በሕግ የበላይነት፣ በፍትሕና ሰብአዊ መብት መከበር ላይ በትኩረት የሚሠራ፣ በፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ስም የተሰየመ ፋውንዴሽን ተቋቋመ፡፡
ፋውንዴሽኑ በማኅበረሰብ ሳይንስና ሰብዓዊ መብት ጥበቃ ምርምር ለሚያደርጉ ወጣቶችና ተመራማሪዎች ድጋፍ እንደሚያደርግም፣ መስከረም 27 ቀን 2014 ዓ.ም. በቀድሞው ኢንተርኮንቲኔንታል በአዲሱ አጠራር ኢንተር ለግዠሪ ሆቴል በተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተገልጿል።
በሰብዓዊ መብት ተሟጋችና የአደባባይ ምሁሩ መስፍን ወልደማርያም (ፕሮፌሰር) ስም የተቋቋመው ፋውንዴሽን የቦርድ ሰብሳቢ በድሉ ዋቅጅራ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ፋውንዴሽኑ ከመንግሥት፣ ከሃይማኖት፣ ከጎሳና ከማንኛውም የፖለቲካ አመለካከት ወገንተኝነት ነፃ ነው።
የፕሮፌሰሩን በጎ ሐሳብ የሚጋሩ ሰዎች ሥራቸውን የማስቀጠል፣ ቤተሰቦቻቸው ጭምር ተሳትፈውበት የተመሠረተ ነው ያሉት ሰብሳቢው፣ ፋውንዴሽኑ ከድህነት የተላቀቀች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የበኩሉን አስተዋፅኦ ለማድረግ መመሥረቱን ይፋ አድርገዋል፡፡
‹‹ለሕግ የበላይነት፣ ለፍትሕ መከበርና የሰብአዊ መብት መከበር ላይ በትኩረት ይሠራል። በማኅበረሰብ ሳይንስና ሰብዓዊ መብት ጥበቃ ምርምር ለሚያደርጉ ወጣቶችና ተመራማሪዎችም ድጋፍ ያደርጋል፤›› ሲሉም የቦርድ ሰብሳቢው አሳውቀዋል፡፡ በዩኒቨርሲቲዎችና በከተሞች የማንበቢያ ማዕከላትና ላይብረሪዎች በፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ስም እንዲከፈት፣ እንዲሁም የታተሙና ያልታተሙ መጽሐፎቻቸው ታትመው ለሕዝብ ተደራሽ ለማድረግ በፋውንዴሽኑ እንደሚሠራም አመላክተዋል።
ዓምና መስከረም 19 ቀን 2013 ዓ.ም. በ90 ዓመታቸው ያረፉት ነፍስ ኄር መስፍን ወልደማርያም፣ በኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ላይ ሐሳባቸውን ለማንፀባረቅ ችላ የማይሉ፣ ዕውቀታቸውንና ምልከታቸውን በአደባባይ ለማስተጋባት የሚተጉ ነበሩ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም፡፡
‹‹ነፃ ሐሳብ ለነፃ ሕዝብ›› የሚል አስተምህሮ የነበራቸው ያንንም ለመተግበር ዕውንም ለማድረግ ወደ ኋላ ማለት ማፈግፈግን ዞር በል የሚሉ ናቸው ይሏቸዋል፡፡ ለሰብዓዊ መብቶች መከበር ከሦስት አሠርታት ወዲህ ኢሰመጉን በመመሥረት ያሳዩት ተላሚነት ይበልታን አስገኝቶላቸዋል፡፡
ከዘውዳዊው ሥርዓት እስከ ወታደራዊው የደርግ መንግሥት፣ ከሕዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊኩ እስከ አሁን ዘመኑ ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ መንግሥታት ድረስ የሽግግር ዘመኑንም ጨምሮ በገሀድ በመሔስ የሚሰማቸውን በመጣጥፍና በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በመግለጽ በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ፡፡ በተለይ ደርግ ወድቆ ኢሕአዴግ መንበረ ሥልጣኑን ሲጨብጥ በሽግግሩ ዘመን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከወቅቱ የሽግግር መንግሥቱ ፕሬዚዳንት አቶ መለስ ዜናዊ ጋር ክርክር የገጠሙበት መንገድም (ሌሎች ምሁራን ጨምሮ) በብዙዎች ዘንድ ይታወሳል፡፡
በ1950ዎቹና በ1960ዎቹ በሰሜን ኢትዮጵያ የደረሰውን ድርቅና ረሃብ ተከትሎ የተፈጠረውን ቀውስ ይፋ በማድረግ የሚጠቀሱት፣ በስሚ ስሚ ያገኙትን ሳይሆን በተለያዩ አካባቢዎች በመገኘት ያዩትን የተመለከቱትን በፎቶግራፍ ጭምር በማስደገፍ ከባልደረቦቻቸው ጋር መጣራቸው ይወሳላቸዋል፡፡ በርሳቸው አገላለጽ ‹‹ጠኔ›› የሚባለውን ረሃብ አስመልክቶ መፍትሔ ማሳያ መጽሐፍም እስከ ማዘጋጀት መድረሳቸው ገጸ ታሪካቸው ያሳያል፡፡
ከባህር ማዶ የቅድመና ድኅረ ምረቃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ የሥራውን ገበታ የተቀላቀሉት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲን ነው፡፡ በዘመኑ ጥቂት ምሁራን ብቻ የሚያደርጉትን ለሚያስተምሩት ትምህርት የመማርያ መጽሐፍ በማዘጋጀት ረገድም ዓይነተኛ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
በአካዴሚያ ሕይወታቸው ለፕሮፌሰርነት የበቁበት የጂኦግራፊያ መምህርነታቸው የኢትዮጵያን መልክዓ ምድር በጥልቀት የሚያሳይ መጽሐፍን አበርክተዋል፡፡ የትምህርት ክፍሉንም እስከ መምራት ደርሰዋል፡፡