አደገኛው የኮቪድ ዴልታ ዝርያ ኢትዮጵያ ውስጥ መኖሩ መረጋገጡን ተከትሎ የጥንቃቄ ዕርምጃዎች ይበልጥ ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ማሳሰቢያ ተሰጠ፡፡
የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር) ጳጉሜን 2 ቀን 2013 ዓ.ም. እንደገለጹት፣ በተደረገው የላቦራቶሪ ምርመራ የተገኘው አዲሱ ዝርያ ሁሉንም የዕድሜ ክልል የሚያጠቃ፣ ለከባድ ሕመምና ሞት የሚዳርግ፣ በተለይም ባልተከተቡ ሰዎች ላይ የሚበረታ ዝርያ ነው፡፡
‹‹ዴልታ›› የተሰኘው ዝርያ በሥርጭት ፍጥነት ቀደም ብሎ ከነበረው ‹‹አልፋ›› ከተሰኘው ዝርያ በሁለት እጥፍ እንደሚበልጥ የጠቆሙት ሚኒስትሯ፣ ባለፈው ሳምንት ብቻ 8300 ሰዎች በኮሮና መያዛቸውንና 118 ሰዎች መሞታቸውን በዚህም ሳምንታዊ በቫይረሱ የመያዝ ምጣኔ 20 ፐርሰንት መድረሱን አማካይ የሞት ምጣኔም በቀን 16 ሰዎች መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በመሆኑም ኅብረተሰቡ ከመከላከያ መንገዶች ጎን ለጎን የተሳሳቱ አመለካከቶችን በመተው በዓለም አቀፍ ደረጃ ጥራቱ የተረጋገጠውንና ላለመያዝ የሚከላከለውን፣ ከተያዙ በኋላም ፅኑ ሕሙም የመሆን ዕድልን የሚቀንሰውን ክትባት እንዲወስድ፣ በዝግ ቦታዎች የሚደረጉ መሰባሰቦችን መቀነስ እንደሚያስፈልግና አገልግሎት ሰጭ ተቋማትም ጥንቃቄያቸውን መጨመር እንደሚገባቸው መክረዋል፡፡
አያይዘውም በተሠሩ በርካታ ሥራዎች የክትባት ተደራሽነት እየሰፋ በመሆኑ በሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች የሚገኙና ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በላይ የሆኑ ዜጎች መከተብ እንደሚችሉ አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ቶሌራ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ አዲሱ ዝርያ መኖሩ በቅርብ ቢረጋገጥም ሥርጭቱ እንደቆየ የሚያሳዩ ጥናቶች መኖራቸውን ጠቁመዋል፡፡
ከዚህ ቀደም ክትባት ያልወሰዱና ለሁለተኛ ጊዜም የሚወስዱ ሰዎች በየጤና ተቋማቱ በመገኘት ክትባቱን ሊወስዱ እንደሚገባ ያሳሰቡት ሚኒስትሯ፣ ባለፉት ሳምንታት በወረርሽኙ የሚያዙ፣ የሚሞቱና የፅኑ ሕሙማን ቁጥር በጣም እንዳሻቀበ ጠቁመዋል፡፡ የኮቪድ-19 ፕሮቶኮልን በመተግበር ከሁሉም ተቋማትና ግለሰቦችም እንደሚጠበቅም አሳስበዋል፡፡
በርካታ አገሮች በሦስተኛና አራተኛ የኮቪድ ሥርጭት ማዕበል እየተመቱ መሆናቸው የሚታወቅ ነው፡፡
በተያያዘም ሚኒስትሯ በአገር አቀፍ ደረጃ የታሰበውን የጳጉሜን 2 የአገልጋይነት ቀን አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት፣ የጤና ባለሙያዎችና የጤና ክብካቤ ሠራተኞች የኮሮና ወረርሽኝን ለመቋቋምና ሕዝቡን ከከፋ ስቃይና ኅልፈተ ሕይወት ለመታደግ፣ ሙያቸውን እና የማይተካ ሕይወታቸውን ጭምር አሳልፈው መስጠታቸውን አስገንዝበዋል፡፡
ሌት ተቀን ከሕዝብ ጎን በመቆም፣ ከቫይረሱ ጋር ፊት ለፊት ተጋፍጠው ማገልገላቸውን፣ እንደዚሁም ሌሎች መሠረታዊ የጤና አገልግሎቶች ሳይቋረጡ በማስቀጠል ረገድም ጉልህና የማይተካ አስተዋጽኦ ያበረከቱ በመሆናቸው፣ በአገልጋይነት ቀን ምስጋና እና ዕውቅና ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
አሁናዊ መረጃና የጥንቃቄ ማሳሰቢያ
እስከ ጳጉሜን 1 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ 316,174 ሰዎች በበሽታው ተይዘዋል። 4,785 ሰዎች ደግሞ በወረርሽኙ ሳቢያ ሕይወታቸው አልፏል። በኮቪድ ወረርሽኝ የመያዝ ምጣኔውም ከ1 በመቶ ወደ 20 በመቶ አሻቅቧል፡፡
በሆስፒታሎች የአስተኝቶ ማከሚያ ክፍሎች፣ አጋዥ የመተንፈሻ መሣሪያ እጥረት እያጋጠመ፣ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ከዕለት ወደ ዕለት በከፍተኛ ደረጃ ከመሠራጨቱም በላይ ሰብዓዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግሮችን እያስከተለ እንደሚገኝም ተገልጿል፡፡
በዚህም የተነሳ የኮቪድ-19 ሥርጭትን ለመከላከልና የሚያስከትለውን ሞት ለማስቆም የሚከተሉትን የመከላከያ ዘዴዎችን መተግበር አስፈላጊ መሆኑን የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡
ከመከላከያ ዘዴዎቹም መካከል ለመጪው የአዲስ ዓመትና ሌሎች ሕዝባዊና ሃይማኖታዊ በዓላት የሚፈጠሩ መሰባሰቦችን ማስቀረት፣ ሁሉም ተቋማት ደንበኞቻቸውን የኮቪድ-19 መከላከያ መንገዶችን እንዲተገብሩ ማድረግ፣ የኮቪድ-19 ምልክቶች ሲታዩ ወደ ጤና ተቋማት በመሄድ ምርመራ ማካሄድና የኮቪድ-19 ክትባትን መከተብ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ከዚህም ሌላ በበዓል ወቅት ለዕርድ አገልግሎት የሚውሉ ማንኛውንም ቁሳቁሶች ንፅህናቸውን እንዲጠበቁ ማድረግና ንክኪዎችን መቀነስ፣ ለግብይት ከቤት ውጪ በሚደረግ መንቀሳቀስ ማስክ ማድረግ፣ የእጅ ማፅጃ ሳኒታይዘር መያዝ ያስፈልጋል፡፡ በበዓል ወቅት ከሌሎች ሰዎች ጋር የሚኖር ማኅበራዊ ግንኙነት መቀነስ፣ ያልበሰሉ የምግብ ተዋጽኦዎችን እንደ ጥሬ ሥጋ፣ ያልተፈላ ወተትና ሌሎችን ከመመገብ መቆጠብ፣ ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በመመርያ 803/2013 ዓ.ም. ላይ የተቀመጡ ድንጋጌዎችን ተግባራዊ ማድረግ ከመከላከያ ዘዴዎች ተጠቃሾች መሆናቸውን ኢንስቲትዩት አስታውሷል፡፡