- Advertisement -

​​​​​​​ይድረስ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር

በፀጋ ቁምላቸው

በአገራችን ከነበረውና ካለው ተሞክሮ አኳያ በርካታ የአገራችን ምሁራንና ተቆርቋሪ ግለሰቦች በዚህና መሰል የአገራችን ጋዜጦች ላይ የሚያሳስቧቸውን፣ የሚያስጨንቋቸውንና ዕረፍት የሚነሷቸውን የአገር አንገብጋቢ ችግሮች ሲጽፉ፣ መፍትሔ እንዲፈለግላቸው ሲያሳስቡ፣ የመጨረሻ ውጤታቸውም አገርንና ወገንን እንደሚጎዳ ሲያስጠነቅቁ፣ ለሰላማችንና ለዕድገታችንም መሰናክል ሆነው እንደሚኖሩ፣ አገሪቱንም ከዘመኑ የዓለም ሒደት ጋር እያጣረሱ ዘወትር ‹‹ባለህበት ሂድ›› ዓይነት ጉዞ ላይ ይዘዋት እንደሚዘልቁ ደግመው ደጋግመው ሲያሳስቡ፣ በአንፃሩ ገንቢና መልካም ነገሮችንና ሒደቶችንም እያነሱ ሲያወድሱና ሲያበረታቱ ኖረዋል፡፡ ከጥቂት ጊዜ ወዲህም ጥቂቶቹ ለእርስዎ ‹‹ይድረስ›› እያሉ ሲጽፉ እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡ እኔም ለዓመታት በውስጤ ሲብሰለሰል ለቆየው አገራዊ ምልከታና ለጠነከረ ግላዊ ጭንቀቴ ምንም መፍትሔ ስላጣሁ፣ እነሆ ዛሬ ይድረስ ለእርስዎ ለማለት ወሰንኩ፡፡

ይህች እናት አገራችን ወትሮም ሆነ አሁን ምርጥና እጅግ ላቅ ያለ ሰብዕና የነበራቸውንና ያላቸውን ልጆቿን ስታፈራ ኖራለች፡፡ እነዚያ የአገርና የወገን ልዩ ፍቅር ተዋህዷቸው የተፈጠሩ ግለሰቦች በሕይወት ዘመናቸው ለአገርና ለወገን እጅግ ላቅ ያለ አገልግሎት አበርክተውና እጅግ የሚያኮራ ተግባር ፈጽመው ያልፋሉ፡፡ እንዳለፉት እንደ እነዚያ በርካታ ጀግኖቻችን አይሁን እንጂ ጥቂቶች አሁንም አሉን፡፡

ታዲያ እነዚያ አኩሪ ጀግኖቻችንም ሆኑ አሁን ያሉን ልሂቃን በሕይወት ዘመናቸው ማንነታቸው በሚገባ ሳይታወቅ፣ ወገናቸው ሳይረዳቸው ይቆዩና ስለእነሱ ማንነትና እንዴትነት የሚወሳው በሕልፈተ ሕይወታቸው ጊዜ ብቻ ይሆናል፡፡ ያውም ለአንድ ሳምንት ብቻ፡፡ እናም ያ የሳምንት ርብርቦሽም ቀስ እያለ ወዲያውኑ ሲከስም ይታያል፡፡ ይህ ለዘመናት ያየሁት ሒደት ነው፡፡ ከጥቂት ጊዜ ወዲህ ግን በአርቲስቶቻችን አካባቢ የሚታየው የተሻለ ድርጊት በመጠኑም ቢሆን የሚያፅናና ሆኗል፡፡ ከቀብር ሳምንት የሚሻገር የሟች ማስታወሻዎችን ሲሞካክሩ ይታያልና፡፡

በበኩሌ የሰው ልጅ ላቅና ለየት ያለ ባለ ክህሎት፣ ጀግንነትም ሆነ ምጡቅ በሆነ ሰብዕና ለእናት አገሩና ለወገኑ እጅግ ለየት ያለ አበርክቶ ከታየበት፣ ያ ሰው በሕይወት ዘመኑ ሊመሠገንና ሊወደስ፣ ማንነቱንም ወገኑ በሚገባ እንዲገነዘበው ሊደረግ ይገባል እላለሁ፡፡ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም ሌሎች አገሮች እንደሚያደርጉት ሁሉ ተከታታይ ትውልዶች ስለዚያ ሰው ማንነትና ምንነት አውቀው እንዲኖሩ፣ ከሕልፈተ ሕይወቱ በኋላም መታሰቢያ ሐውልቶችንና (ቤተሰብ ከሚያስቀምጠው አነስተኛ የቀብር ሐውልት ውጪ ማለቴ ነው) መሰል መታሰቢያዎችና ማስታወሻዎች ሊቆሙለት ይገባል የሚል ፅኑ እምነት አለኝ፡፡

