ትግራይ ክልል ውስጥ ባሉ ዩኒቨርሲቲዎችና በወልዲያ ዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩ ተማሪዎች፣ በጊዜያዊነት በሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች እንዲመደቡ ውሳኔ ማስተላለፉን ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ሚኒስቴሩ በአሸባሪነት በተፈረጀው ሕወሓት ታጣቂዎች እየተቀጣጠለ በመጣው ጦርነት ምክንያት፣ በትግራይ ክልል በመቀሌ፣ በአክሱምና በአዲግራት ዩኒቨርሲቲዎችና በወልዲያ ዩኒቨርሲቲ ሲማሩ የነበሩ ተማሪዎች፣ በጊዜያዊነት በሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች እንዲመደቡ ውሳኔ ማስተላለፉን ያስታወቀው ማክሰኞ ጥቅምት 9 ቀን 2014 ዓ.ም. ነው፡፡
በተጠቀሱት ዩኒቨርሲቲዎች ሲማሩ የነበሩ ተማሪዎች ወደ ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች በጊዜዊነት ለመመደብ፣ የመመዝገቢያ ገጽ ተከፍቶ ተማሪዎች እንዲመዘገቡ ጥሪ አድርጓል፡፡ ምዝገባው ሲጠናቀቅ ምደባ የሚደረግ መሆኑን የተገኘው መረጃ ያስረዳል፡፡
በዩኒቨርሲቲዎቹ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩ ተማሪዎች አስፈላጊውን የትምህርት ማስረጃ በማዘጋጀት፣ ከጥቅምት 9 ቀን ጀምሮ እስከ ጥቅምት 12 ቀን 2014 ዓ.ም. ድረስ መመዝገብ እንደሚችሉ ተገልጿል፡፡
ሪፖርተርም ጉዳዩን በተመለከተ ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት የትምህርት ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊዋን ወ/ሮ ሐረግ ማሞ ለማናገር ጥረት ቢያደርግም፣ ጉዳዩ እንደማይመለከታቸውና የሚመለከታቸው ኃላፊዎች ስብሰባ ላይ እንደሆኑ የተለመደ ምላሽ በመስጠታቸው አልተሳካም፡፡
ከዚህ ቀደም በ2013 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን ከአዲግራት፣ ከአክሱምና ከመቀሌ ዩኒቨርሲቲዎች ተመራቂ የነበሩ ተማሪዎች ባልተጠናቀቁ የትምህርት መርሐ ግብሮች ምክንያት ትምህርታቸውን አጠናቀው አለመመረቃቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