Sunday, March 26, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊ​​​​​​​የሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ እንዲጎለብት ጥሪ ቀረበ

​​​​​​​የሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ እንዲጎለብት ጥሪ ቀረበ

ቀን:

ሴቶች በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚና በማኅበራዊ ጉዳዮች ተሳትፏቸው የጎላ እንዲሆን መንግሥትም ሆነ ሌሎች ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ ቀረበ፡፡

ጥሪው የቀረበው ማክሰኞ ሐምሌ 20 ቀን 2013 ዓ.ም. አክሽን ፎር ሶሻል ዴቨሎፕመንት ኤንድ ኢንቫይሮመንታል ፕሮቴክሽን ኦርጋናይዜሸን ከተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ዕጩ ተወዳዳሪ ከነበሩና ከሌሎች ተቋማት ኃላፊዎችና ተወካዮች ጋር ስለ ጉዳዩ በጋራ ውይይት ባደረገበት ወቅት ነው፡፡

በአሁኑ ወቅት በፖለቲካዊ ጉዳዮች ተሳትፈው እየሠሩ የሚገኙ ሴቶች ጉዳዩን ምን ያህል አውቀው እንደገቡና ከገቡስ በኋላ ያላቸውን አቅም እየተጠቀሙበት ነው ወይ? የሚለውን ለማወቅ መንግሥት መፈተሽ እንዳለበት የጥናት አቅራቢና አማካሪ የሆኑት ወ/ሮ ፍቅር ሽፈራሁ አስረድተዋል፡፡

ሴቶች በፖለቲካ ጉዳዮች ላይ ያላቸው ተሳትፎ አነስተኛ መሆኑን የገለጹት ጥናት አቅራቢዋ፣ ይህም የሆነበት ዋነኛ ምክንያት ለሴቶች የሚሰጠው ግምት የተሳሳተ በመሆኑና መንግሥትም በሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ ላይ ተገቢውን ትኩረት ሰጥቶ ባለመሥራቱ ጭምር እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

አሁን ላይ ባለው ሁኔታ ሴቶች በፖለቲካ ላይ የመሳተፍ አቅማቸው 38 በመቶ እንደደረሰ ከበፊቱ ጋር ሲነፃፀርም ትልቅ ልዩነት እንዳሳየ ገልጸው፣ ይኼም አመርቂ ውጤት የሚባል አይደለም ሲሉ አማካሪዋ ተናግረዋል፡፡

በተለይም በክልሎች ላይ ኑሯቸውን ያደረጉ ሴቶች በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካም ሆነ በማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ተሳትፏቸው ደካማ የሚባል መሆኑን በተለያየ ጊዜ የተደረጉ ጥናቶች እንደሚያመለክቱ አክለዋል፡፡

ከ2008 ዓ.ም. እስከ 2010 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ የሴቶች ተሳትፎ የተሻለ እንደነበር ያስታወሱት ወ/ሮ ፍቅር፣ ይህንንም ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሳደግ መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡

ሴቶች በፖለቲካ ላይ ያላቸው ተሳትፎ ጎላ ብለው ያልታዩበት ዋናው ምክንያት በቤተሰቦቻቸው ጫና ስለሚደርስባቸው ነው ያሉት የኢዜማ ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ገነት አራጌ ናቸው፡፡

ከጥንት ጀምሮ ሲካሄድ የቆየ የፖለቲካ ምኅዳር የሴቶች ተሳትፎ ላይ ያላተኮረ መሆኑን የገለጹት ሥራ አስፈጻሚዋ፣ ከመንግሥት ጣልቃ ገብነት የወጣ መዋቅር በመዘርጋት የሴቶችን ተሳትፎ ማጉላት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፡፡

በተለይም በፖለቲካ ተሳትፎ ላይ የሴቶች ሚና እምብዛም እንደሆነ ይህንንም ለመቅረፍ መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንዳለበት ወ/ሮ ገነት አስረድተዋል፡፡

የባልደራስ ፓርቲ ዕጩ ተወዳዳሪ የነበሩት ወ/ሮ ምንታምር ላቀው እንደገለጹት፣ ሴቶች በፖለቲካ ተሳትፎ ላይ ያላቸው ሚና ምን እንደሚመስል ለማወቅ በቂ የሚባል ጥናት እንዳልተደረገና ያላቸውም ተሳትፎ ደካማ የሚባል ነው፡፡

በገጠር አካባቢ ኑሯቸውን ያደረጉ ሴቶች በአገሪቷ ጉዳዮች ላይ እንዲሳተፉ ለማስቻል እንዲሁም ያላቸውን አቅም አውጥተው እንዲሠሩ ለማድረግ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩሉን ሚና ሊጫወት እንደሚገባ ወ/ሮ ምንታምር ገልጸዋል፡፡

ሴቶች ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ እንዲሳተፉና ያላቸውን አቅም እንዲያሳድጉ ለማድረግ መንግሥት የአንበሳውን ድርሻ መወጣት እንዳለበት በውይይቱ ላይ ተነስቷል፡፡

አክሽን ፎር ሶሻል ዴቨሎፕመንት ኤንድ ኢንቫይሮመንታል ፕሮቴክሽን ኦርጋናይዜሸን ሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ ላይ ትኩረት ያደረገ ፕሮጀክት እየሠራ  ይገኛል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...