ጠቅላይ ፍርድ ቤት ድጋሚ ምርጫ እንዲካሄድ በወሰነበት የቁጫ ምርጫ ክልል፣ የክልል ምክር ቤት ምርጫ የተመዘገቡ ከፊል ዕጩዎች በድጋሚ ምርጫው እንደማይሳተፉ በመታወቁ፣ በቀደመው ምርጫ ያሸነፉት ተወዳዳሪዎች ውሳኔ እንዲፀና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ወሰነ።
ቦርዱ ማክሰኞ ኅዳር 7 ቀን 2014 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ ከቁጫ ምርጫ ክልል ድምፅ መስጫ ወረቀት ጋር በተያያዘ ኢዜማ ያቀረበውን አቤቱታ የተመለከተው የጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት፣ ነሐሴ 21 ቀን 2013 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ድጋሚ ምርጫ እንዲደረግ ውሳኔ መስጠቱን አስታውሷል።
ነገር ግን ከችሎቱ ውሳኔ በኋላ በተከሰቱ ለውጦች የተነሳ ውሳኔውን ለማስፈጸም በመቸገሩ፣ ፍርዱን የሰጠው ችሎት አፈጻጸሙን የተመለከተ ማብራሪያ እንዲሰጠው መጠየቁን ገልጿል።
ከፍርድ ቤቱ ውሳኔ በኋላ በፓርቲው በኩል በተደረጉ ለውጦች ማለትም የፓርቲው ሁለት ዕጩዎች ከምርጫ ውድድሩ ራሳቸውን በፈቃዳቸው ማግለላቸውን በ10/01/2014 ዓ.ም. በጻፉት ደብዳቤ ለቦርዱ በማሳወቃቸው፣ እንዲሁም ሌላዋ የፓርቲው ዕጩ ተወዳዳሪ ፓርቲውን ወክለው እንዳይወዳደሩ የፓርቲው የወረዳ ጽሕፈት ቤት ያገዳቸው መሆኑን በ28/01/2014 ዓ.ም በማሳወቁ፣ ፓርቲውም በዚህ ምርጫ ክልል ስላሉት ዕጩዎች ማብራሪያ ሲጠየቅ ራሳቸውን ማግለል አይችሉም የሚል ምላሽ ከመስጠት ውጪ ተጨማሪ ሐሳብ አለማቅረቡን በመጥቀስ፣ የድጋሚ ምርጫውን አፈጻጸም በተመለከተ ውሳኔ የሰጠው ፍርድ ቤት ማብራሪያ እንዲሰጠው ቦርዱ መጠየቁን አስታውቋል።
ፍርድ ቤቱ በሰጠው ምላሽም፣ ከተሰጠው ፍርድ በኋላ አዲስ ሁኔታ ከተፈጠረ፣ በዚያው መሠረት ቦርዱ መወሰን እንደሚችል ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መስጠቱን ቦርዱ አስታውቋል።
ይህንን ትዕዛዝ መሠረት በማድረግም በገዛ ፈቃዳቸው በድጋሚ ምርጫው ለመሳተፍ ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ያስታወቁትን ሁለት ዕጩዎችን የሚተኩ ዕጩዎች ፓርቲው በወቅቱ ባለማቅረቡ፣ እንዲሁም አንደኛዋ ዕጩ በፓርቲው የወረዳው ጽሕፈት ቤት ከውድድሩ እንዲወጡ በመወሰኑ፣ ድጋሚ ምርጫ ለማድረግ መሠረት የሆነው ሁኔታ የተቀየረ በመሆኑ ድጋሚ ምርጫ ለማድረግ የማይቻል መሆኑን ቦርዱ መገንዘቡን አስታውቋል።
በመሆኑም በቁጫ ምርጫ ክልል ድጋሚ ምርጫ ይደረግባቸው በማለት ፍርድ ቤቱ በሰጠው ውሳኔና ትዕዛዝ መሠረት ዳግም ምርጫውን ማከናወን የማይቻለው መሆኑን፣ ቦርዱ ጥቅምት 26 ቀን 2014 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ እንደወሰነ አስታውቋል።
ይህንንም መሠረት በማድረግ በምርጫ ክልሉ የሚገኘው ሕዝብ ያለ ተወካይ እንዳይቀር በቀደመው ምርጫ አሸናፊ ናቸው ተብለው በቦርዱ የተወሰኑት ዕጩ ተወዳዳሪዎች፣ በምክር ቤቱ ተገኝተው የክልላቸው ሕዝብ ሕጋዊ ወኪል ሆነው እንዲያገለግሉ መወሰኑን ቦረዱ አስታውቋል፡፡