መንግሥት የአስፈጻሚ አካላትን እንደገና ለማደራጀትና ለማቋቋም ባወጣው አዋጅ መሠረት የባህልና ስፖርት ሚኒስቴርን እንዲመሩ የተሾሙት አቶ ቀጀላ መርዳሳ ተቋሙን በኃላፊነት ለማስተዳደር ከተመደቡበት ዕለት ጀምሮ የሚባክን ጊዜ እንደሌለ መግለጻቸው ተነገረ፡፡
ሚኒስትሩ አቶ ቀጀላ መርዳሳ ይህንን ያሉት ጥቅምት 19 ቀን 2014 ዓ.ም. በአዲስ መልክ ከተዋቀረው ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት አመራሮችና ሠራተኞች ጋር በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ በተዋወቁበት ወቅት መሆኑ የቀድሞ ስፖርት ኮሚሽን በማኅበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል፡፡
እንደ አለመታደል ሆኖ የአገሪቱ ስፖርት ከምሥረታው ጀምሮ እስካሁን ለተለያዩ ሚኒስቴሮች ተጠሪ ሆኖ ቆይቷል፡፡ በስፖርቱ መዋቅራዊ ሒደት ዙሪያ የቀረቡ መዛግብት እንደሚያስረዱት ከሆነ፣ በንጉሠ ነገሥቱ ጊዜ የኢትዮጵያ ሕዝብ ስፖርት ኮንፌዴሬሽን (ኢሕስኮ) በዘመነ ደርግ የመጀመርያ ዓመታት የባህል ወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ነበር፡፡ በዚያው ዘመን ራሱን ችሎ ስፖርት ኮሚሽን፣ በመሐል ላይ እንደገና የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ሆኖ እስከ ሽግግር መንግሥቱ ዘልቋል፡፡
በዘመነ ኢሕዴግ ራሱን ችሎ ስፖርት ኮሚሽን ሆኖ ከቀጠለ በኋላ፣ እንደገና የባህል የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር፣ በመሐል ላይ ባህል የሚለው እንዲወጣ ተደርጎ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር፣ በቅርቡ ደግሞ ስፖርት ኮሚሽን ሆኖ የባህልና ቱሪዝም ተጠሪ ተቋም፣ አሁን ደግሞ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ተብሎ ተደራጅቷል፡፡
የአገሪቱ ስፖርት በዚህ መልክ አንዴ ራሱን ችሎ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ከሌላ ተቋማት ጋር እየተደራጀና እየተዋቀረ አልያም ደግሞ ተጠሪ እየሆነ መዝለቁ ከዘርፉ ጋር ተያይዞ በየጊዜው ለሚፈጠሩ ችግሮችና ተግዳሮቶች መንስዔ ተደርጎ እንደሚጠቀስ የሚናገሩ አሉ፡፡
በቅርቡ መንግሥት የአስፈጻሚ አካላትን እንደገና ለማደራጀትና ለማቋቋም ባወጣው አዋጅ መሠረት ስፖርቱን ከባህል ጋር እንዲያስተዳድሩ በሚኒስትርነት የተሾሙት አቶ ቀጀላ መርዳሳ፣ በትውውቅ ፕሮግራሙ ወቅት ለዓመታት መፍትሔ ማግኘት ያልቻለው ስፖርቱ ውስጥ ያለው መገፋፋትና መጠላለፍ ምን ያህል ሥር የሰደደ መሆኑን በመግለጽ፣ ችግሩን ለመፍታት ለሰዓታት እንኳን የሚባክን ጊዜ እንደሌለ መግለጻቸው ተነግሯል፡፡
ሚኒስትሩ የተጣለባቸው ኃላፊነት ቀላል የሚባል እንዳልሆነ፣ በተለይ በስፖርቱ ውስጥ በርካታ ፍላጎቶች የሚስተዋሉበትና የሚንፀባረቁበት ከመሆኑ አኳያ ከሠራተኛው ጋር እጅ ለእጅ በመያያዝ ኢትዮጵያን ወደ ፊት አንድ ዕርምጃ ለማራመድ እንደሚሠሩ እምነታቸው ስለመሆኑ ጭምር ተናግረዋል፡፡
ባህልና ስፖርቱን በአንድ ተቋም በአጭር ጊዜ ውስጥ በማደራጀት ወደ ተሟላ ሥራ ለመግባት ዕቅድ እንዳላቸው፣ ለዚህ ደግሞ የመጀመሪያ የሆነውን የአንድ መቶ ቀናት ተግባራት መዘጋጀቱን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ‹‹ከዛሬ ጀምሮ አንድም ቀን፣ አንድም ሰዓት ያለሥራ የምናሳልፈውና የምናባክነው ጊዜ አይኖርም፣ ሁሉም ሠራተኛ ዕቅዱን መነሻ በማድረግ ሥራውን በትጋትና በጥንቃቄ ሊያከናውን ይገባል፣›› ማለታቸው ታውቋል፡፡