የአሁኑ ወቅት አራተኛው የቴክኖሎጂ አብዮት ዘመን ዓይነተኛው መገለጫም ‹‹ዲጂታል አብዮት›› መሆኑ ይታወሳል፡፡ ይህም በፍጥነቱ፣ በተደራሽነቱና በተፅዕኖ ፈጣሪነቱም ወደር የለሽ መሆኑ ይነገርለታል፡፡ ዲጂታል ቴክኖሎጂ ዛሬ ያልደረሰበት የዓለም ጫፍ፣ ተፅዕኖ ያልፈጠረበትም የሥራ መስክ የለም፡፡ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ውስጥ መጠነ ሰፊ ሥራዎች ከሚታዩባቸውና ለውጥ እያስመዘገቡ ከመጡ ሴክተሮች መካከል የጤናው ሥርዓት ተጠቃሽ ነው፡፡
በዲጂታል ጤና ሥርዓት ግንባታ ውስጥ የማኅበረሰብ አቀፍ የጤና መረጃ ሥርዓት በሁሉም የጤና ዘርፍ ዕርከኖች መረጃዎችን ለመተንተን፣ ለመሰብሰብና ለውሳኔ ሰጪነት ለማብቃት እያገለገለ ነው፡፡
ከዚህ አንፃር የወጣቶችና አፍላ ወጣቶች ጤና መረጃና ክህሎት ለማስፋፋት የማያገለግል ‹‹የኔታብ›› የተሰኘ የእጅ ስልክ መተግበሪያ ከሰሞኑ ይፋ ሆኗል፡፡
የጤና ሚኒስቴር የእናቶችና የሕፃናት ጤናና የሥነ ምግብ ዳይሬክተር መሠረት ዘለዓለም (ዶ/ር) መተግበሪያውን ይፋ ባደረጉበት ወቅት እንደገለጹት፣ ቴክኖሎጂው ከ14 እስከ 25 ዓመት ዕድሜ ላላቸው አፍላ ወጣቶችና ወጣቶች አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ቋንቋዎቹ አማርኛ፣ አፋን ኦሮሞ፣ ሶማሊኛ፣ ትግርኛና እንግሊዝኛ ናቸው፡፡
አገልግሎቶቹም አካልን ለመረዳት፣ መልካም ጓደኝነትን ለመመሥረት፣ የሥነ ተዋልዶ ጤና ክህሎትን ለማዳበር፣ የሱስና የሱሰኝነት ተጋላጭነትን ለመቋቋም፣ ሥርዓተ ምግብን ለማሻሻልና የሕይወት ክህሎትን ለማዳበር የሚያስችሉ ይገኙባቸዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ከኢትዮጵያ የመረጃ መረብ ደኅንነት የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ‹‹የዲጂታል ኢትዮጵያ 2012 እስከ 2017 ዓ.ም. አገራዊ ስትራቴጂ›› ካተኮረባቸው ርዕሰ ጉዳዮች መካከል አንደኛው የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎኖጂን በመጠቀም የሚሰጡ የአገልግሎቶችን ሽፋን በፍጥነት ማስፋፋትን ያመለከተ መሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