በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል ከሰኔ ወር 2013 ዓ.ም. አንስቶ የተፈጸሙ ወንጀሎችን የማጣራት ሥራ መጀመሩንና የወንጀል ምርመራው ዓለም አቀፍ ደረጃን ባሟላ መልኩ የሚከናወን በመሆኑ፣ በወንጀሉ የተሳተፉ የውጭ ዜጎች ተጠያቂነትን ጭምር የሚያረጋግጥ እንደሚሆን የፍትህ ሚኒስቴር አስታወቀ።
የፍትህ ሚኒስቴር ዓርብ ታኅሳስ 15 ቀን 2014 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ በፍትህ ሚኒስቴር የሚመሩ የወንጀል ምርመራና ማስቀጣት ቡድኖች፣ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል የተፈጸሙ ወንጀሎችን በመመርመር አጥፊዎችን በሕግ ተጠያቂ ለማድረግ የሚያስችል የወንጀል ምርመራ ለማከናወን፣ ከሕወሓት ኃይል ነፃ በወጡ የሰሜኑ የአገሪቱ አካባቢዎች መሰማራት መጀመራቸውን ገልጿል።
በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍሎች የተፈጸሙት ወንጀሎች ዓለም አቀፋዊ ወንጀሎችን የሚያቋቁሙ በመሆናቸው፣ በሁሉም ቦታዎች የሚከናወኑት የወንጀል ምርመራዎች፣ ዓለም አቀፍ ደረጃን እንዲያሟሉ በዓለም አቀፍ የወንጀል ሕግ ዙሪያ የተሻለ ዕውቀትና የረዥም ጊዜ ልምድ ያላቸው ባለሙያዎችን በማሳተፍ ‹‹ቼክ ሊስት›› የማዘጋጀት ሥራ መሠራቱንም ገልጿል።
ይህም የምርመራውን ጥራትና ወጥነት ለማስጠበቅ የሚረዳ ከመሆኑም ባለፈ፣ በወንጀሉ የተሳተፉ የሌሎች አገሮች ዜጎችን፣ በራሳቸው በአገራቱ ሕግና የፍትህ ሥርዓት አማካኝነት ክስ መሥርተው ለማስቀጣት ወይም በዓለም አቀፉ የወንጀል ፍርድ ቤት ከተጠየቁም አሳልፈው ለመስጠት ትብብር የማድረግ ግዴታቸውን ሳያመነቱ እንዲወጡ እንደሚያስችል ገልጿል።
ባለፈው ዓርብ ታኅሳስ 15 ቀንም በዋግምራና ወልዲያ ከተሞች፣ የወንጀል ምርመራ የሚያካሂድ ቡድን ወደ ሥፍራው መላኩን ያመለከተው ፍትሕ ሚኒስቴር፣ ቀደም ብሎም በአፋር ክልል አንድ ቡድንና ሁለት ንዑሳን ቡድኖች ያሉት የምርመራ ቡድን ማሰማራቱን አስታውቋል።
በተጨማሪም ሸዋ ሮቢትን ጨምሮ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ሥር የሚገኙ አሥር ወረዳዎችን፣ በደቡብ ወሎ በሚገኙ ስምንት ወረዳዎችን፣ የኦሮሞ ማኅበረሰብ ልዩ ዞን፣ በደሴና በኮምቦልቻ፣ ጋሸናን ጨምሮ በሰሜን ወሎ ዞን ሥር ያሉ ወረዳዎችን ሸፍነው ምርመራ የሚያከናውኑ፣ የተለያዩ የምርመራ ቡድኖችን ወደ ቦታው በመላክ አሸባሪው ቡድን የፈጸማቸውን ወንጀሎች በመመርመር ላይ እንደሚገኙ ገልጿል።
የተመድና የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ተቋማት ጥምር የሰብዓዊ መብት ጥሰት ምርመራ ቡድን ባቀረበው ምክረ ሐሳብ መሠረት፣ በትግራይ ክልል ውስጥ የተፈጸሙ ወንጀሎችን ለመመርመር የሚያስችል በቂ ዝግጅት የተደረገ ሲሆን፣ አሁን በአካባቢው ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት የምርመራ ሒደቱ በምን መልኩ ሊመራ እንደሚገባ በቀጣይ እየተገመገመ የሚቀጥል መሆኑንም ገልጿል።
‹‹የአሸባሪው ሕወሓት የጥፋት ቡድን የፈጸማቸውን ግድያዎች፣ የአካል ጉዳቶች፣ የዜጎች መፈናቀል፣ የወደሙ ቅርሶችን፣ የመሠረተ ልማት አውታሮች፣ የመንግሥትና የግለሰቦች ንብረቶችንና ሌሎች የፈጸማቸውን እኩይ ተግባራት፣ በቼክ ሊስት እየተመሩ የምርመራ ሥራውን ሌት ተቀን በማከናወን ላይ ይገኛል›› ያለው ሚኒስቴሩ፣ በዚህም ቡድኑ ውስጥ በመሪነት፣ በአድራጊነት፣ በአጋዥነት፣ በአነሳሽነት ወይም በሌላ ማንኛውም ዓይነት አቅም ደረጃ የታሳተፉ የቡድኑን አባላት ለመለየት በሚያስችል መንገድ እንደሚከናወን ገልጿል።
‹‹ጎን ለጎንም የመከላከያ ሠራዊትና የፌዴራል ፖሊስ አባላት ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ሥር የማዋልና አጥፊዎችን በፍትህ አደባባይ አቅርቦ ፍትህ የሚሰጥበት ሁኔታ ለመፍጠር ተገቢው ሥራ ይሠራል፤›› ብሏል።
በአጠቃላይ የምርመራ ሒደቱ ተጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን፣ በቅርቡ ከሕወሓት ኃይል ነፃ በወጡ አካባቢዎች ሁሉ ሰፊና ጥልቀት ያለው የወንጀል ምርመራ የሚደረግና የምርመራውን ግኝትም ለሕዝቡ እንደሚገልጽ ያስታወቀው ሚኒስቴሩ፣ ማኅበረሰቡም ለምርመራ ቡድኖቹ ጥቆማና መረጃ እንዲሁም ለምርመራ አስፈላጊ የሆኑ ድጋፎችን በመስጠት፣ ትብብር እንዲያደርግና በወንጀል የተሳተፉ ሰዎች ከሕግ ተጠያቂነት እንዳያመልጡ የዜግነት ድርሻውን እንዲወጣ አሳስቧል።