‹‹ጉንፋን ወይም ኮሮና መሆኑን መለየት የሚቻለው በምርመራ ብቻ ነው››
የሕክምና ባለሙያዎች
በአዲስ አበባ ከተማና በተለያዩ አካባቢዎች ሰሞኑ በወረርሽኝ መልክ እየተሠራጨ ያለው ጉንፋን ምልክቶች ከተለመደው የጉንፋን ዓይነት የተለየና በፍጥነት የመሠራጨቱ ሁኔታ ከፍተኛ ሥጋት እንደፈጠረባቸው ነዋሪዋች ተናገሩ፡፡
ነዋሪዎቹ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ድንገት በማስነጠስ ይጀምርና ወደ ራስ ምታት፣ በሰውነት መገጣጠሚያዎች አካባቢ የቁርጥማት ስሜት ከማስከተሉም በተጨማሪ ምራቅን መዋጥ እስከሚያዳግት ድረስ የጉሮሮ ሕመምና ሳል እንዳለው ገልጸዋል፡፡
ምንም እንኳን በመንግሥት ወይም በጤና ተቋማት አማካይነት ምርመራ እየተደረገበት እንደሆነ ከመግለጽ ያለፈ መረጃ ባይኖራቸውም፣ በውጭ የመገናኛ ብዙኃን እየተነገረ ካለው መረጃ አንፃር አዲሱ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ (ኦሚክሮን) ይሆናል የሚል ጥርጣሬ እንዳደረባቸውና ሥጋት ውስጥ መሆናቸውን አክለዋል፡፡
ነዋሪዋች እያነሱ ያሉትን የሰሞኑን ወረርሽኝ መሳይ ጉንፋን አስመልክቶ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሕክምና ኮሌጅ ረዳት ፕሮፌሰርና የሕፃናት ስፔሻሊስት ሐኪም የሆኑት ፋሲል መንበረ (ዶ/ር)፣ በኮሌጁ ድረ ገጽ ላይ ባሰፈሩት ማብራሪያ የሰሞኑ ጉንፋን ለየት የሚያደርገው ከፍተኛ ትኩሳትና ጠንከር ያለ ሳል አለው፡፡ በተጨማሪም ብርድ ብርድ ማለት፣ የመገጣጠሚያ ሕመም፣ የጀርባ ሕመም፣ የጡንቻ ሕመም፣ የምግብ ፍላጎት መቀነስ፣ ኃይለኛ ራስ ምታትና ፍዝዝ የማለት ምልክቶች ይታዩበታል፡፡
ምክንያቱ ምን ሊሆን እንደሚችል ያብራሩት ፋሲል (ዶ/ር)፣ ጉንፋን ዋና መንስዔዎቹ በትንፋሽ፣ በሳልና በማስነጠስ የሚተላለፉ ቫይረሶች ናቸው፡፡ ለምሳሌ ኮሮና ቫይረስ፣ ራይኖ ቫይረስ፣ ኢንፍሉዌንዛ አዴኖ ቫይረስና የመሳሰሉት ጉንፋንን ሊያመጡ እንደሚችሉ ጠቁመው፣ ‹‹የሰሞኑ ጉንፋን ኮሮና ይሁን አይሁን የሚታወቀው በምርመራ ብቻ ነው፤›› ብለዋል፡፡
መፍትሔውም የመከላከያ መንገዶቹን ማለትም አፍና አፍንጫን መሸፈን፣ የእጅና አካል ንክኪ መቀነስ፣ ሰዎች የሚሰበሰቡበት ቦታ አለመገኘት፣ ስያስሉና ሲያስነጥሱ አፍና አፍንጫን በክንድ ወይም በጨርቅ መሸፈንና መንግሥት በነፃ ያቀረበውን የኮሮና ክትባት መውሰድ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
ልጆችንና ሕፃናትን የቤት ውስጥ ሕክምና መስጠት እንደሚቻል የገለጹት ፋሲል (ዶ/ር)፣ ለብ ያለ ውኃ ውስጥ ትንሽ ጨው አድርጎ አፍንጫቸው ቀዳዳ ውስጥ ሁለት ጠብታ ማድረግና የአፍንጫ ቀዳዳዎችን በመምጠጫ ማፅዳት፣ ትኩሳትን የሚቀንስ መድኃኒት መጠቀም፣ ትኩስ ትኩስ ነገሮችን ማጠጣት፣ ተጨማሪ ምግቦችን በደንብ መመገብ፣ የሕፃናቱን ክፍል በደንብ ማፅዳትና ማናፈስ፣ ቤቱን በውኃ እንፋሎት ማጠን፣ ንፍጥና ትኩሳት በጣም አስፈላጊ ፈሳሾችንና ንጥረ ነገሮችን ይዘው ስለሚወጡ ተጨማሪ ፈሳሽ ነገሮችን ማግኘት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
ለታዳጊ ሕፃናትና ለአዋቂዎችም የቤት ውስጥ ሕክምናን በሚመለከት ከላይ ከተዘረዘሩት በተጨማሪ ራስን በአንድ ክፍል ማግለል፣ ትኩስ ፈሳሽ ነገሮችን ደጋግሞ መውሰድ፣ ነጭ ሽንኩርት፣ ማርና ዝንጅብል መጠቀም፣ በቂ እረፍት ማድረግ፣ የትኩሳትና ራስ ምታት ማስታገሻ መውሰድ ጥሩ እንደሆነ አሳስበዋል፡፡ ምንም ለውጥ ከሌለውና ሳሉ የመባስና ትኩሳቱ የመጨመር ባህሪ ወይም ትንፋሽ የማጠር ምልክት በሕፃንም ሆነ በአዋቂ ላይ ካለ በአፋጣኝ ሆስፒታል መሄድ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፡፡