መንግሥት አሸባሪ ባለው የሕወሓት ኃይል ላይ ‹‹ብርቱና የማያዳግም›› ዕርምጃ እንዲወሰድ ለመከላከያ ሠራዊት፣ ክክልሎች ለተወጣጡ ልዩ ኃይሎችና ለሚሊሻ አባላት አቅጣጫ መስጠቱን አስታወቀ።
የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ማክሰኞ ነሐሴ 4 ቀን 2013 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ‹‹ኢትዮጵያን ለማፈራረስ የተነሳ የክህደት ኃይል›› ባለው የሕወሓት ኃይልና ከዚህ ኃይል ጋር ተሠልፈዋል ያላቸውን ‹‹የውጭ እጆች›› ለመደምሰስ፣ የመከላከያ ሠራዊቱና ከክልል መንግሥታት የተወጣጡ ልዩ ኃይሎች፣ እንዲሁም ሚሊሻዎች ብርቱና የማያዳግም ዕርምጃ እንዲወሰድ አቅጣጫ ተቀምጧል ብሏል።
‹‹ውጊያው የትግራይን ሕዝብ ምሽግ ካደረገው እኩይ ኃይል ጋር እንጂ ከትግራይ ጋር አይደለም፣ እናም ስንፋለም መጠቀሚያ የሆነውን የትግራይ ሕዝብ ብሎም መላዋ ኢትዮጵያን ከአሸባሪው ቡድን ነፃ ለማውጣትና የአገራችንን ሰላምና አንድነት ለማስከበር ነው፤›› ሲል መንግሥት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።
መንግሥት የወሰነውን የተናጠል ተኩስ አቁም በማክበር የአገር መከላከያ ሠራዊትና የክልል መንግሥታት ልዩ ኃይሎች ዕርምጃ ከመውሰድ ቢቆጠቡም፣ ‹‹አሸባሪው›› የሕወሓት ኃይል ግን፣ ‹‹የድፍረት ድፍረት ተሰምቶት የጥፋት ሥራውን ቀጥሎበታል፤›› ብሏል።
የሕወሓት ዓላማና ግብ ኢትዮጵያን ማፈራረስ እንደሆነ አመራሮቹ በዕብሪት መናገራቸውን የጠቀሰው መግለጫው፣ ለዚህ ዓላማ መሳካትም በብዙ የውጭ ኃይሎች በመታገዝ ለበለጠ ጥፋት ምላጭ መሳብን እንደመረጡ ገልጿል።
የሕወሓት ኃይል ወጣቶችን በእኩይ ፕሮፓጋንዳ በመደለልና ሕፃናትን በሐሽሽ እንዲናውዙ በማድረግ ለጦርነት እየመለመለ፣ በአፈሙዝ የሚነዱ አዛውንቶችን ጭምር እያሠለፈ እንደሚገኝ የሚገልጸው መግለጫው፣ የዚህ ‹‹አሸባሪ ጁንታ›› አካሄድ ሕዝብ አስጨራሽ የሆነ የሽፍትነት አካሄድ መሆኑን ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም ሆነ ለትግራይ ሕዝብ በተደጋጋሚ መንግሥት መግለጹንና ማስጠንቀቁን አስታውሷል።
ይህ ኃይል እየከፈተ ባለው ጥቃት ሕዝባዊ መልክ እንዲይዝ ያደረገ በመሆኑ ይህንን ኃይል መመከት የሚገባውም በዚያ አግባብ እንደሆነ በመግለጽ፣ የሕወሓት ኃይል ‹‹የመላው ሕዝባችንን የማያዳግም ምላሽ ሊያገኝ ይገባል፤›› ብሏል። ነገር ግን ትግሉ ከትግራይ ሕዝብ ጋር እንዳልሆነ ጠቁሟል።
‹‹ውጊያው የትግራይን ሕዝብ ምሽግ ካደረገው እኩይ ኃይል ጋር እንጂ ከትግራይ ጋር አይደለም፣ እናም ስንፋለም መጠቀሚያ የሆነውን የትግራይ ሕዝብ ብሎም መላዋ ኢትዮጵያን ከአሸባሪው ቡድን ነፃ ለማውጣትና የአገራችንን ሰላምና አንድነት ለማስከበር ነው። ትግላችን ከአሸባሪው ጁንታ ጀርባ ላይ ተፈናጥጠው አገራችንን ለማፈራረስና የኢትዮጵያን ህልውና ለማጨለም ከተነሱ የቅርብና የሩቅ ኃይላትና አገሮች ጋር ጭምር ነው፤›› ብሏል።
መግለጫው ሁሉም አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ሉዓላዊነቱን ለማስጠበቅ በሙሉ ልቡ እንዲሠለፍ፣ እንደ ጥንቱ ዛሬም የአገሩን ክብር ላለማስደፈር ቆርጦ እንዲነሳም ጥሪ አቅርቧል።
በዚህም መሠረት፣ ‹‹አገር በመከላከል ዘመቻው ለመሳተፍ ዕድሜያችሁና አቅማችሁ የሚፈቅድላችሁ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የመከላከያ ሠራዊቱን፣ ልዩ ኃይሉንና ሚሊሻውን በመቀላቀል የአገር ዘብነታችሁ የምታሳዩበት ትክክለኛው ጊዜ አሁን ነው፤›› ብሏል።
የፀጥታ ኃይሎችን በቀጥታ ለመቀላቀል ያልተቻለው የኅብረተሰብ ክፍል ከመቼውም ጊዜ በላይ ወገቡን አስሮ በልማት ሥራዎች ላይ ተሳትፎውን ማጠናከር እንዳለበት፣ የመንግሥት ሠራተኛውም በሙሉ አቅሙ ቢሮክራሲ ሳይፈጥር ሥራውን እንዲያከናውን ማሳሰቢያ ሰጥቷል።
በተጨማሪም ለመላው ሕዝብ ባስተላለፈው መልዕክት፣ ሁሉም አካባቢውን ነቅቶ እንዲጠብቅ ብሏል።
‹‹የጁንታው ተላላኪዎች የጥፋት ተልዕኳቸውን እንዳይፈጽሙ ሕዝባችን በዓይነ ቁራኛ ይከታተል። ከዚህ ባለፈ ለሠራዊቱ የሚሆን ስንቅ በማዘጋጀትና የሞራል ድጋፍ በማድረግ ብርቱ ደጀን ይሁን። ሚዲያዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችና ማኅበራዊ አንቂዎች ሕዝቡ ከአገሩ ጎን እንዲቆም የበኩላችሁን አስተዋጽኦ እንድታበረክቱ ይጠበቃል። አሸባሪው ጁንታ ሰላማዊ ሰዎች አስመስሎ በየአካባቢው ያሰማራቸው ሰላዮችና የጥፋት ተላላኪዎችን ለመከታተልና ለማጋለጥ እንዲቻል፣ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ለአገሩ ዓይንና ጆሮ በመሆን ከፀጥታ አካላት ጋር በቅርበት ሊሠራ ይገባል። የሃይማኖት አባቶች በጸሎት፣ የአገር ሽማግሌዎች በምክር፣ ሁሉም ዜጋ በችሎታው ኢትዮጵያን ብሎ ይቁም፤›› በማለት ጥሪ አቅርቧል።