ዛሬ ይህን ጽሑፍ ይድረስ ለእርስዎ ብዬ ለማለት የወሰንኩትም፣ ለዓመታት በዚህ ዓብይ ጉዳይ ላይ ሲቆረቁረኝ የቆየ ጉዳይ ስላለ ነው፡፡

- Advertisement -

የጽሑፉ አቅራቢ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ‹‹የስፖርት ፕሮግራም ዋና አዘጋጅ›› በመሆን ለበርካታ ዓመታት ሳገለግል ቆይቻለሁ፡፡ በዚህ የአገልግሎት ዘመኔም የአገራችንን የስፖርት አጀማመር፣ ሒደትና የነበረበትንም ሆነ አሁን የደረሰበትን ደረጃ በሚገባ የማውቅ ይመስለኛል፡፡ በዚሁ መንገድም የአገሪቱን ስፖርት መሥሪያ ቤቱንና የአመራር ባለሥልጣናቱንም የማወቅ ዕድሉ ከሞላ ጎደል አጋጥሞኛል፡፡

ከዚህ አኳያም ለአገራቸው ቀርቶ ለአኅጉራቸው አፍሪካና ለመላው ዓለም ስፖርት ክንውን የላቀ አስተዋጽኦ አበርክተው ያለፉትን የምንጊዜም መኩሪያችንን ክቡር አቶ ይድነቃቸው ተሰማን፣ በቅርበትና በሚገባ ጠንቅቄ ለማወቅ ዕድሉን ያገኘሁ ነበርኩ፡፡ ክቡር አቶ ይድነቃቸው ተሰማ ቀደም ሲል (በወጣትነት ዘመናቸው) ለቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ከዚያም ለብሔራዊ ቡድን ሲጫወቱ የቆዩ ሲሆን፣ ወደ ሥራ ዓለም ሲገቡም በትምህርት ሚኒስቴርና በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች አገልግለዋል፡፡

ይሁን እንጂ በእነዚህ ጥቂት ዓመታት በፅኑ የስፖርት ፍቅር የተነደፈው የይድነቃቸው ተሰማ ልቦና ዕረፍት አላገኘም ነበር፡፡ በመሆኑም በወቅቱ ወደነበሩት በርካታ ባለሥልጣናት እየቀረቡ ያቀዱትን አጀንዳ በተግባር በመተርጎም የሌት ተቀን ጥረታቸውን ቀጠሉ፡፡ ከልብ ጥረት ከተደረገ ደግሞ በተግባር የማይተረጎም ህልም የለምና እሳቸውም የደከሙበትን ጥረት አሳክተው፣ በ1936 ዓ.ም. በስምንት ብር በተከራዩዋት እጅግ አነስተኛ ክፍል የመጀመርያውን የአገሪቱን የስፖርት ጽሕፈት ቤት አንድ ረዳት ብቻ ይዘው ይጀምራሉ፡፡

እነሆ በዚያ ሁኔታ የተጀመረው የአገሪቱ የስፖርት መሥሪያ ቤትም በዘመናት ሒደት አሁን ካለበት ደረጃ የደረሰ ሲሆን፣ በየጊዜው የተቋቋሙት ፌዴሬሽኖቻችንም እንደ ዕድገቶቻቸው በአኅጉርና በዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ውድድሮች መሳተፋቸውን ጀምረው ግንባር ቀደም በሆነው የአትሌቲክስ ውጤታችን፣ የእናት አገራችንን ስም የዓለም ኅብረተሰብ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲሰማውና እንዲያውቀው ለማድረግ ተቻለ፡፡

