የፍርድ ቤት ዳኞች በአብዛኛው የሚያገኟቸው ሥልጠናዎች ሥራ ሊጀምሩ ሲሉ የሚሳተፉባቸው በመሆናቸው፣ ሥልጠናዎቹ ወጥነት ኖሯቸው ይሰጡ ዘንድ የዳኝነት ሥልጠና ስትራቴጂ በአጭር ጊዜ ተቀርፆ ወደ ተግባር መገባት እንዳለበት ተገለጸ፡፡
የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም (UNDP) ጋር በመሆን እየተገበረ ያለው የፍርድ ቤቶች ማሻሻያ ፕሮጀክት አንዱ አካል የሆነው የዳኝነት ሥልጠና ሥርዓት ላይ ያተኮረ የዳሰሳ ጥናት ውጤት፣ ዓርብ ሐምሌ 30 ቀን 2013 ዓ.ም. የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አመራሮችና የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በቤስት ዌስተርን አዲስ ሆቴል በተዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ቀርቧል፡፡
በውይይት መድረኩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ሰለሞን አረዳ እንዳስታወቁት፣ የዳኝነት ሥርዓቱን ለማዘመን የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የሦስት ዓመት የሪፎርም ዕቅድ ተዘጋጅቷል፡፡ ዕቅዱ በዋናነት የዳኝነት ዘርፍን ለማዘመን፣ አሠራሩን ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ አዳዲስ ሕጎችን ከማውጣት ጀምሮ የተለያዩ መመርያዎችንና ደንቦችን የማዘጋጀት ሰፊ ሥራ እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
የዳኞች ሥልጠና ሥርዓትን ማጠናከር አንዱ እየተሠራበት ያለ ጉዳይ እንደሆነ ያስታወቁት ምክትል ፕሬዚዳንቱ፣ የዳኞች ዕውቀትና ክህሎት በየዕለቱ በመዝገቦች እንደመፈተኑ በሙያቸው ብቁ ሆነው ዘመኑ የሚጠይቀውን ዕውቀት ተክነው መገኘት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
በተለይም ወጣት ዳኞች በፍርድ ቤት ሥራ ሲጀምሩ ከዕውቀታቸው በተጨማሪ በቂ ክህሎትና የተሟላ ሰብዕና እንዲኖራቸው ለማስቻል በበቂ ሥልጠና ውስጥ እንዲያልፉ ማድረጉ አስፈላጊ እንደሆነ ጠቁመው፣ ሥልጠና መውሰድ የዳኞች መብት ሳይሆን ግዴታም እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡
የፌዴራል ዳኞች የሥልጠና ሥርዓት የዳሰሳ ጥናት ረቂቁን ያቀረቡት የአጥኚ ቡድኑ ከፍተኛ አማካሪ አቶ ዘካርያስ ፋሲል ስለጥናቱ አስፈላጊነት ሲገልጹ፣ በኢትዮጵያ እስካሁን በነበረው ሁኔታ መገንዘብ እንደተቻለው ዳኞች በአብዛኛው የሚያገኟቸው ሥልጠናዎች ሥራ ሊጀምሩ ሲሉ የሚሳተፉባቸው የቅድመ ሥራና የሥራ ላይ ሥልጠና መርሐ ግብሮች ሥልጠናዎች ናቸው ብለዋል፡፡ ሁሉም ሥልጠናዎች ወጥነት የሌላቸውና አንዳንዴም በቂ እንዳልነበሩ አስታውሰው፣ ዳኞች ሥራ ሊጀምሩ ሲል ሥልጠና የሚሰጠው የፌዴራል የሕግና የፍትሕ ምርምርና ሥልጠና ኢንስቲትዩት በመሆኑ ሥልጠናውም አስገዳጅ እንዳልሆነ ገልጸዋል፡፡
