ ውስጥ ያለውን ባለፈው ዓመት የተያዘውን የውኃ መጠን ጨምሮ እንድትለቅ መጠየቅ መሆኑን አስረድተዋል።
በተለይ የግብፅ መንግሥት ላይ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተቃውሞ ሠልፍ እየጠሩ መሆኑን ተከትሎ፣ የውስጥ ፖለቲካ ቀውሱን ለማርገብ የውጭ ምክንያት የመፈለግ አባዜ ውስጥ መሆኑን ያስረዱት ኃላፊው ይህ አካሄድ እንደማያዋጣ ገልጸዋል።
በተያያዘ ዜና የዓረብ ሊግ የህዳሴ ግድቡን አስመልክቶ ለተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ግብፅና ሱዳንን በመወገን ምክር ቤቱ ኢትዮጵያ የውኃ ሙሌት እንዳታካሂድ በደብዳቤ መጠየቁን፣ ኢትዮጵያ የተቃወመች ሲሆን፣ ተቃውሞዋንም ለፀጥታው ምክር ቤት በጽሑፍ አስገብታለች።
በአፍሪካ ኅብረት በተያዘ ጉዳይ ላይ የዓረብ ሊግ እያደረገ ያለው ጣልቃ ገብነት ለማንም እንደማይጠቅም ያሳወቀችው ኢትዮጵያ፣ ድርጊቱ ከኢትዮጵያ አልፎ የዓረብ ሊግን ከአፍሪካ ኅብረት ጋር ያለውን ወዳጅነት እንደሚጎዳ አሳስባለች።
የፀጥታው ምክር ቤት በዚህ ሳምንት በህዳሴ ግድቡ አለመግባባት ላይ ውይይት የሚያደርግ መሆኑ የታወቀ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ኃላፊዎችም ለዚሁ ስብሰባ ወደ አሜሪካ መሄዳቸው ታውቋል።
የፀጥታ ምክር ቤቱ የዚህ ወር ሊቀመንበር ሆና የተሰየመችው ፈረንሣይ ስትሆን፣ አገሪቱን በመወከል ምክር ቤቱን የሚመሩት በፀጥታው ምክር ቤት የፈረንሣይ አምባሳደር በግድቡ ዙሪያ የሚደረገው ውይይት፣ አገሮች ልዩነታቸውን እንዲፈቱ ከማቀራረብ ያለፈ ፋይዳ እንደማይኖረው ባለፈው ሳምንት መግለጻቸው ግብፅን አስቆጥቶ ነበር።
ግብፅና ሱዳን የፀጥታው ምክር ቤትን አሳስተውም ቢሆን የሚፈልጉት ስምምነት ላይ ሳይደረስ ኢትዮጵያ ሁለተኛውን ዓመት ሙሌት እንዳትይዝ እንዲወሰን ለማድረግ እንደሆነ ያነጋገርናቸው ኃላፊ የገለጹ ሲሆን፣ ይህ ይሆናል ብለው እንደማይገምቱም ተናግረዋል።