አቶ ስብሃት ነጋና አብርሃም ተከስተ (ዶ/ር)ን ጨምሮ ለ21 ተከሳሾች ክስ ተነበበላቸው
በሌሉበት ክስ የተመሠረተባቸውን ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር)፣ አቶ ጌታቸው አሰፋና አቶ ጌታቸው ረዳን ጨምሮ 41 ተከሳሾችን የፌዴራል ፖሊስ አፈላልጎ ይዞ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ተሰጠ፡፡
አቶ ስብሃት ነጋ፣ ወ/ሮ ኬሪያ ኢብራሂም፣ አብርሃም ተከስተ (ዶ/ር)፣ አምባሳደር ዓባይ ወልዱ፣ ሰሎሞን ኪዳኔ (ዶ/ር) እና ወ/ሮ ሙሉ ነጋን ጨምሮ ለ21 ተከሳሾች እያንዳንዳቸው የተሳተፉበት የወንጀል ተሳትፎን የሚገልጽ ክስ በዝርዝር ተነቦላቸዋል።
በክሱ ላይ የእያንዳንዳቸው የወንጀል ተሳትፎ የተጠቀሰ ሲሆን፣ የክልል መንግሥትን በኃይል በመመሥረት፣ የፌዴራል መንግሥትን በኃይል ለመጣል ዝግጅት ማድረግ፣ ሕገወጥ ወታደራዊ ቡድን በማደራጀት ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት ማድረስ፣ በባህር ዳርና ጎንደር ሮኬት በማስወንጨፍ ጉዳት ማድረስና የነዳጅና የገንዘብ ዝርፊያና ሌሎችም የወንጀል ተግባሮችን ችሎቱ በዝርዝር አሰምቷል፡፡ በተጨማሪም ዓቃቤ ሕግ ያሉትን ማስረጃዎች ለእያንዳንዱ ተከሳሽና ለፍርድ ቤቱ በፍላሽ አቅርቧል።
ክሱ ከተሰማ በኋላ የተከሳሽ ጠበቆች ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት፣ በደንበኞቻቸው ላይ የቀረበው ክስ የዋስትና መብታቸውን ሊያስከለክላቸው ስለማይችል ዋስትናቸው ሊከበር ይገባል በማለት የመብት ጥያቄ አንስተዋል፡፡
ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በበኩሉ፣ አብዛኞቹ ተከሳሾች በሁለት ክስ የተከሰሱ መሆናቸውን፣ ተከሳሾቹ የፈጸሙት የሽብር ወንጀል ከዕድሜ ልክ እስራት እስከ ሞት የሚያስቀጣ መሆኑን፣ የፈጸሙት ወንጀልም ከፍተኛ መሆኑንና ተከሳሾቹ ዋስትና እንዳያሰጣቸው የሚያደርጉ ሐሳቦችን ከተቀመጡ የወንጀል መቅጫ ሕጎችና አዋጆች ጋር አጣምሮ መቃወሚያውን አቅርቧል። ከ59ኛ ተከሳሽ ውጪ ያሉ ተከሳሾች ከ2011 ዓ.ም. ጀምሮ የፌዴራል መንግሥትን በኃይል ለማውረድ ሲዘጋጁ ቆይተው ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰሜን ዕዝና በፌዴራል ፖሊስ ላይ የሽብር ሕጉን ተላልፈው ጥቃት መፈጸማቸውን፣ በጥቃቱም በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መሞታቸውንና ይህም በቀጣይ በሰው ማስረጃ የሚረጋገጥ መሆኑን አክሏል፡፡ በሕወሓት ተቃራኒ የሚቆሙ ሕወሓትን የማይደግፉ ሰዎች ጥቃት እንዲደርስባቸው ሲደረግ እንደነበር ጠቅሶ፣ ይህ የሽብር ተግባርን የሚያሳይ ስለሆነ ዋስትና መጠየቁ ተገቢነት እንደሌለው ዓቃቤ ሕግ አስረድቷል፡፡
የተከሰሱበት ተደራራቢ የሽብር ወንጀል በመሆኑም የወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ አንቀጽ 63 ዋስትና የሚከለክል በመሆኑ ዋስትናውን ተቃውሟል፡፡ የተከሳሽ ጠበቆችም በቀዳሚ ምርመራ የተሰሙ በመንግሥት ጥበቃ የሚደረግላቸው ምስክሮች ላይ ተከሳሾቹ በእስር ላይ ሆነው ጥቃት ያደርሳሉ መባሉ ተቀባይነት የሌለው ነው ሲሉ ተከራክረዋል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር ያዳመጠው ፍርድ ቤቱ ዋስትናን በሚመለከት ክርክሩን መርምሮ ብይኑን በጽሑፍ ባሉበት ማረሚያ ቤት እንደሚደርሳቸው በመግለጽ፣ ክሱን ለመመልከት ለጥቅምት 22 ቀን 2014 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