ከቀድሞውም በቂ ደመወዝ የማይከፈለው ተጨቋኝ የኤጀንሲ ተቀጣሪ ሠራተኛ በአሁኑ ወቅት በተከሰተው የኑሮ ውድነት ምን ያህል እየተሰቃየ እንደሆነ ቆም ብሎ ያየ የሕግ አካል ያለ አይመስልም፡፡
ሠራተኛው ተደራጅቶና ማኅበር መሥርቶ መብቱን እንዳይጠይቅ የአንዳንድ ኤጀንሲ ሱፐርቫይዘሮች ተፅዕኖ ያደርጋሉ፡፡ ተቀጣሪው ሠራተኛም ከክፍለ አገር የገቡ ከመሆናቸውም በላይ የትምህርት ደረጃቸው ከመሠረተ ትምህርት ያላለፈ ነው፡፡
በዚህም ምክንያት ግዴታውን ብቻ እንጂ መብቱን ለይቶ አያውቅም፡፡ ስለዚህ አንዳንድ ኤጀንሲዎች ሠራተኛው ግዴታውን ብቻ በአንቀጽ ቁጥር እየጠቀሱ ያስፈራራሉ፡፡ ደፍሮ መብት የሚጠይቅ ካለም በተዘዋዋሪ መንገድ ዕርምጃ ይወሰድበታል፡፡ የሥራ ቅጥር ደብዳቤ መጠየቅ ጥቅማጥቅም መጠየቅ አይቻልም፡፡ የሥራ ውል ስምምነት ሰነዱን እንዲነበብ አይፈቅድም፡፡ ይህም የሚደረገው መብትና ግዴታ መታወቅ ስለሌለበት ነው፡፡
በነገራችን ላይ ሁሉንም ኤጀንሲዎች ማለቴ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ፡፡ ለምሳሌ እኔ እሠራበት የነበረው ኤጀንሲ በባንክ ጥበቃ ሠራተኛ ተቀጥሬ ስሠራ ሌላ ቀርቶ ዩኒፎርም እንኳ የመጠየቅ መብት የላችሁም ተብለን ከተሰጠ ሁለት ዓመት ያስቆጠረ ከመሆኑ የተነሳ፣ ተቀዳዶ በእጅ በመርፌ እየሰፋን ነው የምንለብሰው፡፡ ከመጀመርያውም ልብሱ (ዩኒፎርሙ) ሲሰጥ ተሟልቶ አይሰጥም፡፡ ለምሳሌ ሱሪና ሸሚዝ ከተሰጠ፣ ጫማው ከስድስት ወር በኋላ ይሰጣል፡፡ ጃኬት ደግሞ ሌላ ጊዜ፡፡ ይህም ማለት ልብሱ ሲያልቅ ጫማ፣ ጫማ ሲያልቅ ልብስ እንደማለት ነው፡፡
በአሁኑ ሰዓት አንዳንድ የባንኩ ጥበቃ ሠራተኞች የለበሱት ዩኒፎርም ከዕድሜው መርዘም የተነሳ ከለሩን ለቆ ለተመልካች የባንክ ጥበቃ ናቸው ወይ? የሚል ጥያቄ ያስነሳል፡፡ ያሳፍራል፡፡ በዚህ ላይ ሠራተኛው የ24/48 የጥበቃ ደመወዝ ዳቦ መግዣ አልበቃህ ሲለው 48/24 ስለሚሠራ በወር ውስጥ 20 ቀን በሥራ ላይ ነው፡፡ በአንድ ዩኒፎርም በወር ውስጥ 20 ቀን ይሠራል ማለት ነው፡፡ ዩኒፎርም ሲጠይቋቸው የመጠየቅ መብት የላችሁም ይባላል፡፡ በዚህ ችግር ላይ ደግሞ ኤጀንሲው የመደባቸው አንዳንድ ተቆጣጣሪዎች ከሠራተኛው ጥቅም የሚፈልጉ አሉ፡፡ በጥቅማጥቅም ካልተሳሰርን በሥራ ላይ ተፅዕኖ ይኖረዋል፡፡
ሌላው ደግሞ አንገብጋቢው ጉዳይ ከደመወዛችን ላይ የሚቆረጠው የሥራ ግብር፣ የጡረታና የመሳሰሉት መዋጮዎች አሉ፡፡ ነገር ግን ኤጀንሲውን የጡረታ ካርድና የግብር ከፋይ ቲንነምበር ካርድ እንዲሰጡ ቢጠየቁ ለመስጠት ፈቃደኛ አይደሉም፡፡ ይህ ማለት ደግሞ የግብር እየተባለ የሚቆጠረው ለመንግሥት ገቢ አልሆነም ማለት ነው፡፡
የኤጀንሲዎች ጉዳይ እንዲህ ተዘርዝሮ አያልቅም፡፡ ነገሩን ሕግ ይዞታል ቢባልም መቼ ከዚህ ችግር ውስጥ ሠራተኛው እንደሚወጣ ህልም ሆኖበታል፡፡ ህልሙን የሚፈታለት ይፈልጋል፡፡
ዓባይህነህ ሽባባው፣ ከአዲስ አበባ