በአዲስ አበባ የሚገኙ የተወሰኑ ኤምባሲዎች ጥበቃ የሚያደርጉላቸው ወታደሮችን ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት ጥያቄ ማቅረባቸው ‹‹አስቂኝ ነው›› ሲል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ተቀማጭነታቸው በኢትዮጵያ የሆነ የተወሰኑ ኤምባሲዎች ዜጎቻቸው ከአገር እንዲወጡ እያደረጉ ቢሆንም፣ የተወሰኑት ድሮ ከነበራቸው የሠራተኛ ቁጥር በሦስትና በአራት እጥፍ የሚልቁ ሠራተኞችና ጠባቂ ወታደሮችን ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት ጥያቄ ማቅረባቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገልጿል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዲና ሙፍቲ (አምባሳደር) በሳምንታዊ መግለጫቸው፣ ኤምባሲዎች ሊጠብቁን የሚችሉ ወታደሮችን እናስገባ ብለው ያቀረቡት ጥያቄ አስቂኝና ‹‹ምፀት›› የተሞላበት እንቅስቃሴ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
ኤምባሲዎቹ ዜጎቻቸው ከአገር እንዲወጡ እያደረጉት ያለው እንቅስቃሴ ሆነ ተብሎ የኢትዮጵያን መንግሥት ለማንበርከክ፣ የመከላከያው ሠራዊቱን ለማዳከምና የሕዝቡን ስሜት ተስፋ ለማስቆረጥ የሚደረግ ሴራ እንደሆነ አክለው ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም የሕወሓት ታጣቂዎች እዚህ ደረሱ፣ እዚያ ደረሱ በሚል በተለያዩ ዓለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማት በሐሰት ሲሠራጭ የነበረው የቅስቀሳ አካል መሆኑን፣ በሕዝቡ ላይ ደግሞ የሥነ ልቦና ጦርነት ለመክፈት እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
ይሁን እንጂ አንዳንድ ኤምሳቢዎች ጉዳዩን ባለማወቅ ከአገር ለመውጣት እንደሚውስኑ፣ ከተወሰኑት ጋርም በመነጋገርና መረጃ በመለዋወጥ እንዲረጋጉ እየተደረገ መሆኑን ቃል አቀባዩ ጠቁመዋል፡፡
ጉዳዩን በግልጽ እያወቁና የሕወሓት ታጣቂዎች እየሸሹ መሆናቸውን ጭምር እያወቁ፣ በሥጋት ሰበብ የውጭ ዜጎች ከአገር እየወጡ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ጫና ለማድረግ የሚደረግ ሴራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አንዳንዶቹ ሕወሓትን በሳተላይት አገራቸው ሆነው ሲመሩ እንደነበር በመጥቀስ፣ አሁን እየተከናወነ ያለውን እንቅስቃሴም በግልጽ እያወቁ በተለይም ሕወሓት ከያዛቸው ቦታዎች እየሸሸና እያፈገፈገ መሆኑን እየተረዱ የሚያደርጉት ሴራ ነው ብለዋል፡፡
የሕወሓት ታጣቂዎች ወደ ደቡብ ወሎ ከተሞች ገቡ መባሉን ተከትሎ የአሜሪካ፣ የአውሮፓና የሌሎች አገሮች በኢትዮጵያ የሚገኙ ዜጎቻቸውን ከአገር ለቀው እንዲወጡ ጥሪ ማስተላለፋቸው ይታወሳል፡፡
እየተካሄደ ባለው ጦርነት የኢትዮጵያ መንግሥት በአየርም ሆነ በምድር የኃይል የበላይነት እንዳለው ምንም ጥያቄ የለውም ያሉት ዲና (አምባሳደር)፣ መንግሥት ሁልጊዜም ለሰላም ዝግጁ እንደሆነ አመላክተዋል፡፡
ይሁን እንጂ ለዚህ ሰላማዊ ሒደት መሳካት የሕወሓት አመራሮች በሥልጣን ላይ ላለው የፌዴራል መንግሥት ዕውቅና መስጠት፣ ታጣቂዎቻቸው አሁን ከያዟቸው የአማራና የአፋር ክልሎች ለቀው መውጣት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡
በመሆኑም እነዚህና ሌሎች የሰላም እንቅፋት የሆኑ ጉዳዮች እስከተሟሉ ድረስ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ለሰላም ዝግጁ ነው ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ ጉብኝት እያደረጉ የሚገኙትና ከመንግሥትና ከሕወሓት ኃይሎች ጋር እየተነጋገሩ ያሉት የቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዚዳንትና የአፍሪካ ኅብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ኦሊሴጎን ኦባሳንጆ፣ በኢትዮጵያ እየሆነ ያለውን እውነታ ፍለጋ ላይ መሆናቸውን ቃል አቀባዩ ተናግረዋል፡፡
‹‹መልዕክተኛው በአገር ውስጥ ምን እንዳዩ፣ ምን እንደተገነዘቡና ምን ለማድረግ እንደፈለጉ ወደፊት ዓይተን የምንወስን ይሆናል፤›› ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል ከመንግሥት የሕግ ማስከበር ዘመቻና ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጋር በተያያዘ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሠራተኞች ታስረውብኛል በሚል ለወጣው መረጃ፣ ምን ያህል እንደታሰሩ መረጃው እንደሌላቸው ተናግረዋል፡
ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀስ የተመድም ይሁን የአፍሪካ ኅብረት ወይም ሌላ አካል የአገሪቱን ሕግ ማስከበር እንዳለበት ገልጸዋል፡፡
የአገሪቱን ሕግ ያላከበረ የማንኛውም አገር ዜጋ ወይም ሠራተኛ ካጠፋ፣ የተመድ ሠራተኛ በመሆኑ ‹‹ወደ ቀኝ ሲነዳ ወደ ግራ›› ሊል እንደማይችልና የአገሪቱን ሕግ ማክበር ግድ እንደሚለው አስታውቀዋል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት በኢትዮጵያ ላይ የሚያደርገውን የበረታ ጫና በተመለከተ፣ ‹‹እኔም አይገባኝም፣ መመርመር ይጠይቃል፤›› ያሉት ቃል አቀባዩ፣ የአሜሪካ መንግሥት ከአጎዋ ተጠቃሚነት ኢትዮጵያን ማገዱ በኢትዮጵያ ያለውን ሰፊ ሕዝብ ከመጉዳት ባለፈ፣ የኢትዮጵያና የአሜሪካ ግንኙነትን ጥርጣሬ ላይ ይጥለዋል ብለዋል፡፡