በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በጉጂና በቦረና ዞኖች የዝናብ እጥረት በመከሰቱ፣ ከ395 ሺሕ በላይ ዜጎች አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው፣ የሁለቱ ዞኖች የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ቢሮዎች አስታወቁ።
የጉጂ ዞን የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ገመቹ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ቆላማው የዞኑ አከባቢዎች በ2013 ዓ.ም. የተመረተው የእህል ምርት በቂ አይደለም፡፡ ዘንድሮም የተጠበቀው ዝናብ በወቅቱ ባለመዝነቡ የአካባቢው ማኅበረሰብ ለችግር ተጋልጧል ብለዋል።
በወረዳዎቹ የአስቸኳይ ጊዜ የምግብ ዕርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች 229,000 መሆናቸውንና ሴቶች፣ ሕፃናት፣ ነፍሰ ጡሮችና ሌሎችም የኅብረተሰብ ክፍሎች ይገኙበታል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታው ለሁሉም ተረጂዎች አስፈላጊ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፣ በይበልጥ ሕፃናትና ሴቶች ላይ ችግሩ የጎላ በመሆኑ ዕርዳታው በእጅጉ አስፈላጊ ነው ብለዋል።
በአካባቢው ከሚያዝያ (ሀጌያ) ወር 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ይጠበቅ የነበረው ዝናብ ባለመዝነቡ፣ በሌላ በኩል ከመስከረም 16 ቀን 2014 ዓ.ም. ጀምሮ የሚጠበቀው ዝናብ ሳይዘንብ በመቅረቱ የአካባቢው ማኅበረሰብ ለከፋ ችግር መጋለጡን አቶ ተስፋዬ ተናግረዋል፡፡
በዞኑ ካሉት 13 ወረዳዎችና ሦስት የከተማ አስተዳደሮች ውስጥ በስድስት ወረዳዎች ድርቅ የተከሰተ መሆኑን፣ ከእነዚህ ውስጥ ደግሞ አራቱ ወረዳዎች ድርቁ በይበልጥ የጎዳቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ሰባቦሩ፣ ሊበን፣ ጎሮ ዶላና ጉሜ ኤልደሎ ወረዳዎች ችግሩ ይበልጥ የሚጎላባቸው መሆናቸውን ኃላፊው ገልጸዋል፡፡
በአራቱ የዞኑ ወረዳዎች ችግሩን የከፋ የሚያደርገው ከፍተኛ የፀጥታ ችግር በመኖሩ መሆኑን፣ የድርቅ አደጋ ሲጨመርበት ደግሞ ኅብረተሰቡ ለውስብስብ ችግሮች መጋለጡን ጠቁመዋል፡፡
መንግሥት ማድረግ ስለሚገባው የመፍትሔ ዕርምጃ፣ በየደረጃው ባለው ኮሚቴ መረጃዎች ተቀናጅተው ለማስተላለፍ እየተሠራ መሆኑን ኃላፊው ገልጸዋል።
የቦረና ዞን የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኃላፊ አቶ ሊበን ከበደ እንደተናገሩት፣ በዞኑ ከሚገኙ 13 ወረዳዎች ሙሉ ለሙሉ በድርቅ የተጎዱ ናቸው፡፡ አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ የሚስፈልጋቸው ደግሞ 166,000 ዜጎች ናቸው ብለዋል።
በዞኑ በተለያዩ የመንግሥትና የግል ተቋማት ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን፣ ነገር ግን ከችግሩ ስፋት አኳያ ድጋፉ በቂ እንዳልሆነ ተገልጿል።
በጉጂ ዞን በድርቅ የተጎዱ ዜጎች ሪፖርተር ቃለ መጠይቁን እስካደረገበት ጥቅምት 10 ቀን 2014 ዓ.ም. ድረስ ዕርዳታ እንዳላገኙ፣ የጎሮ ዶላ ወረዳ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኃላፊ አቶ አዲሱ አዶላ ተናግረዋል፡፡
በተለይም በአራቱ የዞኑ ወረዳዎች ችግሩን የከፋ የሚያደርገው፣ የመንግሥት ኃላፊዎች በፀጥታ ችግር ምክንያት መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
የኦሮሚያ ክልል የአደጋ ሥጋት አመራር ምክትል ኃላፊ አቶ ገረሙ ኦሊቃ እንደተናገሩት፣ የጉጂና ቦረና ዞኖች በዓመት ሁለቴ የዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎች ናቸው፡፡
በሚያዝያ ወር (ሀጌያ) በቂ ዝናበ ያላገኙ መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ኃላፊው፣ ከመስከረም 16 ቀን ጀምሮ ይጠበቅ የነበረውን ዝናብ አካባቢው አላገኘም ሲሉ አስረድተዋል፡፡
በቦረና ዞን ካሉት ወረዳዎች በአብዛኞቹ በቂ ዝናብ ባለመዝነቡና በረሃማ በመሆናቸው፣ በጥቂት ጊዜ ቶሎ ለከፋ ችግር የሚጋለጡ ቦታዎች መሆናቸውን ኃላፊው ገልጸዋል፡፡
ይህ ችግር ከመከሰቱ በፊት 30 ሚሊዮን ብር መመደቡን የገለጹት አቶ ገረሙ፣ ችግሩን ለመፍታት በጀቱ ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል፡፡
በቦረና ዞን ችግሩን ለመፍታት በተለያዩ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች፣ በአባ-ገዳዎችና የዞኑ ጎረቤት ከሆኑ አካባቢዎች ዕርዳታ እየተሰበሰበ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