ክቡር አቶ ይድነቃቸው ተሰማ ከ40 ዓመታት በላይ በቆየው አገልግሎታቸው የአገራችንን ስፖርት በዋና ዳይሬክተርነት፣ በረዳት ሚኒስትርነት፣ በምክትል ሚኒስትርነትና በመጨረሻም በኮሚሽነርነት ሲያገለግሉ የኖሩ ነበሩ፡፡ ከአገራቸው ባሻገርም በየጊዜው ለአፍሪካና ለዓለም ስፖርቶች መሪነት በመመረጥ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት፣ የአፍሪካ ስፖርት ኮንፌዴሬሽኖች ማኅበር ፕሬዚዳንት፣ የአፍሪካ ብሔራዊ ኦሎምፒክ ኮሚቴዎች ማኅበር የክብር ሊቀመንበር፣ የአፍሪካ ስፖርት የበላይ ምክር ቤት የቋሚ ኮሚቴ አባል፣ የኢንተርናሽናል ኦሎምፒክ ኮሚቴ (IOC) አባልና የዓለም እግር ኳስ ፌዴሬሽን (FIFA) አባል በመሆን፣ በተለይም በሁለቱ አንጋፋ የዓለም ስፖርት ማኅበራት ውስጥ የተለያዩ ንዑሳን ኮሚቴዎችን ሲመሩ የነበሩና እጅግ የላቀ ሰብዕና የተላበሱ መኩሪያችን ነበሩ፡፡

ስለሆነም በሕልፈተ ሕይወታቸው ወቅት ከመላው ዓለም የጎረፈውን የሐዘን መግለጫ የማንነታቸው ምስክርነት ሊሆን የቻለ ነበር፡፡ በተለይም ታዋቂው የኮትዲቯሩ የሥነ ጽሑፍ ሰው የላኩት እንጉርጉሮ ብዙዎቻችንን ለወራት ሲያስለቅሰን ቆይቷል፡፡

‹‹እናልቅስ አፍሪካውያን ወንድሞች፣

አዲስ መከራ አኅጉራችንን መትቷታል፣

አባችን ተሰማ አብቅቷል፣

አሳዛኝ እውነት፣

ጥሩው የአፍሪካ ስፖርት ደቀ መዝሙር በ66 ዓመቱ አልፏል››፣

ወዘተ.

የሚገርመው ደግሞ በሕይወት ከነበሩበት ጊዜ ጀምሮ ሞሮኮ ካዛብላንካ ውስጥ ለእኚያ ታላቅ ሰው ከፍተኛው ስታዲየም በስማቸው ተሰይሞ የኖረ ሲሆን፣ እንዲህ ሲያኮሩን ለቆዩት ሰው በአገራቸው ግን ‹‹ለእነ አቶ አብነት ገብረ መስቀል ምሥጋና ይድረሳቸውና በቢሾፍቱ የሚገኘውን የወጣቶች ስፖርት አካዴሚ በአቶ ይድነቃቸው ስም ከመሰየማቸው በስተቀር››፣ በመንግሥት በኩል ታስቦበት ለእሳቸው መታሰቢያ በስማቸው የተሰየመ ነገር አለመኖሩ የብዙዎቻችንን ልቦና ሰብሮት ይኖራል፡፡ የስፖርት ቤተሰቡም ሕመም ሆኖ ቆይቷል፡፡

በዚህ በኩል የአገሪቱን ስፖርት የበላይነት የሚመራው የስፖርት ኮሚሽናችንን በየጊዜው በኃላፊነት ሲመሩ የቆዩት ባለሥልጣናት ላይም ሁኔታው ጣት ሲያስጠቁም ቆይቷል፡፡

የሚገርመው ደግሞ በአሁኑ ጊዜ በአገራችን ከፊል ክልሎች በርከት ያሉ (ኢንተርናሽናል) ውድድሮችን ሊያስተናግዱ የሚችሉ ስታዲየሞች ተሠርተው እያሉ፣ አንዱም እንኳ በእሳቸው ስም እንዲሰየም አለመወሰኑ የስፖርት ቤተሰቡን ቅስም ሰብሮት ቆይቷል፡፡ ዛሬ እኔ ይህንን ደብዳቤዬን ይድረስ ብዬ ለክቡርነትዎ ልጽፍ የወደድኩትም የግሌን ፅኑ ምኞት ብቻ በመያዝ ሳይሆን፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠረውን የአገራችንን ስፖርት አፍቃሪ የዓመታት ቅሬታ አንግቤ ይህንን የብዙዎችን ፅኑ ምኞትንም በማካተት ለክቡርነትዎ አቤት ለማለት ነው፡፡

