በየመን የእርስ በርስ ጦርነት ተቀስቅሶ አገሪቷ ማብቂያ ከሌለው መከራ ከተዘፈቀች ሰባት ዓመታት አልፈዋል፡፡ ከሰባት ዓመት በፊት የሃውቲ ታጣቂዎች የየመንን መዲና ሰንአ ከተቆጣጠሩ በኋላ ቀድሞውንም በድህነት ውስጥ ይዳክሩ የነበሩ የመናውያን ለከፋ ችግር ተጋልጠዋል፡፡
በዓለም የከፋ የሰብዓዊ ድጋፍ ቀውስ ከገጠማቸው አገሮች በቀዳሚነት በምትጠቀሰው የመን፣ በተለይ ሕፃናት ለባሰ ጉዳት መዳረጋቸውን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ሰሞናዊ ሪፖርት ያሳያል፡፡
በየመን ለዓመታት የዘለቀውን ጦርነት ለማርገብ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ተደርገዋል ቢባልም፣ በኢራን ይደገፋሉ የሚባሉት የሃውቲ አማፅያንና በሳዑዲ ዓረቢያ የሚደገፈው የየመን መንግሥት የሚያካሂዱት የውክልና ጦርነት ሊያባራ አልቻለም፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የመናውያንን ለረሃብ የዳረገው የውክልና ጦርነትም ሊያቆም የሚችልበት ጭላንጭል እንደማይታይ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
በዚህ ማብቂያ ባጣው ጦርነት ደግሞ እ.ኤ.አ. በ2019 እና በ2020 ብቻ 2,600 ሕፃናት ተገድለዋል ሲል ተመድ በሪፖርቱ አስፍሯል፡፡
ሲቪሎችን ከተዋጊዎች በማይለየው የተኩስ እሩምታ፣ የአየር ድብደባና ፈንጂ ምክንያት ከ3,500 በላይ ሕፃናት የተጎዱ ሲሆን፣ ከዚሁ ጎን ለጎንም ሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረግ አስቸጋሪ ሆኗል ሲል ተመድ አስታውቋል፡፡
የየመናውያን ሕፃናትንና ታዳጊ ወጣቶችን የወደፊት ሕይወት እያጨለመ የሚገኘው ጦርነት አስቸኳይ ፖለቲካዊ መፍትሔ ማግኘት አለበትም ብሏል፡፡
በየመን እየተፈጸሙ ያሉ ጥቃቶችን ለማረጋገጥ አለመቻሉ፣ በየቦታው ያለው ግጭትና ኮቪድን ተከትሎ የተጣለው የመንቀሳቀስ ገደብ ጥቃቶችን በማስረጃ ለመያዝ እንቅፋት መሆኑም ተነግሯል፡፡
የማኅበረሰቡን የቀደመ አኗኗር ያዛባው፣ ሕዝቡ ላይ መከራ የጫነው፣ ከቀየው እንዲፈናቀልና እንዲሰደድ ያደረገው ጦርነት ያቆም ዘንድም በ76ኛው የተመድ ጠቅላላ ጉባዔ ላይ የተገኙት የየመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አህመድ አዋድ ቢን ሙባረክ ጠይቀዋል፡፡
ዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ በሃውቲ ታጣቂዎችና ደጋፊዎች ላይ ጫና እንዲያሳርፍና የደም መፋሰሱ እንዲቆምም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
መንግሥት ለሰላም በተደጋጋሚ እጁን ዘርግቷል፣ ለሰላም ጥሪ ሁሉንም መንገድ ከፍተናል ያሉት ሚስተር ቢን ሙባረክ፣ እንዳለመታደል ሆኖ ሁሉም የሰላም ጥረቶች በሐውቲ ታጣቂዎችና በሚደግፋቸው ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል ብለዋል፡፡
መንግሥት የሚቆጣጠራቸውን አል ባይዳ፣ አባይን፣ አል ዳህሊና በሞካ ፖርት የሚኖሩ ሲቪሎች ላይ ጭምር የሚያደርሰውን ጥቃት እያፋፋመ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡
‹‹በመረብ የሃውቲ ሚሊሻዎች ኃላፊነት የጎደለው ወታደራዊ ዘመቻ ከጀመሩ አንድ ወር ሆኗቸዋል፣ ባለስቲክ ሚሳይል፣ ድሮንና ከባድ መሣሪያዎችንም እየተጠቀሙ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ታጣቂዎች በአደባባይ ዘጠኝ የመናውያንን መግደላቸውን፣ በርካቶችም እስር ቤት ሆነው ተራቸውን እየጠበቁ እንደሚገኙ፣ በሚስጥራዊ እስር ቤቶች ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞችና ወትዋቾች መታሰራቸውን አስታውሰዋል፡፡
በጦርነቱ ምክንያት የመን ለኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ቀውስ መዳረጓን፣ ደም መፍሰሱ ማየሉንና የሰላም አማራጭ ተቀባይነት አለማግኘቱን በመግለጽም፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በሀውቲ ታጣቂዎች ላይ ጫና እንዲያሳርፍ ለ76ኛው የተመድ ጠቅላላ ጉባዔ ታዳሚዎች ጥሪ አቅርበዋል፡፡
አሶሽየትድ ፕሬስ እንደዘገበው ደግሞ፣ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን የደኅንነት አማካሪ ጄክ ሱሊቫን ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ በሳምንቱ መጀመርያ አቅንተዋል፡፡
ሳዑዲ ዓረቢያ መራሹ ጦር የየመን መንግሥትን ደግፎ፣ ከአጋሮቹ አሜሪካ ፈረንሣይና እንግሊዝ ጋር በመሆን እጁን ካስገባ ወዲህ በየመን የተስፋፋው ጦርነትና ረሃብ ከ100 ሺዎች በላይ እንዲሞቱ ምክንያት ሆኗል፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠሩትን ደግሞ ለረሃብና መፈናቀል ዳርጓል፡፡
ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ያቀኑትና ከልዑል አልጋ ወራሽ መሐመድ ቢን ሳልማን ጋር ይወያያሉ የተባሉት ሚስተር ሱሊቫን፣ ከመወያያ አጀንዳቸው ከቀዳሚው የየመን መንግሥትን ወግነው በሚዋጉት የሳዑዲ ዓረቢያና በሀውቲ አማፅያን መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት ማድረግ ይገኝበታል፡፡
ሱሊቫን የሳዑዲ ምክትል መከላከያ ሚኒስትር ካሊድ ቢን ሳልማን ጋርም ይወያያሉ ተብሏል፡፡