የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) እና ሌሎች ሰብዓዊ ድጋፍ ሰጪዎች በሶማሊያ ላለፉት ሰባት ወቅቶች ብቁ ዝናብ ባለመገኘቱ ለድርቅ የተጋለጡ ሶማሊያውያንን ለመርዳት 1.5 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልጋቸው አስታወቁ፡፡
ድርጅቶቹ ለድርቅ በይበልጥ ተጋላጭ የሆኑ 5.5 ሚሊዮን ዜጎችን እ.ኤ.አ. በ2022 ለመርዳት የ1.5 ቢሊዮን ብር ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው ሲገልጹ፣ በተመድ የሰብዓዊ ድጋፍ ጉዳዮች (አቻ) ከአደጋ ጊዜ ምላሽ ፈንድ 17 ሚሊዮን ዶላር በድርቅ ለተጎዱ የማኅበረሰብ ክፍሎች እንደሚለቅ አስታውቋል፡፡
የሶማሊያ ሕዝብ የተጋረጠበትን የተፈጥሮ አደጋ ለመቀልበስና ለተጨማሪ ረሃብ እንዳይጋለጥ ዕርዳታውን እንደሚያደርጉ ድርጅቶቹ ገልጸዋል፡፡ ድርጅቶቹ ሱማሊያን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ ሶማሊያውያን ከአሥርት በላይ ለዘለቀ ጦርነት፣ በተከታታይ ለሚከሰት የአየር ንብረት ለውጥ አደጋ፣ ለበሽታዎች ወረርሽኝ እንዲሁም በኮቪድ-19 ተፅዕኖ እየተፈተኑ ይገኛሉ፡፡ በምሥራቅ አፍሪካ ለረዥም ጊዜ የቆየው የበረሃ አንበጣም በሰብሎች ላይ ጉዳት አድርሷል፡፡ አሁን ላይ ከአሥር ዜጎች ሰባቱ ከድህነት ወለል በታች እየኖሩም ይገኛሉ ብሏል፡፡
እ.ኤ.አ. በ2022 7.7 ሚሊዮን ሶማሊያውያን የሰብዓዊ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው ሲሆን ከዚህ በፊት 5.5 ሚሊዮኑ አፋጣኝ ድጋፍ የሚሹ ናቸው፡፡ የተረጂዎች ቁጥርም በዓመት ውስጥ በ30 በመቶ አድጓል፡፡
አሁን ላይ ደግሞ ከሰላሳ ዓመታት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ በአገሪቱ ለሦስት ተከታታይ የምርት ወቅቶች ዝናብ አለመዝነቡ ችግሩን አባብሶታል፡፡
ድርቁ የሰዎችን ሕይወት አደጋ ላይ ጥሏል፡፡ በተለይም ከአምስት ዓመት በታች ያሉ ሕፃናት የችግሩ ቀዳሚ ተጋላጭ ሆነዋል፡፡
ዕርዳታቸው ከአምስት ዓመት በታች የሚገኙ አንድ ሚሊዮን ሕፃናትን ጨምሮ ለአምስት ሚሊዮን ዜጎች በቅድሚያ የሕይወት አድን ድጋፍ እንደሚሰጥ ተመድ አስታውቆ ይህም የረሃብን መጠን የበሽታ ወረርሽኝ፣ ጥቃትን ለመቀነስ ያስችላል ብሏል፡፡
አጋር ድርጅቶች 3.9 ሚሊዮን በመጠለያ ካምፕ ቅድሚያ ድጋፍ የሚፈልጉ ውስጥ ያልገቡትን ጨምሮ 1.6 በመጠለያ ያሉና አካል ጉዳት ያለባቸው በ74 ቀጣናዎች የሚገኙ ሱማሊያውያንን እንደሚረዱም ጠቁሟል፡፡
በ2021 ብቻ 777 ሺሕ ሶማሊያውያን ግጭትን በመሸሽ ከቤታቸው ተሰደዋል፡፡ እነዚህን ጨምሮ 2.9 ዜጎች በአገር ውስጥ ተፈናቅለዋል፡፡ አብዛኞቹ ተፈናቃዮች በአደገኛ ሁኔታ ውስጥ የሚኖሩና አስቸኳይ ዕርዳታ የሚፈልጉ ናቸው፡፡
ሴቶችና ሕፃናት ግማሽ ያህሉን የተፈናቃዮች ቁጥር የሚይዙ ሲሆን፣ ለትንኮሳና ለፆታዊ ጥቃትም የተጋለጡ ናቸው፡፡
ድርቁ ደግሞ ቀድሞ የነበረውን አስቸጋሪ ሁኔታ አባብሶታል፡፡ በቀጣዮቹ ስድስት ወራትም በድርቅ ብቻ 1.4 ሶማሊያውያን ከቀዬአቸው ይፈናቀላሉ ሲል ተመድ ገልጿል፡፡ አሁን ላይ በርካታ የቀንድ ከብቶች እየሞቱ መሆናቸው እየተነገረ ሲሆን፣ የምግብ፣ የውኃና የነዳጅ ዋግ በፍጥነት እያሻቀበ ነው፡፡ በጥር 2022 ሱማሊያ ልታመርት ትችላለች ተብሎ የሚጠበቀው ሰብልም ባለፉት አሥር ዓመታት …….ከነበረው ምርት ከ50 በመቶ እስከ 70 በመቶ ያነሰ እንደሚሆን ተተንብይዋል፡፡
ከወራት በፊት ጀምሮ በሶማሊያ የተከሰተው ድርቅ ሰዎች ምግብና ውኃ ፍለጋ ቀያቸውን ለቀው እንዲሰደዱ እያደረገ ነው፡፡
በሶማሊያ በተከታታይ ዓመታት ያጋጠመ ድርቅ እንዲሁም ለአሥርታት የዘለቀ ግጭት በተለይ ሕፃናትና ሴቶችን ጎድቷል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2021 ብቻ በመላ ሶማሊያ 5.9 ሚሊዮን ዜጎች የሰብዓዊ ዕርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ተተንብዮ የነበረ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 15 በመቶ ሴቶችና እናቶች 66 በመቶ ደግሞ ሕፃናት ነበሩ፡፡