- ሦስት ጨዋታ ያለ ደጋፊ እንዲጫወትም ተወስኖበታል
በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም እየተካሄደ በሚገኘው ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሚሳተፈው የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ክለብ፣ በፋሲል ከነማ የደረሰበትን ሽንፈት ተከትሎ ደጋፊዎቹ ባስነሱት ሁከት ምክንያት ለደረሰው ጥፋት በፌዴሬሽኑ የዲሲፕሊን ቅጣት ተላልፎበታል፡፡ በውሳኔው መሠረት ሲዳማ ቡና 150 ሺሕ ብር ቅጣትና በቀጣይ በሜዳው በሚያደርጋቸው ተከታታይ ሦስት ጨዋታዎች ያለ ደጋፊ የሚጫወት ይሆናል፡፡
የሊጉ የውድድር አመራርና ሥነ ሥርዓት ኮሚቴ ባለፈው ሰኞ ታኅሣሥ 4 ቀን 2014 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ፣ በሰባተኛው ሳምንት በተደረጉት ጨዋታዎች ከጨዋታ ዳኞችና ታዛቢዎች በደረሰው የዲሲፕሊን ጥሰት ሪፖርት መሠረት የተለያዩ ውሳኔዎችን ማሳለፉን ይፋ አድርጓል፡፡
ኮሚቴው እንዳስታወቀው ከሆነ፣ የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ክለብ ከፋሲል ከተማ እግር ኳስ ክለብ ጋር በነበረው ጨዋታ፣ የክለቡ ደጋፊዎች የክለቡን ዋና አሠልጣኝና የዕለቱን የጨዋታ አመራሮችን ጨምሮ ሌሎች አካላትን በግልጽ አፀያፊ ስድብ ሲሳደቡ መደመጣቸው፣ ከደጋፊዎቹ በተጨማሪ የክለቡ አስተባባሪዎች የክለቡ ተጨዋቾች ጨዋታውን ጨርሰው ሲወጡ ግጭት እንዲፈጠር ማድረጋቸው፣ ግጭቱን ተከትሎ የዩኒቨርሲቲው ስታዲየም ወንበሮችና መስተዋቶች በድንጋይ መሰባበራቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡
ጥፋቱ የመጀመርያ እንዳልሆነና ደጋፊዎቹ ቀደም ሲል በነበሩ ጨዋታዎች ላይ ተደጋጋሚ ጥፋት መፈጸማቸውን ያስታወሰው ኮሚቴው፣ ሁኔታው ከመሻሻል ይልቅ እየባሰ በመምጣቱ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዲሲፕሊን መመርያ በክፍል 3 አንቀጽ 66 ተራ ቁጥር 4(ሀ) መሠረት፣ ክለቡ የ150,000 ብር ቅጣት እንዲከፍል፣ ደጋፊዎቹን በተመለከተ ደግሞ ክለቡ በቀጣይ በሜዳው በሚያደርጋቸው ተከታታይ ሦስት ጨዋታዎች ያለ ደጋፊ በዝግ ስታዲየም እንዲጫወት ተወስኖበታል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ክለቡ በግጭቱ ምክንያት የተሰባበሩና የተነቃቀሉ ወንበሮችና ሌሎች ንብረቶችን እንዲያሠራ፣ ካልሆነም ለግንባታው ወጪ ባለ ንብረቱ በሚያቀርበው ዋጋ መሠረት ክፍያውን እንዲፈጽም ተወስኗል፡፡
ሲዳማ ቡና በቀጣይ በሜዳው ከወላይታ ድቻና ከባህር ዳር ከተማ እንዲሁም ከሜዳው ውጪ ደግሞ ከመከላከያ ጋር የሚያደርጋቸው ጨዋታዎች በውሳኔው መሠረት የሚከናወኑ ይሆናል፡፡
ሲዳማ ቡና በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች ሰባት ነጥብ በመያዝ በደረጃ ሰንጠረዡ 13ኛ ላይ ይገኛል፡፡