ከቤተሰቦቼ ጋር ሆኜ የመስቀል በዓል ስናከብር ሳለ ስልኬ ጮኸ፡፡ ሳነሳው አንድ የማውቀው ሰው ነው የደወለልኝ፡፡ ትዊተር ላይ ጉደኛ ዜና አለልህ ብሎኝ ስልኩን ዘግቶ ወዲያው በቴሌግራም ማስፈንጠሪያ (ሊንክ) ላከልኝ፡፡ ምን ሰበር ዜና ይኖር ይሆን ብዬ ሳስብ አንዲት ወጣት ሚኒስትር ሥራዋን በገዛ ፈቃዷ መልቀቋን አውጃለች፡፡ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ኦፊሴል ደብዳቤ ላይ ምክንያቷን በመደርደር ውሳኔ ላይ መድረሷን በገደምዳሜ ገልጻለች፡፡ ወጣቷ ሚኒስትር ስለደረሰችበት ውሳኔ ስለማይመለከተኝ እንዲህ ነው፣ እንዲያ ነው ማለት አልፈልግም፡፡ ነገር ግን በጉዳዩ ላይ የሚነጋገሩ ሰዎችን አስተያየቶች ሳነብ አንድ ምሥራቅ አፍሪካዊ የወያኔ አፈ ቀላጤ፣ ‹‹ከሚሰምጥ ጀልባ ጋር ማን አብሮ ይሰምጣል…›› የሚል ሟርት ቢጤ ተጽፎ አየሁ፡፡ አገር ለማፍረስ የሚባዝነው ወንበዴ ቅጥረኛ ተላላኪ ሆኖ ትዊተር ላይ የሚያሸረግደው ይህ ምንደኛ አንድ ነገር አስታውሶኝ፣ ይህንን ማስታወሻ ለመጻፍ ተገደድኩ፡፡
ከአሥር ዓመት በፊት ይመስለኛል በምሠራበት መሥሪያ ቤት ውስጥ መካሄድ ስላለባቸው መሠረታዊ ለውጦች እየተነጋገርን ነበር፡፡ መሠረታዊ ለውጥ የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ምን እንደሆኑ ከለየን በኋላ እያንዳንዳቸውን በመተንተን ምን ያህል ድረስ ዘልቀን ለውጡን ማምጣት እንዳለብን ሐሳቦችን ተለዋወጥን፡፡ በውይይታችን ወቅት የተነሱት መሠረታዊ ችግሮች የግልጽነት አለመኖር፣ የተጠያቂነት ወሰን አለመታወቅ፣ ዳተኝነት፣ የብቃት ማነስ፣ አሉባልታ፣ የዲሲፕሊን ችግርና ሙስና ነበሩ፡፡ የእነዚህን ችግሮች መነሻ ምክንያቶች መተንተን ስንጀምር ግን በመካከላችን ውዝግብ መነሳት ጀመረ፡፡ ውዝግቡ ሁለት ጎራዎችን ቁልጭ አድርጎ አሳየን፡፡
የመጀመርያው ጎራ ሥር ነቀል ለውጥ መኖር አለበት በማለት ያጋጠሙትን ችግሮች ያለ ምንም ይሉኝታ ለመፍታት የሚጣጣርና ለአገር አሳቢ ሲሆን፣ ሁለተኛው ጎራ ደግሞ ያሉትን ችግሮች በማድበስበስ ለማለፍ የሚሞክር የሌቦች ጥርቅም ነው፡፡ ሥር ነቀል ለውጥ ፈላጊዎችና አድበስባሾች በተፋጠጡበት በዚህ ውይይት ላይ መግባባት ሊደረስ ባለመቻሉ፣ ሁለቱን ጎራ በማስማማት ወደ ማዕከላዊ ነጥብ ሊያመጣ የሚችል የድርድር ኮሚቴ እንዲቋቋም ጥያቄ ተነሳ፡፡ ሁለቱም ወገኖች የያዙትን አቋም ሳያረግቡ እያመነቱ ድርድሩን ለመቀበል ለጊዜው ተስማሙ፡፡ ይህንን ድርድር ያመቻቹት ገለልተኛ ሰዎች መካረሩ የትም ስለማያደርስ ውጤት ሊገኝ ይችላል ብለው በማሰብ ነበር፡፡
