በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚገኙ የግል ትምህርት ተቋማት የ2014 ዓ.ም. የትምህርት ዘመንን ምክንያት በማድረግ ተገቢ ያልሆነ ጭማሪ በማድረግና በወላጆች ላይ ጫና በመፍጠር ላይ በመሆናቸው፣ የማያዳግም ዕርምጃ ከመውሰዱ በፊት እንዲያስተካክሉ ሲል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ አሳሰበ፡፡
ቢሮው ሰኞ ነሐሴ 24 ቀን 2013 ዓ.ም. በድረ ገጹ በወጣው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ ለ2014 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን ለትምህርት አገልግሎትና ምዝገባ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርትና ሥልጠና ጥራት፣ የሙያ ብቃት ምዘናና ማረጋገጫ ባለሥልጣን ባወጣው የማስፈጸሚያ መመርያ መሠረት መሥራት እየተገባቸው፣ ያንን ባለመፈጸም በመቶዎች የሚቆጠሩ ትምህርት ቤቶች የተጋነነ ዋጋ ጭማሪ አድርገዋል፡፡
ይህ ድርጊት ተገቢና የጊዜውን ሁኔታ ከግንዛቤ ውስጥ ያስገባ ድርጊት ባለመሆኑ፣ ኢትዮጵያዊ የጨዋነትና አብሮነት እሴቶችን በማዳበር፣ ይህንን ወሳኝና አስቸጋሪ ጊዜ በጋራ ማለፍን ማዕከል በማድረግ፣ ሁሉም የትምህርት ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ ቢሮ አሳስቧል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውስጥ የሚገኙ የግል ትምህርት ተቋማት በትምህርቱ መስክ በመሰማራት፣ የትምህርት ተደራሽነትን ከማረጋገጥና ለከተማው ነዋሪ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ሚናቸው ላቅ ያለ መሆኑን፣ እንዲሁም የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት የተቀመጠውን ፕሮቶኮል በማክበር የመማር ማስተማሩ ሒደት እንዲከናወንና ተማሪዎች ውጤታማ እንዲሆኑ ላደረጉት ሥራ፣ ማዕድ በማጋራት፣ የአቅመ ደካሞችን ቤት በማደስ፣ መልካም ሥራ ውስጥ በመሳተፍ የበርካቶችን ዕንባ በማደስና ለመከላከያ ሠራዊትም የገንዘብ ድጋፍ በማድረግ መንግሥት ለጀመረው ሕግ የማስከበር ተግባር አጋርነታቸውን ዕውቅና እንደሚሰጥና እንደሚያመሠግን ጠቁሟል፡፡
ለቢሮውና ለወላጅ ምላሽ በመስጠታቸውና የማስተካከያ ዕርምጃ በመውሰዳቸው በ41 ትምህርት ተቋማት ላይ ተጥሎ የነበረው ዕገዳ እንዲነሳላቸውና አገልግሎት እንዲሰጡ ተደርጓል፡፡ ‹‹ወቅቱ ተደጋግፈን የምናልፍበት እንጂ አንዱ በሌላው ላይ ጫና የሚፈጥርበት እንዳልሆነ ታውቆ፣ የግል ትምህርት ቤቶች ከደንበኞቻቸው ጋር በመነጋገርና በመግባባት እንዲሠሩ እናሳስባለን፡፡ በቀጣይ ይህ ታልፎ ድርጊቱ የሚቀጥል ከሆነ፣ በሚቀርበው ጥቆማ መሠረት ቢሮው ፈጣንና የማያዳግም ዕርምጃ ይወስዳል፤›› ሲልም አስጠንቅቋል፡፡