ከፍተኛ አማካሪው እንደገለጹት፣ ጥራት ያለው የዳኝነት አገልግሎት መስጠት የሚቻለው ፍርድ ቤቶች በዋነኛነት ከፍተኛ ሙያዊ ብቃት ባላቸው የሰው ኃይል መደራጀት ሲችሉ ነው፡፡ የዳኝነት ሥርዓቱን ቀልጣፋ፣ ውጤታማና ዘመናዊ ማድረግ የሚቻለው ዳኞች ቀጣይነትና አስተማማኝነት ባለው ሥልጠና ማብቃት ሲቻል እንደሆነ ገልጸው፣ ይህ ሥራ ሰፊና ቀጣይነት ያለው ከመሆኑ አንፃር በአግባቡ የተደራጀና ተልዕኮውን በባለቤትነት ተቀብሎ በሙያዊና በዘመናዊ አስተሳሰብ፣ በአሠራርና አደረጃጀት የሚመራ አካል ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡
በጥናት ቡድኑ ተባባሪ አማካሪ የሆኑት አቶ ዮናስ መስፍን እንደገለጹት፣ የዳኝነት ሥልጠና ፕሮግራሞችን ለመምራትና ለመተግበር የአጭርና የረዥም ጊዜ የሥልጠና ሥልትና ዕቅድ በመቅረፅ መመራት እንዳለበት የብዙ አገሮች ልምድ ያሳያል፡፡ የዳኝነትና የሥልጠና ስትራቴጂ የአገሪቱን የቀደመ፣ ነባራዊና ቀጣይ ሁኔታዎችን በማጥናትና በመረዳት፣ የፍርድ ቤቶችን ስትራቴጂካዊ ግቦች በማገናዘብ፣ ያለውን ሀብትና አቅም በማቀናጀትና ያሉትን ተቋማዊና መዋቅራዊ አደረጃጀቶች በመፈተሽ ከዳኝነት አካሉ አሁናዊና የወደፊት የብቃትና አፈጻጸም ደረጃ ጋር በማመዛዘን የሚነደፍ እንደሆነም አማካሪው አስረድተዋል፡፡
ስትራቴጂ ይዘጋጅ ሲባል የዳኝነት ሥልጠናው በምን ጉዳዮች ላይ ትኩረት መስጠት እንዳለበት፣ በማንና እንዴት መሰጠት እንዳለበት፣ ለማን፣ መቼና ለምን ያህል ጊዜ መሰጠት እንዳለበት የሚመልስ መሆን እንደሚገባው በጥናቱ ተመላክቷል፡፡
ላለፉት ሃያ ዓመታት ከፍትሕና ከፍርድ ቤቶች ማሻሻያ ፕሮግራሞች ትግበራ ጋር ተያይዞ፣ የፍትሕ አካላት ሥልጠና ሕጋዊና ተቋማዊ መዋቅር ኖሮት እንዲመራ ተደርጎ ሲሠራበት መቆየቱ ተገልጿል፡፡ የፍትሕ አካላት ባለሙያዎች ማሠልጠኛ ተቋማት በፌዴራልና በክልል ደረጃ ተቋቋመው በቅድመ ሥራና በሥራ ላይ የሥልጠና መርሐ ግብሮች የዳኞች ሥልጠና ለመስጠት ቢችሉም፣ ግልጽና ሁሉንም ጉዳዮች የመለሰ የዳኝነት የሥልጠናና ትምህርት ስትራቴጂ አለመኖር እንደ ትልቅ ክፍተት የሚታይ መሆኑ በዳሰሳ ጥናቱ ተገልጿል፡፡
የዳኝነት ሥልጠና ራሱን የቻለ የአጭር፣ የመካከለኛና የረዥም ጊዜ ስትራቴጂ ተቀርፆለት መመራት ይኖርበታል ያሉት ጥናት አቅራቢዎቹ፣ የዳኝነት የሥልጠና ተቋማት የዳኝነት ሥልጠና ስትራቴጂና ፍላጎቶችን መሠረት በማድረግ የሚቀረፁ የተለያዩ የሥልጠና መርሐ ግብሮች ሊኖራቸው እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