- የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አስገዳጅ የቦንድ ግዥ እንዲነሳለት ጥያቄ አቅርቧል
የኢትዮጵያ ልማት ባንክን ለመደገፍ ባንኮች የጥቅል ብድራቸውን አንድ በመቶ ለቦንድ ግዥ እንዲያውሉ የሚያስገድደው መመርያ ከወለድ አልባ ባንኮች አሠራር ጋር እንደሚቃረን ተጠቆመ።
ከሁለት ወራት በፊት ተግባራዊ የተደረገውን ቦንድ የመክፈያ ጊዜ ሲደርስ ሦስት በመቶ ወለድ ለባንኮች እንዲከፈል የሚያስገድድ ሲሆን፣ ይህም ወለድ አልባ ባንኮች ከሚከተሉት ሸሪዓ ሕግ ጋር የሚፃረር መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ፋይናንስ ኢንዱስትሪውን በ850 ሚሊዮን ብር የተቀላቀለው የዘምዘም ባንክ የስትራቴጂክ ዕቅድ ዲፓርትመንት ዳይሬክተር አቶ ከድር አባስ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ወለድ አልባ ባንኮች ወለድ የሚከፍል ቦንድ ግዥ መፈጸም የማይችሉ በመሆኑ ከተፈጠሩበት ዓላማ ጋር እንደሚቃረን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ የወለድ አልባ ባንክ አገልግሎት መስጠት ከተጀመረ ከስምንት ዓመታት በላይ ቢያስቆጥርም፣ በመስኮት ደረጃ ተገድቦ የነበረው አገልግሎት ወደ ሙሉ ባንክ አገልግሎት እንዲያድግ ከዛሬ ሦስት ዓመታት አንስቶ መወሰኑን ተከትሎ ለሁለት ባንኮች ፈቃድ ተሰጥቷል።
ከዘምዘም ባንክ በተጨማሪ ሒጅራ ባንክ ከተቀላቀሉት ወለድ አልባ ባንኮች መካከል ሲሆን፣ በ700 ሚሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታል የፋይናንስ ዘርፉን የተቀላቀለው ባለፈው ዓመት ነው። አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የባንኩ የሥራ ኃላፊ ለሪፖርተር እንደናገሩት፣ የቦንድ ግዥን አስገዳጅ የሚያደርገውን መመርያ ጨምሮ ብሔራዊ ባንክ ሌሎች የፋይናንስ ሕጎችን ከወለድ ነፃ አገልግሎት ሰጪዎች አሠራር አኳያ ሊፈተሽ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በተመሳሳይ በቦንድ ፈንታ የወለድ አልባ ባንኮች ልማት ባንክን ሊደግፉ የሚችሉበት አማራጭ እንዳለ ተናግረዋል። ለአብነትም ሙዳራባህ የተሰኘውን የወለድ ባንክ አገልግሎት ዓይነት ያነሱ ሲሆን፣ ይህም ወለድ አልባ ባንኮች ተበዳሪው ሊያከናውን ያሰበው ፕሮጀክት ላይ ትርፍ ተጋሪ በመሆን ፋይናንስ ማቅረብ እንዲችሉ ያስችላቸዋል በማለት አክለዋል።
ይህ በሚደረግበት ጊዜ ተበዳሪው የሚሠራው ፕሮጀክት ከሸሪዓ ሕግ ጋር አብሮ የሚሄድ መሆኑን ማረጋገጥ ይገባል ያሉት አቶ ከድር፣ ልማት ባንክም የወለድ አልባ ፋይናንስ የሚያቀርብበት ራሱን የቻለ ክፍል ሊያቋቁም እንደሚገባ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የሥራ ኃላፊዎች በወለድ አልባ ባንኮች በኩል የቀረበውን የመፍትሔ ሐሳብ በማጤን ላይ መሆናቸውን የባንኩ ምክትል ገዥና ቺፍ ኢኮኖሚስት ፈቃዱ ድጋፌ የተናገሩ ሲሆን፣ ማሻሻያ ሊደረግ እንደሚችል ጠቁመዋል።
በሌላ በኩል አጠቃላይ የብድር ክምችቱ 700 ቢሊዮን ብር የደረሰው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአስገዳጅ ቦንድ ግዥ ደስተኛ አለመሆኑን ለሪፖርተር ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የመንግሥት ፕሮጀክቶችን የሚደግፍ እንደመሆኑ መጠን ሊነሳለት እንደሚገባ ጠቁሟል።
‹‹ከዓመታዊ የብድር አቅርቦት ሳይሆን ከአጠቃላይ የብድር ክምችት አንድ በመቶ ለቦንድ ግዥ እንዲውል ማስገደዱ ባንኮችን ይጎዳል፤›› ያሉት የንግድ ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት ሙሉነህ አቦዬ፣ ‹‹መመርያው አገራዊ ፋይዳ ያላቸውን ፕሮጀክቶች እንደሚደግፈው መጠን መመርያው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ላይ ሊተገበር አይገባም፤›› ብለዋል።
በተመሳሳይ የግል ባንኮችም አስገዳጅ መመርያው ላይ ማስተካከያ እንዲደረግ በማኅበራቸው በኩል ጥናት አስጠንተው ለብሔራዊ ባንክ ቅሬታቸውን ለማቅረብ ዝግጅታቸውን ጨርሰዋል። ባንኮቹ በጥናታቸው ላይ እንደገለጹት፣ ተፎካካሪያቸው የሆነውን ልማት ባንክ እንዲደግፉ መጠየቃቸው ፍትሐዊ አይደለም፡፡ የቦንድ ግዥ ይፈጸም የተባለው በየዓመቱ ከሚሰጥ ብድር ላይ ሳይሆን ከተከማቸ ብድር ላይ ጭምር መሆኑ የባንኮችን አቅም ያዳክማል ብለዋል።
እስካለፈው ዓመት መጨረሻ ድረስ የብድር ክምችታቸው 1.3 ትሪሊዮን ብር የደረሰው ባንኮች ከዚህ ቀደም ከሚሰጧቸው እያንዳንዱ ብድሮች 27 በመቶ የሚሆነውን ልማት ባንክን ለመደገፍ የሚውል ቦንድ ግዥ ማዋል ይጠበቅባቸው የነበረ ሲሆን፣ መመርያው የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ሊሻር ችሏል።
ይህም የባንኮችን የማበደር አቅም በከፍተኛ ሁኔታ አሳድጎታል፡፡ እንደ ኮቪድ-19 እና የፖለቲካ አለመረጋጋት ችግር በገጠማቸው ጊዜ እንኳን ትርፋማ ሆነው እንዲቀጥሉ ትልቅ ሚና ተጫውቷል።
ይሁን እንጂ ከያዝነው ዓመት አንስቶ የወጡ መመርያዎች ትርፋማነታቸው ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳያሳድር ሥጋት ጭሯል። ለአብነትም ለብሔራዊ ባንክ የሚያስረክቡት የውጭ ምንዛሪ መጠን ወደ 50 በመቶ ከፍ ማለቱንና የሚያስቀምጡት የመጠባበቂያ ገንዘብ ከአምስት ወደ 10 በመቶ ከፍ ማለቱን መጥቀስ ይቻላል።
በተጨማሪም በኢትዮጵያ የሰሜን ክፍል ባሉ ከተሞች ባንኮች አገልግሎት ማቋረጣቸው የቁጠባና የብድር አሰባሰብ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሯል፡፡ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ደንበኞቻቸውን እንዲያጡም ምክንያት ሆኗል።