በኢትዮጵያ የእንግዳ ማረፊያ አገልግሎቶችን በዘመናዊ መንገድ ለመስጠት የሚያገለግል መተግበሪያ ይፋ ሆነ፡፡ ‹‹የኛ ሆም›› በሚል መጠርያ የሚታወቀው መተግበሪያ የውጭና የአገር ውስጥ እንግዶችን ከአገልግሎት ሰጪ ሆቴሎችና ልዩ የእንግዳ ማረፊያ ሪዞርቶች ጋር በቀላሉ ያገናኛል፡፡
የዲጂታል ቴክኖሎጂው ከሚሰጠው አገልግሎት መካከል ሰዎች እንግልት ሳይደርስባቸው በፈለጉት ወቅትና ሰዓት ሆቴሎችን እንዲያገኙ የሚያደርግ መሆኑን፣ ‹‹የእኛ ሆም›› መተግበሪያ መሥራች አቶ ዮሐንስ ተኮላ አስረድተዋል፡፡
መተግበሪያውም የድረ ገጽ (ዌብሳይት) መጠቀሚያን፣ የሞባይል መተግበሪያና የጥሪ ማዕከል መገልገያዎችን በመጠቀም አገልግሎት ሰጪን ከአገልግሎት ፈላጊ ጋር የሚያገናኝ መሆኑን መተግበሪያው ይፋ በተደረገበት ነሐሴ 25 ቀን 2013 ዓ.ም. አቶ ዮሐንስ አብራርተዋል፡፡
መተግበሪያው አገልግሎት ፈላጊውንና ሰጪውን በቀላሉ ከማገናኘት ባሻገር የአገር ውስጥ ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ በማዋል የውጭ ምንዛሪ ወጪን ለማስቀረት እንደሚረዳም ገልጸዋል፡፡
‹‹እንደዚህ ዓይነት ቴክኖሎጂዎች ባለንበት ቦታ የፈለግነው አገልግሎት ለማግኘት አስተዋጽኦቸው የጎላ ነው›› ያሉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የአይሲቲ ዘርፍ ዋና ዳይሬክተር አብዮት ሲናሞ (ዶ/ር)፣ አገልግሎቱን የሚጠቀም ማኅበረሰብ ለመፍጠር የዲጂታል ዕውቀት መፍጠር ላይ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ዘርፎች ላይ ዲጂታል ቴክኖሎጂ አሠራር እየተተገበረ መሆኑን የገለጹት አብዮት (ዶ/ር)፣ ‹‹ይህም የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድገት አንድ ዕርምጃ ከፍ እንዲል ያደርጋል፤›› ብለዋል፡፡
የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂ ካስቀመጣቸው መሪ አቅጣጫዎች ዋነኛው ቱሪዝምን በቴክኖሎጂ ማገዝ በመሆኑ፣ እንደዚህ ዓይነት ቴክኖሎጂ ፈጣሪ ሰዎችን ማበረታታት እንደሚገባም አክለዋል፡፡
በአሥር ዓመቱ አገራዊ የልማት ዕቅድ ላይ ቱሪዝምና የግሉ ዘርፍ መሪ የሆነበት ኢኮኖሚ መፈጠር መታቀዱን የገለጹት የፕላን ምክትል ኮሚሽነር አቶ እንዳልካቸው ስሜ፣ እንደ ‹‹የእኛ ሆም›› ያሉ የቴክኖሎጂ አገልግሎቶች ለዚህ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ ብለዋል፡፡