የአቶ ይድነቃቸው ተሰማን ማንነትና እንዴትነት በሚገባ ጠንቅቀው እንደሚያውቁት አልጠራጠርም፡፡ ክብር ፕሬዚዳንትነት ሳህለ ወርቅ ዘውዴ ደግሞ በቅርበት የሚያውቁት ሀቅ እንደሆነ በእርግጠኝነት እናገራለሁ፡፡

በመሆኑም ከረዥም ጊዜ ጀምሮ ይሠራል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረውና ሥራው ከተጀመረ በኋላም ለተወሰነ ጊዜ ግንባታው ተቋርጦ የቆየው በአዲስ አበባ እየተገነባ የሚገኘው አዲሱ ስታዲየም አሁን ወደ ፍፃሜው እየተቃረበ ስለሆነ፣ ‹‹አደይ አበባ ስታዲየም›› የሚለው ስያሜ ተለውጦ ብርቅዬና ድንቅ የኢትዮጵያ ልጅ በነበሩት ሰው ስም ‹‹ይድነቃቸው ተሰማ ስታዲየም›› ተብሎ ቢሰየም፣ እውነቴን ነው የምልዎ የሚሊዮኖች የረዥም ጊዜ ምኞት ተሳካ ማለት ይሆናል፡፡ ይህም ሁኔታ አንዱን የአገራችንን አጉል ልማድ አርሞና አስተካክሎ የወደፊቱን ጉዞም በእጅጉ ሊለውጠው ይችላል፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው እናት አገራችን በአደይ አበባ የተሞላችና በአበቦች አብባ የምትኖር ናት፡፡ በተለይ ደግሞ በየዓመቱ መስከረም፣ ጥቅምትና ኅዳር ወራት በመጡ ቁጥር መላው የአገራችን አካባቢ በአደይ አበባ አምሮና ተውቦ የብዙዎቻችንም ልቦና በዚያ ውብ ምልክታ ረክቶና ፈክቶ እነዚያን ወራት ያሳልፋል፡፡ እናም ተፈጥሮ ያደለችንን ፀጋ በየዓመቱ እየረካንበት የምንኖር እስከሆነ ድረስ፣ ይህ ስታዲየም ግን በሁሉም መልኩ በእኚያ ምንጊዜም በማንረሳቸው በታላቁ ሰው ስም ቢሰየም ከእኛ በዘለለ የዓለምን ትኩረት ይስባል፡፡ በሚመረቅበት ጊዜም ይህንን ስያሜ ቢቀዳጅ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የዘለዓለም ኩራት ይሆናልና ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ከልብ አስበውት እዚያ ውሳኔ ላይ እንዲደረስ ቢደረግ እያልኩ ልባዊ የአክብሮት ማሳሰቢያዬን አቀርባለሁ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የስፖርት ፕሮግራም ዋና አዘጋጅ የነበሩ ሲሆን፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

- Advertisement -

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን

ከ ተመሳሳይ አምዶች

የኢትዮጵያ ልሂቃን የፖለቲካ ባህል ከዕልቂትና ከውድመት አዙሪት እንዴት እንውጣ?

(የመጨረሻ ክፍል) በሰለሞን ኃይለ ማርያም (ዶ/ር) ባለፈው ሳምንት ጽሑፌ ስለፖለቲካ ባህል ጽንሰ ሐሳብ፣ ከኢትዮጵያ የልሂቃን የፖለቲካ ባህል ውስጥ ስም ማጥፋትን፣ ተቀናቃኝን ማጥቃትንና የመደራደርና የሰጥቶ መቀበል ባህል...

የኢትዮጵያ ልሂቃን የፖለቲካ ባህል

ከዕልቂትና ከውድመት አዙሪት እንዴት እንውጣ? በሰለሞን ኃይለ ማርያም (ዶ/ር) መግቢያ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ባህል በኢትዮጵያ አጠቃላይ ዕድገት ላይ ምን ያህል በጎ ያልሆነ ተፅዕኖ እንዳሳደረና ይህም...

አሳዛኙ የግብይት ሥርዓታችን ገመና ሲፈተሽ

በእንግዳ መኮ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን በብዙ ፈተና፣ መከራና ውጣ ውረድ ውስጥ ስለመሆናቸው ማንም በቀላሉ የሚረዳው እውነት ነው፡፡ የዓለሙን ሁኔታ እንተወውና በአገራችን የተፈጠረው የሰላም መደፍረስና የፖለቲካ አለመረጋጋት፣...

የኢትዮጵያን ትንሳዔ ለማብሰርና ለመከወን ምን እናድርግ?

