የመንግሥት ልማት ድርጅቶች በ2014 የበጀት ዓመት የመጀመሪያ ሦስት ወራት ውስጥ ከ60 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸው ተገለጸ።
የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታ አስተዳደር ኤጀንሲ ሥር የሚተዳደሩት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች፣ የበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸም በተጠናቀቀው ሳምንት በተገመገመበት ወቅት እንደተገለጸው፣ የልማት ድርጅቶቹ በሩብ ዓመቱ (በሦስት ወራት ) ውስጥ 60.2 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘታቸው ታውቋል።
የመንግሥት ልማት ድርጅቶቹ ከሚያቀርቡት ምርትና አገልግሎት ሽያጭ ካገኙት አጠቃላይ ገቢ ውስጥ ትልቁን ድርሻ የያዘው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሦስት ወራት ያገኘው ገቢ ሲሆን፣ ኢትዮ ቴሌኮምና የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ደግሞ ሁለተኛና ሦስተኛ ሆነዋል።
በሁለተኛ ደረጃ ትልቁን ገቢ ማግኘት የቻለው ኢትዮ ቴሌኮም ሲሆን፣ ኩባንያው በተጠቀሱት ሦስት ወራት ውስጥ 13.54 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱ ታውቋል።
ኢትዮ ቴሌኮም በሩብ ዓመቱ 15.4 ቢሊዮን ብር ለማግኘት ዕቅድ ይዞ የነበረ ቢሆንም ማሳካት የቻለው ግን 87.9 በመቶውን እንደሆነ ተገልጿል። ነገር ግን ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት አፈጻጸሙ ጋር ሲነፃፀር የ9.5 በመቶ ብልጫ አለው። ኢትዮ ቴሌኮም ካገኘው ገቢ ውስጥ ወጪዎቹን ቀናንሶ 5.93 ቢሊዮን ብር ትርፍ በሦስት ወራት ማግኘቱ ተገልጿል። ይሁን እንጂ የኢትዮ ቴሌኮም የሩብ ዓመት ትርፍ ከ2013 ዓ.ም. ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ25 በመቶ ቅናሽ ታይቶበታል።
የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት በበኩሉ ከባህርና የየብስ ትራንስፖርት አገልግሎቶች ማለትም ገቢና ወጪ ዕቃዎችን በማስተናገድ፣ ወጪ ጭነት በማሸግና ለላኪዎች ባዶ ኮንቴይነር በማቅረብ 9.71 ቢሊዮን ብር ገቢ በሦስት ወራት ማግኘት ችሏል። ዕቅዱ 11.9 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘት የነበረ መሆኑን ከግምት በማስገባት የሦስት ወራት ክንውኑ ከዕቅዱ 88 በመቶ ያህሉን እንዳሳካ ተገምግሟል። ድርጅቱ ያገኘው ገቢ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት በ61.4 በመቶ ከፍ ያለ ሲሆን፣ ከአጠቃላይ ገቢው ውስጥ ወጪውን ቀንሶ ከታክስ በፊት 1.45 ቢሊዮን ብር ማትረፉ ታውቋል።
የስኳር ልማት ኮርፓሬሽን በበኩሉ 51,391 ቶን ስኳር በመሸጥ ከ1.14 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘት እንደቻለ የተገለጸ ሲሆን፣ ኮርፖሬሽኑ የወጪ ቅነሳ ሥራ ተግባራዊ በማድረግ ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ ከወጪ ማዳን እንደቻለም ታውቋል።
ሌላው ተቋም የኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን ሲሆን፣ በሩብ ዓመት ውስጥ ከምርት ሽያጭና ከሌሎች ገቢዎች በድምሩ 643 ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱ በግምገማው ላይ ተጠቅሷል፡፡
የመንግሥት የልማት ድርጅቶች የሆኑት፣ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን፣ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ዲዛይንና ሱፐርቪዥን ሥራዎች ኮርፖሬሽን፣ የግዮን ሆቴሎች አገልግሎት ድርጅት፣ የኢትዮጵያ ፐልፕና ወረቀት አክሲዮን ማኅበር፣ የብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካና የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን በድምሩ 3.01 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘታቸው በተደረገው ግምገማ መረጋገጡ ተገልጿል።
በተመሳሳይም የፍል ውኃ አገልግሎት ድርጅት፣ የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት፣ የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሸን፣ የኢትዮጵያ ቱሪስት ንግድ ሥራ ድርጅትና የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት የሩብ ዓመቱ አጠቃላይ ድምር ገቢ ደግሞ 1.48 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ቀድም ሲል ሜቴክ በሚል ስያሜ የሚታወቀውና በድጋሚ የተዋቀረው የኢትዮ ኢንጂነሪንግ ግሩፕ በበኩሉ በሩብ ዓመቱ ከተሸከርካሪ፣ ከእርሻ መሣሪያዎች፣ ከኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክስ ቁሳቁሶች፣ ከኮንስትራክሽን ማሽነሪዎች፣ ከብረታ ብረት፣ መለዋወጫና ፋብሪኬሽንና ከፕላስቲክ ምርቶች ሽያጭ ብር 280.67 ሚሊዮን ብር ገቢ አግኝቷል።
ተቋሙ ለሩብ ዓመቱ በዕቅድ ይዞት የነበረው የገቢ መጠን 916.70 ሚሊዮን ብር ሲሆን፣ ከዕቅዱ አኳያ ሲመዘን አፈጻጸሙ 31 በመቶ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ተቋም ለበርካታ ዓመታት በኪሳራ ውስጥ የነበረ ከመሆኑ አንፃር አፈጻጸሙ ወደ ትርፋማነት የሚያሸጋግረው እንደሚሆን ተገምግሟል።