ከሁለቱም ወገኖች የተመረጡት አደራዳሪዎች መሠረታዊ የተባሉ ችግሮችን አንስተው የመነጋገሪያ አጀንዳ መምረጥ እንደሚኖርባቸው መነጋገር ሲጀምሩ፣ ዋናው ስብሰባ ላይ ያልተግባባንባቸው ችግሮች እዚህም መታየት ጀመሩ፡፡ አደራዳሪዎቹ በተለይ ከዘራፊዎቹ ጎራ የቤት ሥራ ተሰጥቷቸው የመጡ ይመስል የማደራደር ኃላፊነታቸውን ዘንግተው በበፊቱ ጭብጥ ላይ ያነታርኩን ጀመሩ፡፡ በዚህን ጊዜ በልምድም በዕድሜም ጠና ያሉ አንድ የሥራ ባልደረባችን ቆጣ ይሉና፣ ‹‹የእኛ ተግባር የምንወግንለትን ፍላጎት ማንፀባረቅ ሳይሆን፣ ለተቋማችን ይበጃል የሚባለውን ለውጥ ለማምጣት የሚረዱ በመረጃ ላይ የተመሠረቱ አማራጮችን ማሳየት ነው፡፡ በአንድ ጎራ ሴራ ንትርክ ስንጀምር ገለልተኛ የሆነ የድርድር ኮሚቴ መቋቋሙ ውዝግቦችን በማጥበብ አማካይ የመነጋገሪያ አጀንዳ ለመፍጠር ነው፡፡ ስለዚህ ቡድናዊ አስተሳሰባችንን ትተን የጋራ መነጋጋሪያ መድረክ እናመቻች፤›› አሉ፡፡
በእሳቸው መሪነት ቀደም ሲል የተነሱትንና የተነተኑትን ነጥቦችን ይዘን የሚያቀራርቡና ወደ ጋራ መፍትሔ የሚያመሩ ሐሳቦችን ማቅረብ ስንጀምር፣ የተወሰኑ የኮሚቴ አባላት ተንቀሳቃሽ ስልኮች መጮህ ጀመሩ፡፡ የአንዳንዶቹ ደግሞ የጽሑፍ መልዕክት ያስተናግዱ ጀመር፡፡ ለስልኮቻቸው ጥሪዎችና መልዕክቶች ምላሽ ለመስጠት የአምስት ደቂቃ ዕረፍት በስምምነት ተደረገ፡፡ ከዕረፍት ተመልሰን የጀመርነውን ሥራ ለመቀጠል ስንዘጋጅ የወጠንናቸው ሐሳቦች ምስቅልቅላቸው ይወጣ ጀመር፡፡ የኮሚቴው አባላት ከዘራፊው ቡድን አለቆች ጋር በ‹ቴክስት ሜሴጅ› እየተነጋገሩ ለካ ውይይታችን በሪሞት ኮንትሮል ይመራ ኖሯል፡፡ የወያኔ ጎራ አለቆች በሰጡት ትዕዛዝ መሠረት የድርድር ኮሚቴው ሥራ ተደነቃቅፎ ሳንስማማ ተበታተንን፡፡
ስለገጠሙን መሠረታዊ ችግሮች ተነጋግረን ድርጅታችንን ከገባበት ችግር ማውጣት ሲገባን መስማማት አልቻልንም፡፡ አለመስማማቱን በድርድር ለመፍታት ኮሚቴ ብናቋቁም እንዲበተን ተደረገ፡፡ በዚያን ጊዜ በፍፁም የማልረሳው ነገር ቢኖር የወያኔ ታዋቂ ሰዎች ጭምር ከጀርባ ሆነው ለአገር የሚበጀውን ሥራችንን ሲያፈራርሱ፣ ወደውም ሆነ ተገደው የሴራቸው ተካፋይ እንዲሆኑ የተደረጉ ሰዎች ጭንቀት አይረሳኝም፡፡ በሌላ በኩል በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የጥቅም ተካፋይ የነበሩት ደግሞ፣ የደም ሥራቸው እስኪገታተር ድረስ ከባድ ትግል ገጥመው ነበር፡፡ በአሻጥርና በተንኮል መረብ የተተበተበው ወያኔ ታች ድረስ እየወረደ ነበር አገርን ይገዘግዝ የነበረው፡፡
ይህ ነገር እየከነከነኝ ሳለ አንድ የሥራ ባልደረባዬ ከድርጅቱ ሊለቅ መሆኑን ከአንድ ሰው ሰማሁ፡፡ ይህ ከፍተኛ ዕውቀትና ችሎታ ያለው ሰው ድርጅቱን እንደሚለቅ አልነገረኝም፡፡ እንዲያውም በርካታ ዕቅዶች እንዳሉት ነበር የማውቀው፡፡ የእሱ የመልቀቅ ዜና እያበሳጨኝ ላናግረው ወደ ቢሮው ስሄድ የለም፡፡ አብሮት ያለውን አንድ ሰው፣ ‹‹ምን ተፈጠረ?›› በማለት ጥያቄ አቀረብኩለት፡፡ ‹‹ላለፉት ሁለት ዓመታት ጥርሱን ነክሶ ሲሠራ የነበረው ይህንን ድርጅት ከማጥ ውስጥ በማውጣት የስኬት ምሳሌ ለማድረግ ነበር፡፡ አሁን ግን እንደማይቻል ስለታወቀው በቃኝ አለ፤›› አለኝ፡፡ ለተወሰነ ጊዜ መታገስ እንዳለበት በወዳጅነት መልክ ለምን እንደማይነግረው ስጠይቀው፣ ‹‹ወንድሜ አንተም ይብቃህ፣ ለውጥ ከማይቀበሉ ኃይሎች ጋር ትግል ሰልችቶኛል፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ እየሰመጠ ካለ የወያኔ ጀልባ ጋር ለምን ጊዜዬን አጠፋለሁ ነው ያለኝ፤›› ብሎኝ እሱም ጓዙን እያመቻቸ ሊለቅ መሆኑን ነገረኝ፡፡
ይህ ሁሉ የተፈጸመው እንግዲህ ሕወሓት መራሹ መንግሥት አገር በሚያተራምስበትና በሕዝብ በተጠላበት ዘመን ነው፡፡ ዛሬ ሕዝብ አገሬን እያለ ሲፋለማቸው ከእነ ተላላኪዎቻቸው እያሻጠሩ ሊያደናግሩን ቢሞክሩም አይሳካላቸውም፡፡ የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ወያኔ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ተወግዶ፣ ሰላም ሲሰፍንና ወጀቡ ሲቆም ተላላኪዎቹም ብን ብለው ይጠፋሉ፡፡ ይህ ደግሞ መላመት ሳይሆን እርግጥ ነው፡፡ ወጣቷ ሚኒስትርም በራሷ ምክንያት ከሥራዋ መልቀቋን ማሳወቋ እንዳለ ሆኖ፣ ለራሷም ሆነ ለወገኖቿ ስትል የወያኔዎች የፕሮፓጋንዳ ሰለባ ሆና ታሪኳን እንዳታበላሽ በወንድምነት አሳስባታለሁ፡፡ ከወያኔ ጋር ያበረ ከውርደት በስተቀር ክብር የለውምና፡፡
(ዘማርያም ዮሐንስ፣ ከሰሚት)