በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የዓለም የምግብና የግብርና ድርጅት (ፋኦ) የኢትዮጵያ ጽሕፈት ቤት ለአንበጣ መከላከያ ድጋፍ ሰጥቶ የነበረውን ሔሊኮፕተሮች እንዳያበር መከልከሉ ታወቀ። ድርጅቱ ሔሊኮፕተሮቹ በኢትዮጵያ የአስቸኳይ ጊዜ መታወጁን ተከትሎ እንዳይበሩ ማድረጉን፣ አንድ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣን ለሪፖርተር አረጋግጠዋል።
ለተመሳሳይ ተግባር በግብርና ሚኒስቴር ግዥያቸውን ለመፈጸም በሒደት ላይ የነበሩ ሔሊኮፕተሮችና ድሮኖች፣ የዓለም ባንክ ለሌላ ዓላማ ሊውሉ ይችላሉ በሚል ምክንያት ብድሩን ማጓተቱ ታውቋል።
በኢትዮጵያ የምግብና ግብርና ድርጅት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ታምሩ ለገሰ፣ ስለክልከላው በሪፖርተር ተጠይቀው መረጃ እንደሌላቸው ተናግረዋል። ‹‹ለአንበጣ አሰሳና ለኬሚካል መርጫ የሰጠናቸው ሔሊኮፕተሮች እስከቅርብ ጊዜ ድረስ ሲሠሩ እንደነበረ አውቃለሁ። ከአዋጁ ጋር ተያይዞ ቆመው ከሆነ ከአለቆቼ አረጋግጬ እመልሳለሁ፤›› ቢሉም ለኅትመት እስከገባንበት ድረስ ምላሽ ሊሰጡ አልቻሉም።
ድርጅቱ ሔሊኮፕተሮችን ኬንያና ደቡብ አፍሪካ ካሉ ትልልቅ የግል እርሻ ባለቤቶች በማስመጣት ኪራያቸውንና ነዳጅ እየቻለ፣ በግብርና ሚኒስቴር ውስጥ ለተቋቋመው የአንበጣ መከላከል ግብረ ኃይል ድጋፍ ሲያደርግ እንደነበር ይታወቃል።
ለሦስት ዓመታት ምሥራቅ አፍሪካን ሲያምስ የነበረው የበረሃ አንበጣ የመዛመት ፍጥነቱ በአሁኑ ጊዜ የተገታ ቢመስልም፣ በማንኛውም ወቅት ተመልሶ ዕፅዋትና ሰብል ሊያወድም እንደሚችል ሥጋት አለ።
‹‹አገራዊ አቅም እየገነባን ነበረ። ነገር ግን ብዙ የውጭ ጫና እየተደረገብን ነው፤›› ሲሉ ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁት ባለሥልጣን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ለዓለም ባንክ ጽሕፈት ቤት በጽሑፍና በስልክ ጥያቄ ቢቀርብም ምላሽ ማግኘት አልተቻለም።