በጌታነህ አማረ ኢትዮጵያ ማለት ታላቅ አገር ቀደምት የሰው ዘር መገኛና የሥልጣኔ ባለቤት የሆነች አገር እንደነበረች ታሪክ ሲያወሳን ይኖራል። በዚያውም ልክ ይህች ታላቅ ነበረች የምትባል አገር...

አሸናፊና ተሸናፊ የሌለበት ትንቅንቅ ማብቂያው መቼ ይሆን?

በናኦድ አባተ በአውሮፓውያን ዘንድ በስፋት የሚታወቀው “A House Divided Against Itself Cannot Stand.” (እርስ በርሱ የተከፋፈለ ቤት አይቆምም) አባባል ትልቅ መልዕክት አለው፡፡ ኢትዮጵያውያንም በታሪክ አጋጣሚ...

የሐረሪን ክልል በኦሮሚያ የመጠቅለል ዕሳቤ ፌዴራላዊ ሥርዓትን ማፍረስ ወይስ መገንባት?

በኑረዲን አብደላ በቅርቡ ለአገራዊ የምክክር ኮሚሽን የቀረበው የሐረሪን ክልል በኦሮሚያ የመጠቅለል አጀንዳ የነባር ሕዝቦችንና የብሔር ብሔረሰቦች የራስን ዕድል በራስ የማስተዳደር ሕገ መንግሥታዊ መብትን የሚፃረር፣ በምሥራቅ...

አዳዲስ ጽሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የካቢኔ አባል የሆነ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ ስልክ ደውሎላቸው ሰሞኑን በተካሄደው ድርጅታዊ ጉባዔ ዙሪያ እያወሩ ነው]

ሰላም ክቡር ሚኒስትር፡፡ ሰላም ሰላም፣ እንዴት ነህ? ቢዘገይም እንኳን አደረስዎት ክቡር ሚኒስትር። ለምኑ? ለፓርቲዎ ሁለተኛ መደበኛ ጉባዔ እንኳን አደረስዎት ማለቴ ነው። ቆየ እኮ ከተጠናቀቀ? አስቀድሜ ቢዘገይም ያልኩት እኮ ለዚያ ነው...

የጋዛ ውዝግብ በአፍሪካ ቀንድ ላይ የደቀነው ሥጋት

የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አማችና የቀድሞ የመካከለኛው ምሥራቅ የፖሊሲ አማካሪያቸው ጄርድ ኩሽነር፣ ከአሥር ወራት በፊት ነበር ፍልስጤሞችን ከጋዛ አንስቶ ሌላ ቦታ ስለማስፈር በይፋ ሲናገር...

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በውክልና ለግሉ ዘርፍ ለማስተላለፍ ያቀዳቸው አገልግሎቶች

የከተማው አስተዳደር ካቢኔ ሰሞኑን ባሳለፈው ውሳኔ የተመረጡ መንግሥታዊ አገልግሎቶችን በሦስተኛ ወገን ለማሠራት የሚያስችለውን ደንብ በማፅደቅ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩ ታውቋል፡፡  አስተዳደሩ ደንቡን ከማጽደቁ አስቀድሞ በሦስተኛ ወገን...

የተገራ ስሜት!

እነሆ መንገድ ከስታዲዮም ወደ ጦር ኃይሎች። በጥበቃ የተገኘ ለበርካታ ዓመታት ያገለገለ ሚኒ ባስ ታክሲ ውስጥ ተሳፍረናል፡፡ ምሁር መሳይ ተሳፋሪ አጠገቡ ለተቀመጠ የዕድሜ እኩያው ማብራሪያ...

የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ አውጪዎች ችግር የት ጋ ነው ያለው?

በጌታነህ አማረ የአንድን አገር ኢኮኖሚ ችግር ለመፍታት መጀመሪያ ቁልፍ የሆነውን ነገር መረዳት በጣም ጠቃሚ  ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ቁልፍ ነገር ተብሎ የሚጠራው ‹‹ተርኒንግ ፖይንት›› ነው፡፡...

ፈተና የበዛበት አመጋገብ እንዴት ይፈታ?

አቶ አብነት ተክሌ የሥነ ምግብ ባለሙያ ሲሆን የመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪውን ምግብና ምግብ ነክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ትኩረቱን አድርጎ ነው ያጠናው፡፡ በመጀመሪያ ዲግሪው በሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ...
[the_ad id="124766"]

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን