በኢትዮጵያ እየፈረሱ የሚገኙና አገልግሎት ሳይሰጡ የተቀመጡ ቅርሶችን ለመታደግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየሠራ መሆኑን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ ሚኒስቴሩ ይህንን ያስታወቀው ባለፈው ሳምንት መጨረሻ አካባቢ በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ላይ የ2013 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ባቀረበበት ወቅት ነው፡፡
የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ሒሩት ካሳው (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በኢትዮጵያ በተለያዩ ቦታዎች ላይ የሚገኙ ቅርሶችን ጠብቆ ለቱሪዝም መስህብነት ለማዋልና በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማስተዋወቅ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው፡፡
ከአሁን በፊት የነበሩ ፖሊሲዎችን እንደ አዲስ በማሻሻል የቱሪዝም መስህቡን ማጎልበት እንደሚያስፈልግ የገለጹት ሚኒስትሯ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ያሉ ቅርሶች እንዳይጠፉ ለመታደግ ከከተማ አስተዳደሩና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት የሚሠራ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በ2013 ዓ.ም. 12,371 ተንቀሳቃሽ ቅርሶችን ጥብቅ የሆነ እንክብካቤ ለማካሄድ ታቅዶ፣ 19,505 ቅርሶችን እንክብካቤ በማድረግ የዕቅድ አፈጻጸሙን በብልጫ ማሳካት እንደተቻለ ሒሩት (ዶ/ር) አስረድተዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ክልሎች ላይ የሚገኙ ቅርሶች በምን ዓይነት ሁኔታ ላይ ናቸው የሚለውን ለማወቅ መረጃው እንደሌላቸው፣ በከተማዋም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ላይ በግለሰብ ደረጃ የተያዙ ቅርሶች እንዳሉ አክለዋል፡፡
ቅርሶችን መጠበቅ ለመንግሥት ብቻ የሚተው ነገር አለመሆኑንና ኢትዮጵያ የብዙ ባህልና እሴት ባለትሩፋት በመሆኗ አብዛኛዎችን ነገሮች ጠብቆ ለማስቀጠል በ2014 በጀት ዓመት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡
- በአገር አቀፍ ደረጃ የቅርስ አጠባበቅ ሁኔታ ሲታይ
በባህል ዘርፍ የጌዴኦ ባህላዊ መልክዓ ምድር፣ የአሸንዳ ሻደይ ባህላዊ ቅርስን በዓለም ቅርስነት ለማስመዝገብ ጥናቱ ተጠናቆ ለዩኔስኮ መላክ ችሏል፡፡ በ2013 ዓ.ም. በጀት ዓመት 400 የቋሚ ቅርሶችን ምዝገባ ለመካሄድ ታቅዶ 2,038 ቋሚ ቅርሶችን ምዝገባ ማከናወን ተችሏል፡፡ 27,400 የተንቀሳቃሽ ቅርሶችን ምዝገባ ለማካሄድ ታቅዶ 17,712 የተንቀሳቃሽ ቅርሶች ምዝገባ ማከናወን እንደተቻለ መረጃው ያመለክታል፡፡ 854 የቋሚ ቅርሶች ጥበቃና እንክብካቤ ለማካሄድ ታቅዶ 1,047 ማከናወን እንደተቻለ ተነግሯል፡፡ 12,371 የተንቀሳቀሽ ቅርሶች ጥበቃና እንክብካቤ ለማካሄድ ታቅዶ 19,505 ያህል ተከናውኗል፡፡
የቅርሶችን ጥበቃና እንክብካቤ ከዕለት ወደ ዕለት በማሻሻል፣ እንዲሁም በዘርፉ ላይ ፖሊሲዎችን በመቅረፅ በኩል በዘርፉ ብዙ ክንውኖችን ለማድረግ ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ ይገኛል፡፡ በ2013 ዓ.ም. የነበሩትን ችግሮች በመቅረፍና በ2014 ዓ.ም. ላይ በማሻሻል ሰፊ ሥራ እንደሚሠራ ሪፖርቱ በቀረበበት ወቅት ተገልጿል፡፡ በአሁኑ ወቅት በፖለቲካ ምክንያት ግጭት የተፈጠረባቸው ቦታዎች ላይ የቅርሶች አጠባበቅ ሁኔታ ምን እንደሚመስል ማወቅ እንዳልተቻለ ተናግሯል፡፡
- በ2014 በጀት ዓመት ተግባራዊ ከሚሆኑ ዕቅዶች መካከል
የአገር ውስጥ ቱሪዝም ማጠናከር፣ የፀደቁ መመርያዎችን ተግባራዊ ማድረግ፣ የቱሪዝም አገልግሎት መስጫ ተቋማት ቁጥር ማሳደግ፣ የቱሪዝም ልማት ማጎልበት በአገሪቱ የሚገኙ ባለሀብቶችን ዘርፍ ላይ ማሳተፍ፣ የቅርስ ጥበቃ እንክብካቤ ማጎልበት፣ እንዲሁም ማኅበረሰቡም ስለቅርስ እንዲያውቅ ግንዛቤ መፍጠርና ሌሎች ነገሮች ተግባራዊ በማድረግ ዘርፉን ለማሳደግ የሚሠራ መሆኑን ሚኒስቴሩ ሪፖርት ባቀረበበት ወቅት አስታውቋል፡፡