በትግራይ ክልል የሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ታጣቂዎች ወደ መጠለያ ካምፖች በመግባት ቢያንሰ ስድስት ኤርትራዊያን ስደተኞች መገደላቸውን የስደተኞችና ከስድት ተመላሾች ጉዳይ ኤጀንሲ አስታወቀ፡፡
ኤጀንሲው ሐሙስ ሐምሌ 15 ቀን 2013 ዓ.ም. ለሪፖርተር በላከው መግለጫው የሕወሓት ታጣቂዎች በማፀምሪ የሚገኙ የኤርትራ ስደተኞችን የገደሉት ስደተኞች ወደሚገኙበት ካምፕ በቀጥታ በመግባታ መሆኑን መረጃ እንደደረሰው አስታውቋል፡፡
በአሁኑ ጊዜም ዓለም ዓቀፉን የሰብዓዊ መብት ሕግ በመጣስ የሕወሓት ታጣቂዎች በስደተኛ መጠለያዎች ውስጥ ከባድ መሣሪያዎችን እንደሚተኩሱና ቀጣይነት ያለው እንቅስቃሴ በማድረግ በቦታውም አልፎ አልፎ የተኩስ ጩኸት እንደሚሰማ ገልጿል፡፡
በተጨማሪም ለሰብዓዊ አገልግሎት የተዘጋጁ የተቋሙ ጤና ጣቢዎችን ጨምሮ አንቡላንሶችና መሠረተ ልማቶች ለወታደራዊ አገልግሎት እየዋሉ እንደሆነ የኤጀንሲው መግለጫ አመላክቷል፡፡
የጤና መሠረተ ልማቶችን ሕወሓት በመቆጣጠሩ ምክንያት ቢያንስ ሁለት የኤርትራ ስደተኞች በጤና አገልግሎት እጥረት መሞታቸውንና በካምፑ የሚኖሩ እናቶችም አስጊ በሆነ የጤና ሁኔታ መኖራቸውን የተቋሙ መግለጫ ያመላክታል፡፡
በካምፕ የሚገኙ ስደተኞች ሕወሓት እያስገደደ ለጦርነቱ የሚውል የዓይነትና የገንዘብ መዋጮ እያስገደደ እንደሚያስከፍላቸው በመግለጫው ተጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል ስደተኞች ከካምፕና ከጦርነቱ አካባቢ ለመልቀቅ የሚያደርጉት ጥረት በሕወሓት ታጣቂዎች እንደሚከለከሉና አኗኗራቸውም ከእገታ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ሕይወት ነው ሲል ጠቁሟል፡፡
የኤጀንሲው መግለጫ እንደሚያሳየው ስደተኞች በጅምላ ወደአልታወቀ ቦታዎች በኃይል እንደተወሰዱ የተወሰኑት ደግሞ በኅዳር ወር መጀመርያ ግጭቱ መከሰቱን ተከትሎ በሕወሓት ታጣቂዎች ጥቃት ደርሶባቸው ወደተዘጉት ሕፃና ሸመልባ የተባሉ መጠለያ ጣቢያዎች እንዲዛወሩ መደረጋቸውን አስታውቋል፡፡
በአሁኑ ጊዜ የትኛውም ዓለም አቀፍ የግብረ ሰናይ ድርጅት ማይፀምሪ ወደሚገኙት የስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎች መግባትም ሆነ ለስደተኞች አገልግሎት ማቅረብ እንዳልቻለ በመግለጫው ተመላክቷል፡፡
ኤጀንሲው የኢትዮጵያ መንግሥት የስደተኞችን ደኅንነት ለመጠበቅ እያደረገ ያለውን ጥረት በመደገፍ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የተፈጸሙትን በጭካኔ የተሞሉ ወንጀሎችን እንዲያወግዝ ሲል ጥሪ አቅርቧል፡፡ በተጨማሪም ስደተኞችን ከእገታ ለመታደግ ጥረት እንዲያደርግና በስደተኞች ላይ የተፈጸሙ ወንጀሎችን ለማጣራት የዓለም አቀፉን ማኅበረሰብ ዕገዛ ጠይቋል፡፡